ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ግቢ ውስጥ የተገነባውን የአብነት ትምህርት ቤት ባርከው ሥራ አስጀመሩ።
በቅዱስነታቸው ቡራኬ የተመረቀው ይህ የአብነት ትምህርት ቤት ክቡር ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም ከባለቤታቸው ክብርት ወ/ሮ ኢትዮጵያ ጥላሁን ጋር ከ133 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ አድርገው ያስገነቡት ነው።
በዚሁ የምርቃት መርሐ ግብር ከቅዱስ አባታችን በተጨማሪ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ፤ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ ሀድያና ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና ሌሎችም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተገኝተዋል።
በተጨማሪም ሊቀ ሥልጣናት ቆሞስ አባ ሲራክ አድማሱ የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አስተዳዳሪ ፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ ካህናት አባቶች ፣ በአብነት ትምህርት ቤቱ ግንባታ ላይ የተሳተፉ መሐንዲሶች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
ቅዱስነታቸው በምርቃቱ ላይ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ ሲሰጡ “ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም የአብነት ትምህርት ቤት መገንባታቸው የቅድስት ቤተክርስቲያንን መሠረት የሚያጸና ሊቃውንትን ፣ ካህናትን ሊአስገኝ የሚችል ከሁሉም የበለጠ ለቅድስት ቤተክርስቲያን የሚጠቅም በጎ ተግባር ነው” ብለዋል።
ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ኦርቶዶክሳዊያን ባለፀጋዎች ልክ እንደ ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም እግዚአብሔር ባርኮ የሰጣቸውን ሀብት ለትውልድ በሚጠቅም ዘመን ተሻጋሪ ሥራ ላይ አውለው በረከት እንዲያገኙም አባታዊ ጥሪ አቅርበዋል።
በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የተመረቀውን የአብነት ያስገነቡት ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም ባስተላለፉት መልእክት ደግሞ “በሕይወቴ የሚያስደስተኝ ቤተክርስቲያን ሲተከል የአብነት ትምህርት ቤትም አብሮ ሲሠራ ነው” ተብለዋል ።
ቢትወደድ ባሕሩ አክለውም በዚህ ታሪካዊ ካቴድራል ግቢ ውስጥ የአብነት ትምህርት ቤት ያስገነቡት “የአሁኑ ትውልድ ጥንታዊውን የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ትምህርት በተመቻቸ መልኩ እንዲማር” ስለሚፈልጉ መሆኑንም ጠቁመዋል።
ዛሬ ግንቦት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ለመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የአብነት ትምህርት ቤት ሠርተው ያስረከቡት ቢትወደድ ባሕሩ አብርሃም ከባለቤታቸው ክብርት ወ/ሮ ኢትዮጵያ ጥላሁን ጋር ከዚህን ቀደም በልዩ ልዩ የአገራችን ክፍሎች በርካታ አብያተ ክርስቲያናትንና የአብነት ትምህርት ቤቶችን ማሳነጻቸው ይታወቃል።
