• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ጥር 11 ቀን 2011 ዓ.ም. በጥምቀት በዓል በጃንሜዳ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ፤

ሥጋችንና ነፍሳችንን ከቃሉ ጋር በውኃ መታጠብ ያነፃን የጌታችን የአምላካችንና የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አባት እግዚአብሔር እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ አንድ ዓመተ ምሕረት በዓለ ጥምቀት በሰላም አደረሳችሁ!!

“ወውእቱ ያጠምቀክሙ በመንፈስ ቅዱስ ወበእሳት
እርሱ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፤”
(ሉቃ. 3፥16)

ጥምቀት ማለት የተለያየና ሰፋ ያለ ትርጒም ቢኖረውም ምሥጢራዊ ትርጒሙን ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው መንጻት፣ መተባበር፣ መለወጥ፣ መሻገር፣ አዲስ ሕይወት፣ አዲስ ልደት፣ አዲስ ፍጥረት፤ የሚሉት መሠረተ ሐሳቦችን ያመሠጥራል፡፡

የጥምቀት ጥንተ ታሪክ ስንመለከት ከሊቀ ነቢያት ሙሴ ጀምሮ ይነሣል፤ በዘመነ ብሉይ ሰውን ጨምሮ ልዩ ልዩ ነገሮችን ለማንጻት ማጠብና ማጥመቅ የተለመደ ሃይማኖታዊ ተግባር ነበረ፤ ከዚያ ተያይዞ በወረደው ሥርዐትና ትውፊት መሠረት ነቢያትና ካህናት በየዘመናቸው ያጠምቁ ነበረ፤ በክፉ ደዌ ተይዞ ይሰቃይ የነበረ ጻድቁ ኢዮብ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ ከጽኑ ደዌው ድኖአል፤ ሶርያዊው ንዕማንም በነቢዩ በኤልሳዕ ትእዛዝ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ ከለምጽ በሽታው ተፈውሶአል፤ ደቂቀ እስራኤልም የኤርትራን ባሕርና የዮርዳኖስን ወንዝ መሻገራቸው ጥምቀት ተብሎ ተጽፎአል፤ በተለይም ታቦተ እግዚአብሔርን ተሸክመው ይጓዙ የነበሩ ካህናት እግሮቻቸው የዮርዳኖስ ወንዝ ውኃን ሲነኩና ውኃው ሲቆም የሆነው ክሥተት ጥምቀት ተብሎአል፤ ይህ ዐይነቱ የጥምቀት ሁኔታ በየጊዜው እየተፈጸመ እስከ ዘመነ ዮሐንስ መጥምቅ ደርሶአል፡፡ ከጥምቀተ ክርስቶስ በፊት የነበሩት ጥምቀታት በክርስቶስ ለሚሰጠው እውነተኛ ጥምቀት እንደ ምሳሌ እንደ ጥላና እንደ አመልካች ቀስት የሚያገለግሉ ማዘጋጃ ነበሩ እንጂ ስርየተ ኀጢአትን፣ ሀብተ ንጽሕን፣ ሀብተ ልደትን፣ አዲስ ሕይወትን የሚያጎናጽፉ አልነበሩም፤ የሚከናወኑትም በውኃ ብቻ ነበረ እንጂ በመንፈስ ቅዱስ ጭምር አልነበረም፤ ለዚህም ነው መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ እኔ ለንስሓ የሚሆን የማዘጋጃ ጥምቀት አጠምቃለሁ፤ ከኔ በፊት የነበረው፣ ከኔ የሚበረታው፣ ከኔ በኋላ የሚመጣው ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በውኃ ብቻ ሳይሆን በውኃ፣ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል በማለት የመሰከረው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ የማጥመቅ ሥራን ያከናውን የነበረው እንዲሁ በድንገትና ያለአስተምህሮ አልነበረም “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ “የሚለውን የኃጥአን ዋና ተስፋ ዐቢይ ርእስ አድርጎ በመጠቀም የንስሓን ጠቃሚነትና የኀጢአትን ጎጂነት በስንዴና በገለባው እየመሰለ አጒልቶ ያስተምር ነበር፤ በሰዎች መካከል የበላይና የበታች ሳይኖር ሁሉም በእኩልነትና በኅብረት በተስተካከለ ህላዌ ይኖሩ ዘንድ “ ተራራውና ኮረብታው ዝቅ ይበል፤ ጐድጓዳው ይሙላ” እያለ ደጋግሞ አስተማረ፤ ክፋት ጠማማነት ተወግዶ በሰው አእምሮ ውስጥ የተስተካከለና ቅን አስተሳሰብ ሰፍኖ ይኖር ዘንድ ጠማማውና ጠመዝማዛው፣ ሸካራውና ጐባጣው መንገድ ሁሉ ተስተካክሎ ቀጥ ይበል ብሎ አሰምቶ ተናገረ፤ እነዚህ ድርጊቶች ንስሓን ገንዘብ ባደረገ ሰብኣዊ ሕይወት ውስጥ የሚታዩ ግዙፋን ፍሬዎች ናቸውና እነዚህ በሰው አፍአዊና ውሣጣዊ ሕይወት ጎምርተውና አፍርተው እንዲታዩ ቅዱስ ዮሐንስ ያለመታከት አስተማረ፤ ሰው በንስሓ ሕይወት ለመታደስ ሳይዘጋጅ ዘርን በመቁጠር የእገሌ ልጅ ነኝ እያለ በዘር የሚመካ ከሆነ በሁለመናው ወድቆ ሌሎች ቀድመውት ወደፊት እንደሚራመዱ “አብርሃም አባት አለን በማለት የምትድኑ አይምሰላችሁ” እያለ በማስተማር በዘር መመካትን ከንቱ እንደሆነ አሳይቶአል፤ ቅዱስ ዮሐንስ በማጠቃለያ ትምህርቱ “ እነሆ ምሳር በዛፎች ሥር ተቀምጦአል፤ መልካም ፍሬ የማያፈራውን ለመቊረጥ ከዚያም በእሳት ለማቃጠል “ በማለት ሥልጣነ እግዚአብሔር ኢተነሳሕያንን ለመቅጣት፣ ተነሳሕያንን ለመሸለም መዘጋጀቱን አስረግጦ አስምሮአል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ እያለ ሕዝቡን በማስተማርና በማጥመቅ ተግባር በፈለገ ዮርዳኖስ ተጠምዶ በነበረበት ጊዜ ጌታ ሊጠመቅ ወደ እርሱ መጣ፤ ቅዱስ ዮሐንስ አንተን ማጥመቅ አልችልም ቢልም በተነገረው አምላካዊ ቃልና ትእዛዝ መሠረት በዮርዳኖስ ወንዝ አጥምቆታል፤ ጌታችን በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀ ጊዜ ሦስት ዐበይት ነገሮች ተከናውነዋል፤ ይኸውም፡ ሰማያት ተከፍተዋል፣ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ወርዶ በጌታችን ላይ ተቀምጦአል፣ እግዚአብሔር አብ “የምወደው ልጄ ይህ ነው “ ብሎ የእሱን የባሕርይ አባትነት፣ የጌታችንን የባሕርይ ልጅነት ገልጾአል፡፡ ይህ መለኮታዊ አስተርእዮ በአንድ በኩል ጌታችን አምላክ ወልደ አምላክ መሆኑን ሲያረጋግጥ፣ በሌላ በኩል ሰው በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም በውኃ ሲጠመቅ በመንፈስ ቅዱስ ኀይል ከኀጢአት ነጽቶ በልጅነት ክብር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንደሚገባ ያሳያል፤ ከዚህም ጋር መንግሥተ ሰማያት ለጥሙቃን ምንጊዜም ክፍት መሆኗን እናስተውላለን፤ ቅዱስ ዮሐንስ እሱ በውኃና በመንፈስ ቅዱስ ያጠምቃል ብሎ ያስተማረው ትምህርት ምን ማለት እንደሆነም በጌታችን ጥምቀት በግልጽ ታየ፤ ታወቀ፤ ከዚህም የተነሣ ዛሬ ምእመናን በውኃና በመንፈስ ቅዱስ ይጠመቃሉ፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤

በዘመነ ዮሐንስ የነበረው የዘረኝነት ዐይነት፣ መለያየት፣ ጠማማነትና የተመሰቃቀለ ማኅበራዊ ሕይወት ሀገራችንን ጨምሮ መላ ዐለማችንን ዛሬም ክፉኛ እየናጠ እንደሆነ የማንክደው እውነታ ነው፡፡ አይሁዳውያን እኛ የአብርሃም ዘርና ልጆች ስለሆን ከሌላ የተሻልን ነን የሚል አመለካከት ሲጎዳቸው እንጂ ሲጠቅማቸው አላየንም፤እኛ ኢትዮጵያውያንም የሁላችን የጋራ ባሕርይ መጠሪያ በሆነው ስም ማለትም ሰው በሚለው የማንነታችን መገለጫ ስም ብቻ ተዋደን ተስማምተንና ተጋግዘን፣ በአንድነትና በእኩልነት በመኖር ፈንታ ኋላ በኀጢአት ምክንያት በተፈጠረው የነገድ፣ የጎሳ፣ የቋንቋ፣ የመልክዐ ምድር ወዘተ እየተለያየን ራሳችንን በራሳችን እንዳንጐዳ መጠንቀቅ ይኖርብናል፤ ለሰው ከሰው የበለጠ ሌላ ማንነት እንደሌለው ለማሳየት እግዚአብሔር ሁላችንንም ሰው ተብለን እንድንጠራ አድርጎአል፣ በዚህ ተፈጥሮኣዊ ስማችንም አንድ አድርጎ እንደ አዳነን ቅዱስ መጽሐፍ ዋቢአችን ነው፤ እኛም ምን ዐይነት ፍጡር እንደሆን ብንጠየቅ መልሳችን ሰው የሚል እንጂ ሌላ መልስ ሊኖረን አይችልም፤ ታድያ ይህን እውነታ ጨፍልቀን በቋንቋ፣ በነገድ፣ በጎሳ፣ እየተለያየን አንተ የዚህ ነህ፣ አንተ የዚያ ነህ፣ አንተ ውጣ፣ አንተ ቆይ የምንልበት ባህል ከየት የመጣ ነው? ነባሩ ጥንታዊውና የተከበረው ኢትዮጵያዊ ባህላችንስ ይህ ነው ወይ?ይህ ፈጽሞ መስተካከል ያለበት አስተሳሰብ ነው፤ ተራራዎቹ ሸለቆዎቹ እንደልባችን እየተንቀሳቀስን፣ አየራቸውንም እየተጐነጨን በደስታ ልንኖርባቸው፣ ወንዞቹም ውኃ ልንጠጣባቸው፣ ልማት ልናለማባቸው፣ ቋንቋዎቹ ልንግባባባቸው፣ ክልሎቹ ልንተዳደርባቸው ተፈጠሩ እንጂ፣ እኛን ሊለያዩና ሰው መሆናችንን ሊያሳጡን አልተፈጠሩም፤ በመሆኑም የማንነት መገለጫ ሰውነት ብቻ መሆኑን ተገንዝበን ሰውን በሰውነቱ ብቻ ማክበርና መቀበል ይገባናል፤ ቅዱስ ዮሐንስም በትምህርቱ ሰውን በሰውነቱ እኩል ይሁን ያለው ለዚህ ነው፡፡

በአሁኗ ሰዓት በመላ ሀገራችን እየተከበረ የሚገኘው የጥምቀት ሥነ በዓል ሰውን ሁሉ በሰውነቱ ተቀብሎ ጸጋ እግዚአብሔርን እያደለ የሚገኝ በዓል መሆኑን ልብ ብለን እናስተውል፤ በዓሉ ደማቅና ተወዳጅ የሆነውም ለዚህ ነው፤ ተለያይቶ ውበትም፣ ጒልበትም፣ ድምቀትም የለም፣ ተጣልቶም እድገት የለም፤ ስለዚህ በዛሬው ዕለት ለመላ ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን የምናስተላልፈው ዐቢይ መልእክትና አደራ ሁላችሁም በኀይለ ቃላት ውርወራ መጐናነጥን ትታችሁ፣ በወንድማዊ ፍቅር በአንድነት ተሰብስባችሁ፣ አለ የተባለውን ሁሉ በውይይትና በውይይት ብቻ ፍቱ፤ መጋጨትን፣ መንገዶች መዝጋትን፣ ሰው ማፈናቀልን፣ ማሳደድን፣ መግደልንና መዝረፍን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አቁሙ፤ በሁሉም የሀገሪቱ አቅጣጫ ያላችሁ የሃይማኖት መሪዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የማንንም ሕይወት እንዳይጠፋ አጥብቃችሁ አስተምሩ፣ምከሩ፣ አስታርቁ፤ ገሥፁ፣ የተሳሳቱትንም ወገኖች መልሱ፡፡

ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሆይ “የቈላ በሬ ጤፉን ሳይቀምሱ ጣፊያውን” እንደተባለው እንዳይሆን ሰላምን እኩልነትን፣ አንድነትን፣ ዲሞክራሲንና ልማትን እናመጣልሃለን ብላችሁ ለምትደክሙለት ሕዝብ ሳትሆኑና ከሕልማችሁ ሳትደርሱ ነገሩ ብልሽትሽት ብሎና የሕልም እንጀራ ሆኖ እንዳይቀር እባካችሁ በውይይት የማይፈታ ነገር የለምና አንድ ላይ ሆናችሁ በመወያየት የዚህን ሕዝብ የአንድነትና የሰላም ጥማቱን ፍቱለት፤

የተወደዳችሁ ወጣት ልጆቻችን፤

የዛሬ አርባ ዓመት የሆነውን ዐይነት አካሄድ በመድገም ታሪካዊ ስሕተትን እንዳትፈጽሙ ተጠንቀቁ!! የምትሹትንና የምትመኙትን ሁሉ ልታገኙ የምትችሉት አንድነትና ሰላም እስካለ ብቻ ነው፤ አርቆ በማየትና አስተውሎ በመራመድ በትዕግሥትና በመቻቻል ሳይሆን በኀይልና በጒልበት የምንፈልገውን እናገኛለን ብላችሁ የምታስቡ ከሆነ ሁሉንም ልታጡ ትችላላችሁና አስተውሉ፤ ወጣቶች ልጆቻችንና አክቲቪስቶች እስቲ እባካችሁ ሰከን በሉና ዕድሉን ለልኂቃኖቻችሁ ስጡ፤ እነርሱ የሚሏችሁን አዳምጡ፤ መደማመጥ፣ መታዘዝ፣ መከባበር፣ መቻቻል፣ ርኅራኄ፣ ቸርነት ይኑር፤ ሰው ሰው ነውና ማንንም በሰውነቱ አክብሩ፤ ይህ ነው የሰላሙና የአንድነቱ መንገድ፤ በቀል ሰላምን አይወልድም፤ ይቅርታ ግን ሀገርን በሰላም ያጥለቀልቃል፤ ምሕረተ እግዚአብሔርም ከበረከት ጋር ይከተለዋል፤ ስለዚህ ከሁሉ በፊት የሀገር አንድነት፣ የሰላም መረጋገጥ፣ የሰው ልጅ መብት መከበር ይረጋገጥ፤ ሌላው ሁሉ ከዚህ በኋላ ነው፡፡

በመጨረሻም፤ እግዚአብሔር አምላካችን በጥምቀቱ ወደ እርሱ እንደሰበሰበን ኢትዮጵያውያንን ሁሉ ወደ አንድነት አሰባስቦ በይቅርታ፣ በሰላምና በስምምነት ያኖርልን ዘንድ ከልብ እየጸለይን መልካም በዓለ ጥምቀት ይሁንልን እንላለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32019-01-19 13:45:472025-01-28 13:47:03ጥር 11 ቀን 2011 ዓ.ም. በጥምቀት በዓል በጃንሜዳ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ታኅሣሥ 29 ቀን 2011 ዓ.ም የልደት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ታኅሣሥ 29 ቀን 2011 ዓ.ም የልደት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ታኅሣሥ 29 ቀን 2011 ዓ.ም የልደት በዓል ቃለ ምዕዳንና... Link to: የካቲት 25 ቀን 2011 ዓ.ም. የዐቢይ ጾም መግቢያ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: የካቲት 25 ቀን 2011 ዓ.ም. የዐቢይ ጾም መግቢያ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ የካቲት 25 ቀን 2011 ዓ.ም. የዐቢይ ጾም መግቢያ ቃለ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top