• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ነሐሴ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ በዓለ ዕርገት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በመላው ዓለምና በሀገር ውስጥ ሆናችሁ፣ በፍቅረ እግዚአብሔርና በፍቅረ ቅድስት ድንግል ማርያም ተስባችሁ፣ የጾመ ፍልሰታ ለማርያምን በጾም ፣ በጸሎት፣ በምጽዋት፣ በአምልኮና ቅዱስ ቊርባንን በመቀበል ያሳለፋችሁ የተወደዳችሁና የተከበራችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት በሙሉ፡፡

በቅዱስ አጠራሩ ወደ እርሱ ያቀረበን፣ ከቅዱሳን ጋር ሰማያዊ ርስቱን እንድንካፈል ያደረገ፣ ሰውን የሚወድ፣ መሓሪውና ይቅር ባዩ አምላካችን እግዚአብሔር እንኳን ለሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት በዓለ ፍልሰታ ለቅድስት ድንግል ማርያም በሰላም አደረሳችሁ!!

“እስመ ኅሉቀ ወምቱረ ነገር ይነግር እግዚአብሔር ውስተ ዓለም ዘሀለዎ ይግበር
እግዚአብሔር በዓለም ውስጥ ያደርገው ዘንድ ያለውን ያለቀና የተቈረጠ ነገርን ይናገራል።”
(ሮሜ 9÷28)፡፡

ይህንን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የትምህርተ ወንጌል መርሐ ግብር በመከታተል የምትገኙ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፣ በዛሬው ትምህርታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ነገረ ትንሣኤ እንማራለን፤ በዚህ መነሻነትም እግዚአብሔር ከሞት በኋላ ስላለው አጠቃላይ ዘለዓለማዊ ሕይወት የገለጸልንን እንሰማለን፡፡ በተለይም የእኛ የሰው ልጆች ትልቁና የመጨረሻው ተስፋችን ትንሣኤ ሙታን ስለሆነ በዚህ ዙሪያ እግዚአብሔር በተግባርና በትምህርት የገለጸልንን እንመለከታለን፤ ስለሆነም ቃሉን ሰምተን እንድናስተውልና ለእርሱ ታዛዥ ሆነን በቃሉ እንድንኖር እግዚአብሔር ዐይነ ልቡናችንን ያብራልን፡፡

የትምህርታችን ርእስ፦ “እስመ ኅሉቀ ወምቱረ ነገረ ይነግር እግዚአብሔር ማለትም እግዚአብሔር ያደርገው ዘንድ ያለውን ያለቀና የተቈረጠ ነገርን ይናገራልና” የሚል ነው ፡፡

በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ በግልጽ እንደተጻፈው የሙታን መነሣትን በተመለከተ እግዚአብሔር ያለቀና የተቈረጠ ጉዳይ እንደሆነ በብዙ ቦታ በማያሻማ መልኩ አሳውቆናል፡፡ ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር የሚያደርገውን ሥራ ለወዳጆቹ ለነቢያት ሳይገልጽ የሠራበት ጊዜ የለም፣ ሲናገርም ግልጽና የማያሻማ አድርጎ በቊርጥ እንደሚያሳውቅ የርእሳችን ኀይለ ቃል ያሳያል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በነቢዩ በአሞጽ አድሮ እንደገለጸው “እስመ አልቦ ዘይገብር እግዚአብሔር ዘኢተናገረ ወዘኢከሠተ ለአግብርቲሁ ነቢያት፤ በእውነት ጌታ እግዚአብሔር (ምሥጢሩን) ለባሪያዎቹ ለነቢያት ያልገለጸውናን ያልተናገረውን ምንም አያደርግም” ብሏል (አሞ. 3÷7)። እነዚህ ጥቅሶች እግዚአብሔር ለወደፊት ሊያደርግ ያሰበውን ሥራ ለወዳጆቹ ሳይገልጽ እንደማይሠራ ያስገነዝባሉ።

እኛም ኅሊናችንን እና መንፈስ ቅዱስን አስተማሪ፣ መሪ አድርገን ነገሩን ስናጤነው ትክክለኛ መሆኑን ለመረዳት አስቸጋሪ ሆኖ አይታይም፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ሥራዎቹን ሁሉ ከመሆናቸው በፊት ለነቢያቱ እየገለጸ እንደሠራ፣ ለነቢያቱ ከገለጸውም አንዳች ስንኳ ሳያስቀር እንደፈጸመ በብዙ ቦታ ተጽፎ እናገኘዋለንና ነው፤ ይኸውም እውነት እንደሆነ በቅዱስ መጽሐፍ፣ በታሪክ ፍጻሜ፣ በሥነ ምድር ጥናት ሳይቀር የተረጋገጠና በየጊዜው እየተረጋገጠ ያለ ሐቀ ነው፡፡ እግዚአብሔር ካሁን በፊት ተናግሮ ሳይፈጽመው የቀረ ነገር እንደሌለ፣ ለወደፊትም ከተናገረው ውስጥ የሚቀር ነገር እንደሌለ መገንዘብ ከእኛ ከፍጡራኑ ይጠበቃል፡፡

እግዚአብሔር ግልጽ አድርጎና በማያወላውል ሁኔታ ከተናገረው ውሰጥ ያልተፈጸመው አንዱና ዋነኛው የትንሣኤ ሙታን ነገር ነው፤ ይህም ቢሆን ፍጻሜው ስላልደረሰ ጊዜውን እየጠበቀ ያለ ጉዳይ እንጂ የሚቀር ሆኖ አይደለም፤ ከዚህ አኳያ እግዚአብሔር ስለ ትንሣኤ ሙታንና ስለቀጣዩ ለዘለዓለማዊ ሕይወት በትምህርትም፣ በቃልም፣ በተግባርም አስተምሮአል አሳይቶአልም፡፡ በእግዚአብሔር ቊጣ አጠገብ ምሕረቱም አይለይምና ሰዎችን ከኀጢአታቸው የተነሣ ተቈጥቶ ከገነት ካስወጣ በኋላ ፍጡራን የአቤልን መሞት በተረዱበት ማግስት ሄኖክን ሳይሞት እንዳለ ከነሥጋው ወደ ሕይወታዊ ዓለም መውሰዱ ሞት ብቻ ሳይሆን ከሞት በኋላም ሕይወት እንዳለ እግዚአብሔር ለሰዎች የተናገረበት ክሥተት ነበረ፤ ሰዎች ይህንን የሄኖክን አለመሞት አይተው በተስፋ መሞላታቸውን ሲያመለክት ከአበው አንዱ “በአቤል አፍርሆሙ ወበሄኖክ አንቅሆሙ ማለትም በአቤል መሞት አስደነገጣቸው ወይም አስፈራቸው፤ በሄኖክ አለመሞት ደግሞ አነቃቃቸው ” ሲል ተናግሮአል፡፡

በይቀጥላልም እነ ኤልያስ፣ እነ ዕዝራ ሳይሞቱ እንዳሉ ወደ ሕያዋን ዓለም ሲወሰዱ፣ እንደዚሁም እግዚአብሔር ለአርእስተ አበው የገባው ዘለዓለማዊና የሕይወት ቃል ኪዳን ጥልቅና እስከ ወዲያኛው ዓለም ድረስ የሚዘልቅ መሆኑን ግልጽ እየሆነ ሲመጣ፣ ከዚህም ጋር ነቢዩ ኤልያስ አንድ ምዉትን ሲያስነሣ፣ የእርሱ ደቀ መዝሙር የነበረ ኤልሳዕም በአጥንቱ ንክኪነት ሳይቀር ሁለት ሙታንን ሲያስነሣ፣ ነቢዩ ዳንኤልም “በምድር ትቢያ ውስጥ ካንቀላፉት ብዙዎቹ ይነቃሉ” ብሎ ሲናገር የትንሣኤ ሙታን ነገር ያለቀና የደቀቀ መሆኑ ታወቀ፤ ነቢዩ ኢሳይያስም “ሙታን ይትነሥኡ ወየሐይዉ እለ ውስተ መቃብር፤ ሙታን ይነሣሉ በመቃብር ያሉትም ይድናሉ በሕይወትም ይኖራሉ” ሲል የሙታን ትንሣኤን አይቀሬነት አስረድቶአል፡፡ ከሁሉ በላይ ደግሞ እግዚአብሔር ወልድ ሥጋችንን ለብሶ በዚህ ዓለም በተገለጠ ጊዜ ወልደ መበለትን፣ ወለተ ኢያኢሮስን፣ አልዓዛርን፣ አምስት መቶ ቢጽን ከሞት ከማስነሣቱም ሌላ ስለ ትንሣኤ ሙታን በሰፊው ማስተማሩን፣ ከዚህም ሌላ በትንሣኤ ሙታን እምነት ያልነበራቸው ሰዱቃውያን የተባሉ የአይሁድ ክፍሎች ስለ ትንሣኤ ሙታን ጉዳይ መስቀለኛ ጥያቄን ባቀረቡለት ጊዜ የእግዚአብሔር ኀይልና የቅዱሳት መጻሕፍትን ቃል ባለማወቅ ስሕተት ላይ መውደቃቸውን ገልጾ ሙታን እንደሚነሡ፣ ሰማያዊ ሕይወታቸውም እንደ መላእክት እንደሚሆን አስረግጦ ነግሮአቸዋል፡፡ በዚህ ሁሉ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን ነገረ ትንሣኤ ሙታንን በማያወላውልና በማያሻማ ሁኔታ ለዓለም በቊርጥ ተናግሮአል፡፡

የተወደዳችሁ ልጆቻችን ሕዝበ ክርስቲያን፤

በየዓመቱ በጾም፣ በጸሎት፣ በአምልኮተ እግዚአብሔር፣ በቅዳሴ፣ በውዳሴና፣ ቅዱስ ቊርባንን በመቀበል የምናከብረው የቅድስት ድንግል ማርያም በዓለ ፍልሰታ ወይም በዓለ ትንሣኤ ከዚህ በላይ ከተገለጸው ነገረ ትንሣኤ ጋር በቀጥታ የተያያዘ ነው፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም በዚህ ዓለም ለስድሳ አራት ዓመታት ያህል በሕይወተ ሥጋ ከቆየች በኋላ ጥር ሃያ አንድ ቀን ጽርሐ ጽዮን ውስጥ በሚገኘው በባለ አደራው በዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ ቤት ዐርፋለች፡፡ የቅድስት ድንግል ማርያም ነፍስ በእደ እግዚአብሔር ፣ በይባቤ መላእክት፣ ወደ ብርሃናዊውና ሰማያዊው ዓለም ስትወሰድ፣ ሥጋዋ ደግሞ ጌቴሴማኒ ውስጥ በሚገኘው በወላጆቿ መቃብር ለማሳረፍ ቅዱሳን ሐዋርያት ሥጋዋን ተሸክመው ጒዞ ጀመሩ፡፡ ነገር ግን የክርስትናውን እምነትና አስተምህሮ ያልተዋጠላቸው የአይሁድ ወገኖች ሥርዐተ ቀብሯ በሰላም እንዳይፈጸም ከመዶለታቸውም ሌላ ቅዱስ የሆነው ሥጋዋን ከሐዋርያት እጅ ለመንጠቅና ለመውሰድ ሞከሩ፡፡

ይህንን ሙከራ ያደረገ ታውፋንያ የሚባል ሰው ነበረና መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እሱን ቀጥቶ ቅዱሱን የእመቤታችን ሥጋን ከባለ አደራው ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር ነጥቆ ወደ ገነት ወሰደው፤ በዚህ ሁኔታ የቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ በዚያ እንዲቀመጥ ሆነ፤ ቅዱስ ዮሐንስ ግን ወደ ወንድሞቹ ወደ ሐዋርያት ተመልሶ የድንግል ማርያምን ቅዱስ ሥጋ በገነት ውስጥ በዕፀ ሕይወት ሥር መቀመጡን ለሐዋርያት ነገረ፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ወኵሎ ዘሰአልክሙ በስምየ ይትገበር ለክሙ፤ በስሜ የምትለምኑት ሁሉ ይደረግላቸኋል” ብሎ የገባላቸውን ቃል ኪዳን በመከተል የቅድስት ድንግል ማርያም አስከሬን ያለበትን ቦታ ማየትና ቅዱሱ ሥጋዋን መሳለም እንዲችሉ ከነሐሴ አንድ ቀን ጀምሮ እስከ ነሐሴ ዐሥራ አራት በጾምና በጸሎት ሱባዔ ገብተው እግዚአብሔርን ደጅ ጸኑ፡፡ጌታችንም እንደ ቃሉ ጸሎታቸውንና ጾማቸውን ተቀብሎ ነሐሴ ዐሥራ አራት ቀን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥጋን አምጥቶ ሰጣቸው፤ እነሱም ሥጋዋን ተቀብለው በታላቅ ክብር በጌቴሴማኒ ውስጥ በወላጆችዋ ርስት ቀበሩአት፡፡

ከዚህ በኋላ የእመቤታችን ሥጋን በተቀበረ በሦስተኛው ቀን ነሐሴ ዐሥራ ስድስት ቀን ጌታችን ነፍሷን ከሥጋዋ ጋር አዋሕዶ በማስነሣት ወደ ብርሃናዊው ዓለም ወደ መንግሥተ ሰማያት አሳርጎአታል፡፡ በዕርገቷ ጊዜ በሕንድ ሀገር ቅዱስ ወንጌልን እያስተማረ የነበረው ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ በደመና ሰማይ ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲጓዝ፣ እመቤታችን በሰማያውያን ሠራዊት ታጅባ በመላእክት ዝማሬና በቅዱሳን ይባቤ ስታርግ አገኛት፡፡ቅዱስ ቶማስ ከነበረው የድንግል ማርያም ጽኑ ፍቅር የተነሣ በቁጭት በትንሣኤሽ ቀን ሳልገኝ ቀረሁን! ብሎ ሲያዝን፣ አይዞህ ወዳጄ ቶማስ ወንድሞችህ ሐዋርያትም በክብር ገንዘው ቀበሩኝ እንጂ ትንሣኤዬን አላዩም፤ አንተ ብቻ ነህ ትንሣኤዬን ያየህ፤ ስለዚህ እኔን የገነዙበት ሰበን (መጐናጸፊያ) ለሁላችሁም ለበረከት እንዲሆናችሁ ይኸው ሰጥቻችኋለሁ ብላ በመስጠትና በማጽናናት ትንሣኤዋን ለሐዋርያት እንዲያበሥር ነግራው ዐረገች፡፡ ቅዱስ ቶማስም የተሰጠውን ሰበን ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም በመሄድ ከሐዋርያት ጋር ተገናኘ፤ ሐዋርያትም በበኩላቸው ጌታ የእመቤታችንን ሥጋዋን እንደሰጣቸውና በክብር ገንዘው እንደቀበሯት ነገሩት፤ ቅዱስ ቶማስ ግን በያዘው ሰበን ትንሣኤዋን ለመግለጽ ስለፈለገ “ሞት በጥር፣ በነሐሴ መቃብር እንዴት ይሆናል?” ብሎ ተከራከራቸው፤ ቅዱስ ጴጥሮስ ግን ነገሩ እውነት እንደሆነ ለመግለጽና እርሱን ለማሳመን ሲል መቃብሯን ቈፈረ፤ ሆኖም ሥጋዋን አላገኘም፤ ቅዱስ ጴጥሮስና ሐዋርያት በሁኔታው ደነገጡ፤ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ እኔ ብቻ ከምነግራችሁ እናንተም ራሳችሁ አይታችሁ እንድታምኑ ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንማ ተነሥታ አርጋለች፤ እርሷን የገነዛችሁበት ሰበንም ለወንድሞቼ ለሐዋርያት ለበረከት እንዲሆናቸው ስጣቸው ብላኝ ይኸው ይዤ መጥቻለሁ ብሎ አሳያቸው፤ እነሱም ነገረ ትንሣኤዋን በመስማታቸው እግዚአብሔርን እያመሰገኑ የተገነዘችበትን ሰበን ተካፈሉት፡፡

ዛሬ በምሥራቃውያን አብያተ ክርስቲያናትና በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ከመስቀል ጋር የሚያዘው ሰበን የእመቤታችን ትንሣኤ መታሰቢያ እንደሆነ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያስረዳል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ለቶማስ የተገለጸውን ነገረ ትንሣኤዋ ለእነርሱም እንዲገለጸላቸው በመሻት በድጋሚ በዓመቱ ከነሐሴ አንድ ቀን ጀምረው ጾምና ጸሎት ያዙ ሱባዔም ገቡ፤ አሁንም ጌታችን ጸሎታቸውንና ጾማቸውን ተቀብሎ ነሐሴ ዐሥራ አምስት ቀን ሐዋርያትን ከያሉበት ሀገረ ሰብከት በደመና ሰማይ ሰበሰባቸው፤ በበነጋው ነሐሴ ዐሥራ ስድስት ቀን ጌታችን እመቤታችንን፣ ቅዱሳን መላእክትን፣ ከአዳም ጀምሮ እስከዚያው ያሉትን ቅዱሳን ሁሉ አስከትሎ ተገለጠላቸው፣ ጸሎተ ቅዳሴን አድርሶ ቅዱስ ቊርባንን አቀበላቸው፤ በዚህ ሁኔታ ትንሣኤዋን ከገለጸላቸው በኋላ ይህንን ትንሣኤዋን እንዲያስተምሩ አዘዛቸው፤ ለእርሷም ሐዋርያት ለፍቅሯ ሲሉ በጾሙት በጾመ ፍልሰታ ጾምን የጾመ፣ ቅዱስ ቊርባንን የተቀበለ፣ የተራበውን ያበላ፣ የተጠማውን ያጠጣ፣ የታረዘውን ያለበሰ እምርልሻለሁ ብሎ ቃል ኪዳን በመግባት በመጣበት አኳኋን ወደ ሰማያት አርጓል፡፡

ጌታችንም ሆነ ሐዋርያት የሠሩትን ተኣምራትና ምግባር ትሩፋት እንደዚሁም ያስተማሩትን ትምህርት ሙሉ በሙሉ በጽሑፍ እንዳልሰፈረ በቅዱስ መጽሐፍ የተረጋገጠና በዮሐ ፳፩÷፳5 ተጽፎ የምናገኘው ሐቅ ነው፡፡ በመሆኑም ቅዱሳን ሐዋርያት በመልእክታቸው ውስጥ በጽሑፍ የሰፈረውን ብቻ ሳይሆን በትውፊትና በቃላቸው ያስተላለፉትንም ጭምር አጥብቀን እንድንይዝ “ወንድሞች ሆይ ጸንታችሁ ቁሙ በቃላችንም ቢሆን ወይም በመልእክታችን የተማራችሁትን ሁሉ ወግ (ትምህርት) ያዙ” ብለው አስተምረውናል፤( ፪ ተሰ ፪.፲5) ቅዱሳን ሐዋርያት በቃል ካስተማሩት ውስጥ አንዱ ፍልሰታ እያልን የምንጠራው የቅድስት ድንግል ማርያም ነገረ ትንሣኤ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከዕርገተ ክርስቶስ በኋላ በአንደኛው ዓመት፣ ከልደተ ክርስቶስ ደግሞ በሠላሳ አራተኛው ዓመት ማለትም ሁሉም ሐዋርያት በሕይወተ ሥጋ እያሉ የክርስትና ሃይማኖትን የተቀበለች በመሆኗ ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን ትባላለች፤ ይህም ማለት በትውፊትም ሆነ በቃላዊ ትምህርት ከተላለፈው ከሐዋርያት አስተምህሮ ያመለጣት ምንም ነገር እንደሌለ ያመለክታል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ከጥንት ጀምሮ የቅድስት ድንግል ማርያምን ሱባዔና በዓለ ትንሣኤ በከፍተኛ ሁኔታ እያከበረች ትምህርቱንም እምነቱንም ሥርዐቱንም በምልአት ይዛ መገኘቷ የዚሁ እውነት ማረጋገጫ ነው፡፡ ለነገሩ እኛ ብቻ ሳንሆን ሌሎቹ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናትም ማለትም ከደኃራውያኑ በቀር ጥንታውያኑ ሁሉ የምዕራቡም ሆኑ የምሥራቁ ክፍለ ዓለም አብያተ ክርስቲያናት የድንግል ማርያምን ትንሣኤ እንደኛ ያምናሉ ያስተምራሉ ጾሙንም ይጾማሉ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ግን ከሁሉም ይልቅ የሐዋርያት ትውፊትና ትምህርት፣ የቅድስት ድንግል ማርያም ፍቅር በኢትዮጵያ አርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በእጅጉ እንደሚያይል ለማንም ግልጽ ነው፤ ይህም የቤተ ክርስቲያናችንና የምእመናኖቻችን ሃይማኖት ምን ያህል በጸጋ እግዚአብሔር የተሞላ መሆኑን ያሳያል፡፡

የተወደዳችሁ ሕዝበ ክርስቲያን ልጆቻችን፤

የሙታን ትንሣኤ በቅድስት ድንግል ማርያም ብቻ የሚያቆም ሳይሆን በፊታችን ቆሞ ሁላችንንም እየጠበቀ የሚገኝ ድንቅ የእግዚአብሔር ግብዣ ነውና በእርስዋ ትንሣኤ ልክ እንድንነሣ ከሐዋርያት የወረስነውን ትምህርትና ትውፊት እንደ ቅዱሳን አባቶቻችን አጥብቀን በመያዝ እርሱን በማመንና በመጠባበቅ ለተጠራንለት የትንሣኤ ዘጉባኤ አምላካዊ ግብዣ በሚገባ ልንዘጋጅ ይገባል፤ ለዚህም እግዚአብሔር በቸርነቱ ይርዳን፤ ቅድስት ድንግል ማርያምም በጸሎቷና በአማላጅነቷ አትለየን፡፡ በድጋሚ እንኳን ለበዓለ ፍልሰታ ለማርያም በሰላም አደረሳችሁ፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32017-08-22 13:26:112025-01-28 13:27:24ነሐሴ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ በዓለ ዕርገት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ነሐሴ 1 ቀን 2009 ዓ.ም. የጾመ ፍልሰታ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ነሐሴ 1 ቀን 2009 ዓ.ም. የጾመ ፍልሰታ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ነሐሴ 1 ቀን 2009 ዓ.ም. የጾመ ፍልሰታ ቃለ ምዕዳንና... Link to: መስከረም 1 ቀን 2010 ዓ.ም. የዘመን መለወጫ በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: መስከረም 1 ቀን 2010 ዓ.ም. የዘመን መለወጫ በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ መስከረም 1 ቀን 2010 ዓ.ም. የዘመን መለወጫ በዓል ቃለ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top