• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ነሐሴ 1 ቀን 2009 ዓ.ም. የጾመ ፍልሰታ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
በሀገር ውስጥና በተለያዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፤

እኛን ለክብርና ለምስጋና የፈጠረ እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት የጾመ ማርያም ሱባዔ በሰላም አደረሳችሁ።

“ታዓብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር
ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች፤ ”
(ሉቃ. 1÷47)

ይህንን የምስጋና ቃል የተናገረችው ወላዲተ እግዚአብሔር ቃልና ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፤ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ይህንን የአምልኮ ምስጋና ለእግዚአብሔር ስታቀርብ እርሱ ያደረገላትን ሦስት ዐበይት ምክንያቶች በመጥቀስ እንደሆነ ከቅዱስ መጽሐፍ እናስተውላለን፡፡ እመቤታችን ይህንን ምስጋና ከማቅረቧ በፊት እግዚአብሔር ለታላቅ በረከትና ለፍጹም ደስታ እንደመረጣት፣ የእርሱ ባለሟልና ምልእተ ጸጋ እንዳደረጋት፣ ቅዱሱን የእግዚአብሔር ልጅ በመንፈስ ቅዱስ ፀንሳ እንደምትወልድና እግዚአብሔር ከእርሷ ጋር እንደሆነ በመልእክተኛ በቅዱስ ገብርኤል በኩል ነግሮአታል፡፡

እርሷም በቅዱስ ገብርኤል በኩል የተላከላትን የእግዚአብሔር ቃል ተቀብላ እነሆ የእግዚአብሔር ባሪያ ነኝ እንዳልከኝ ይሁንልኝ በማለት በታዛዥነትና በትሕትና ለደረሳት መለኮታዊ ጥሪ ተገቢውን የይሁንታ መልስ ሰጥታለች፡፡ በዚህ ጊዜ ቀዳማዊ ወልደ እግዚአብሔር በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍስዋ ነፍስን ነሥቶ ራሱን በማዋሐድ የዕለት ፅንስ ሆኖ በማሕፀንዋ አደረ፡፡ ጌታችን አምላካዊ ማንነቱን መግለጽ የጀመረው ከማሕፀን አንሥቶ ነውና እመቤታችን እሱን ፀንሳ ሳለች ኤልሳቤጥን እንዴት ነሽ ብላ የሰላምታ ድምፅን ስታሰማት በማሕፀነ ኤልሳቤጥ ያለው ፅንስ በማሕፀነ ማርያም ላለው ፅንስ በደስታ ሰግዶአል፡፡ ይህ አምላካዊ ምሥጢር በድንግል ማርያም ማሕፀን ውስጥ ያለው ፅንስ የአምልኮ ስግደት የሚገባውና ሁሉን የፈጠረ፣ ሁሉንም ማድረግ የሚችል የባሕርይ አምላክ መሆኑን አሳይቶአል፡፡ ይህ ብቻም አይደለም የቅድስት ድንግል ማርያም የሰላምታ ድምፅ በኤልሳቤጥ ጆሮ በተሰማ ጊዜ በማሕፀንዋ ያለ ፅንስ በደስታ ሲሰግድ፣ በዚያ ቅጽበት ኤልሳቤጥ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልታ እግዚአብሔር በቅዱስ ገብርኤል በኩል የገለጸውን የእመቤታችን ክብርና ጸጋ፣ በረከትና ብፅዕና፣ የጌታ እናትነትና ባለሟልነት፣ የልጇ በረከትና አምላክነት በኤልሳቤጥ አንደበትም በድጋሚ እንዲነገር ማድረጉ የነገሩ ክብደትና ታላቅነት ምን ያህል እንደሆነ እንዲታወቅ አስችሎአል፡፡

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በቅዱስ ገብርኤልና በቅድስት ኤልሳቤጥ በኩል ስለ እርስዋ መናገሩና የእግዚአብሔር ወልድ በማሕፀኗ ማደሩ በዚህ ሁሉ እጅግ በጣምከኀይል ሁሉ የበለጠ ታላቅ ኀይል በእርስዋ ላይ እንደተደረገ እመቤታችን በሚገባ አውቃለች፡፡ ይህ እጅግ በጣም ታላቅ የሆነ ጸጋ ለሰው ልጅ ሁሉ የሚተርፍ ልዩ በረከትና የእግዚአብሔር የማዳን ቁልፍ ተግባር እንደሆነ ለማመልከትም ካንቺ የሚወለደው ሕዝቡን ከኀጢአታቸው የሚያድናቸው ስለሆነ ስሙ ኢየሱስ ትይዋለሽ ተብሎ በመልአኩ ተነግሮአታል፤ እርስዋም አምና ተቀብላለች፤ ለዚህ ታላቅ በረከትና መዳን በመሣሪያነት እርሷ መመረጥዋንም ልዩ ዕድል መሆኑን አልዘነጋችም፡፡ እንግዲህ እነዚህ ዐበይት ነገሮች በእመቤታችን አእምሮ ውሰጥ ከፍተኛ ስፍራ ነበራቸውና ያለምስጋና ልታልፋቸው አልፈለገችም፡፡ በመሆኑም የሆነው ነገር በሙሉ ለእርስዋና ለሰው ልጆች ሁሉ መሆኑን በሚገልጽ ኀይለ ቃል የአምልኮ ምስጋናዋን ለፈጣሪዋ ለእግዚአብሔር ግሩም በሆነ ሁኔታ አቅርባለች፡፡ በምስጋናዋም “ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች፤ መንፈሴም በአምላኬና በመድኀኒቴ ደስ ይላታል፤ የባርያይቱን ውርደት አይቶአልና፤ እነሆ ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ነሽ ይሉኛል፤ እርሱ ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልኛልና” የሚል ጥልቅ ምሥጢር ያለው ኀይለ ቃል ይገኝበታል፡፡ ይኸውም “ብዙኃ አበዝኆ ለሕማምኪ ወለፃዕርኪ፤ በሕማም ለዲ፤ ምጥሽን ጣርሽን እጅግ አበዛዋለሁ፤ በጭንቅም ትወልጂያለሽ የሚል መርገም ተሸክማ በመከራ የኖረችውና ይህንን መከራ ለልጆችዋ ያወረሰችው ሔዋን በእርስዋ ጊዜና መሣሪያነት ከመርገም ተላቃ ወደ ገነት የምትመለስበት ጊዜ እየተቃረበ መምጣቱን ስታመለክት የባርያይቱን ውርደት ተመልክቶአልና ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች በማለት አመሰገነች፡፡

የሰው ልጅን በአጠቃላይ ከገጠመው ውድቀት ለመታደግ እግዚአብሔር በጀመረው ነገረ አድኅኖ ከኀይል ሁሉ የበለጠ ኀይል እግዚአብሔር ወልድ በማሕፀኗ ማደሩ፣ እንደዚህም እርስዋ ለዚህ የበቃች ቅድስት፣ ንጽሕት፣ ቡርክት፣ ልዕልት፣ ብፅዕትና ከሴቶች ሁሉ የተለየች ምልእተ ጸጋ፣ ሙኃዘ ፍሥሐ፣ የእግዚአብሔር ልዩ ባለሟልና የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ አድርጎ መምረጡንና ማክበሩን ሁሉ ለእርስዋ የተደረጉ ታላላቅ ነገሮች መሆናቸውን በመገንዘብዋ እመቤታችን ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልኛልና መንፈሴ በአምላኬና በመድኀኒቴ ደስ ይላታል በማለት ፈጣሪዋን አመስግናለች፡፡ ከዚህም አይይዛ በእግዚአብሔር መልእክተኛ በቅዱስ ገብርኤልና መንፈስ ቅዱስ በሞላባት በቅድስት ኤልሳቤጥ የተገለጸውን ቅድስናዋና ብፅዕናዋ ዘመንና የስሑታን ትምህርት ሳይገቱት ከትውልድ ወደ ትውልድ ሳይቋረጥ እንደ ወራጅ ውኃ እስከ ዕለተ ምጽአት እንደሚነገርና እንደሚተገበር በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝታ ተናግራለች፤ ቤተ ክርስቲያናችንም የእመቤታችንን ብፅዕና አክባሪና ከአማላጅነቷ ተጠቀሚ ሆና መገኝቷ የእግዚአብሔርን ፈቃድ በደምብ ያወቀችና ቃሉን በምልአት የተቀበለች መሆኗን ያረጋግጣል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤ ከቅድስት ድንግል ማርያም የምስጋና ቃል የምንማረው ብዙ ትምህርት እንዳለ ማስተዋልና መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

ከሁሉ በፊት ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም የተነገሩ ነገሮች በሙሉ ከፍጡራን መንጭተው የተነገሩ ሳይሆኑ ከእግዚአብሔር በቀጥታ ከተላከው መልአክ ከቅዱስ ገብርኤል፣ መንፈስ ቅዱስ ከሞላባት ከቅድስት ኤልሳቤጥና እንደዚሁም መንፈስ ቅዱስ ባንቺ ላይ ይመጣል ከተባለላት ከቅድስት ድንግል ማርያም የተነገሩ በመሆናቸው ምንጫቸውና ተናጋሪያቸው ራሱ እግዚአብሔር እንደሆነ መገንዘቡ አያዳግትም፤ ምክንያቱም ተላኪ የላኪውን፣ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት የመንፈስ ቅዱስን ቃል እንደሚናገር ለሁሉም ግልጽ ነውና፤ ቅዱስ መጽሐፍም እነዚህን በጥንቃቄ መዝግቦ መገኘቱ ይህንን እንድንገነዘበው ብሎ እንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ ከዚህ አንጻር እግዚአብሔር ራሱ በፍጹም ክብር ያከበራትንና ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ነሽ እያሉ እንዲያመሰግኗት በቅዱስ መንፈሱ ያናገረላትን ቅድስት ድንግል ማርያምን ማክበርና ማመስገን፣ብፅዕናዋንና ቅድስናዋን ማመን፣ መስበክና ማሰተማር የእግዚአብሔርን ቃል በትክክል ተረድቶ ለቃሉ መታዘዝና ለተግባራዊነቱ መቆም እንደሆነ ለሕዝበ ክርስቲያን ሁሉ ግልጽ ሊሆንለት ይገባል፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ላደረገላት ታላቅ ነገር ሁሉ ምስጋናን አምልኮትንና ምስክርነትን በመስጠት ለእኛ መልካም አስተማሪና አርኣያ መሆኗን ማስተዋል ከሁላችንም ይጠበቃል፡፡ ሁላችንም ልብ ብለን ካየነው እግዚአብሔር ለሰው ልጅ በአጠቃላይ ታላላቅ ሥራዎችን ያልሠራበት ቀን አይገኝም፤ ነገር ግን በየጊዜው ለሠራልን ሥራዎች ተገቢ ዕውቅና በመስጠትና በመመስከር እንደ ቅድስት ድንግል ማርያም በደስታ የአምልኮ ምስጋናን ለእግዚአብሔር የሚያቀርቡ ስንት ናቸው? የሚለውን ጥያቄ ብናነሣ መልሱ አስቸጋሪ ሳይሆን አይቀርም፤ ነገር ግን ድሮም እኛ የተፈጠርነው ለምስጋና ነውና እግዚአብሔር ያለሟቋረጥ ሁሌም ታላላቅ ነገሮችን እየሠራልን እንደሆነ ዐውቀንና አምነን ለእርሱ የሚገባ የአምልኮ ምስጋና ልናቀርብ ይገባል፡፡

ከዘመነ ሐዋርያት ጀምሮ በቀኖና ጸድቆ በጥንታውያንና በኦርቶዶክሳውያን አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ እየተፈጸመ የሚገኘው የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ ዐላማም፣ እግዚአብሔርን በምስጋና በቅዳሴ በውዳሴ ለማምለክ፣ ለቅዱስ ቃሉ ፍጹም ታዛዥ በመሆን ምሥጢረ ቊርባንን ለመቀበልና ከኀጢአት ሸክም ተላቀን ከእግዚብሔር ጋር የጠበቀ ግንኙነት ለመፍጠር ነው፡፡

በዘመነ ብሉይም ሆነ በዘመነ ሐዲስ የእግዚአብሔር ሞገስና ጸጋ አግኝተው ለቅድስና ደረጃ የበቁ ቅዱሳን ሁሉ ጸሎታቸውና፣ ተማሕፅኖአቸው ለራሳቸው ብቻ ሳይሆን ለዓለሙ ሁሉ እንደሚተርፍ ቅዱስ መጽሐፍ በትምህርትም ሆነ በተግባር ያረጋገጠውና የመዘገበው ነው፡፡ ይልቁንም “እስመ ረከብኪ ሞገሰ በኀበ እግዚአብሔር ከእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን አግኝተሻልና ምልእተ ጸጋ ነሽ፤ደስ ይበልሽ ብሎ እግዚአብሔር በመልእክተኛው ያረጋገጠላት ቅድስት ድንግል ማርያም ባላት ከፍተኛ የእግዚአብሔር ባለሟልነት በጸሎቷ በአማላጅነቷና ወደ እግዚአብሔር በምታቀርበው ተማሕፅኖ ግዳጃችንን እንደምትፈጽም የቃና ዘገሊላው ምልጃዋና የተገኘው በረከት በቂ ማስረጃችን ነው፡፡

በመሆኑም የጾመ ፍልሰታ ሱባዔ እግዚአብሔርን በአባትነት፣ ቅድስት ድንግል ማርያምን በእናትነት የምናገኝበት ልዩ ወቅት በመሆኑ እግዚአብሔር በቃሉ የተናገረውን በመከተልና እንደ ቃሉ በመመላለስ ጾሙን ልንጾም ይገባል፡፡ ከሁሉ በላይ ደግሞ ፍቅርና ሰላም፣ መተጋገዝና መረዳዳት፣ ንስሓ መግባት፥ ጸሎት መጸለይ፣ ቅዱስ ቊርባንን መቀበል፥ ሰውን ማክበር የእግዚአብሔርን ቃል በማዳመጥና በመከተል መጾም ይኖርብናል፡፡ ይህ ጾም የሀገራችንን አንድነትና ነፃነት፣ የሕዝባችንን አብሮነትና የእርስ በርስ መተሳሰብ፣ እግዚአብሔርን የመፍራትና ድንግል ማርያምን የመውደድ፣ ሃይማኖታዊና ኢትዮጵያዊ ዕሴቶችን ሁሉ አዳብሮ ጥሩ ሰብእና ያለው ማኅበረ ሰብን ያፈራ፣ እንደ አሸንዳ የመሳሰሉ ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ባህሎችን የገነባ ጾም ስለሆነ፣ ለሃይማኖታችን መጠበቅ፣ ለሀገራችን መልካም ገጽታ ግንባታና ለልማት መፋጠን እንደዚሁም ለቱሪዝም ክፍለ አኮኖሚ መበልፀግ የሚሰጠው ጥቅም ከፍተኛ ስለሆነ ሃይማኖታዊ፣ ባህላዊና ሀገራዊ ይዘቱ ተጠብቆ እንዲቀጥል ኢትዮጵያዊ የሆነ ሁሉ የበኩሉን ሊወጣ ይገባል፡፡

በመጨረሻም፡ የጾም ወቅት ምእመናን ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙበት፣ ርኅራኄና አዘኔታ ለሰው ልጅ ሁሉ የሚያደርጉበት እንደመሆኑ መጠን፣ ምእመናን እጆቻቸውን ለተቸገሩ ወገኖች እንዲዘረጉ፣ ስለ ሀገርና ስለ ዓለም ሁሉ ሰላም መጠበቅ ወደ እግዚአብሔር ጸሎት እንዲያቀርቡ፣ በሀገራችን እየተካሄደ ያለው ዙሪያ መለስ የልማትና የእድገት ሽግግር እንዲሰምር በፍቅርና በሰላም ቆመው በአንድነት ጸሎታቸውን ሁሉን ወደሚችል ወደ ኀያሉ እግዚአብሔር ለማቅረብ እንዲተጉ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናሰተላልፋለን፡ ወትረ ድንግል ማርያም፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡ 

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32017-08-07 13:24:402025-01-28 13:25:44ነሐሴ 1 ቀን 2009 ዓ.ም. የጾመ ፍልሰታ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ሐምሌ 9 ቀን 2009 ዓ.ም የኤጲስ ቆጶሳት ሥርዐተ ሢመት በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በታላቅ ክብርና ሥነ ሥርዐት ተፈጽሟል፡፡ Link to: ሐምሌ 9 ቀን 2009 ዓ.ም የኤጲስ ቆጶሳት ሥርዐተ ሢመት በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በታላቅ ክብርና ሥነ ሥርዐት ተፈጽሟል፡፡ ሐምሌ 9 ቀን 2009 ዓ.ም የኤጲስ ቆጶሳት ሥርዐተ ሢመት... Link to: ነሐሴ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ በዓለ ዕርገት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ነሐሴ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ በዓለ ዕርገት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ነሐሴ 16 ቀን 2009 ዓ.ም. የእመቤታችን ቅድስት ድንግል...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top