• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ታኅሣሥ 29 ቀን 2014 ዓ.ም የልደት በዓልን መግባት አስመልክተው ያስተላለፉት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ሁሉ፤

እኛን ለማዳን ሥጋችንን ተዋሕዶ ፍጹም አምላክ፣ ፍጹም ሰው በመሆን በዚህ ዓለም የተወለደው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ ልደቱ በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ፡፡

“ወውእቱ ቃል ሥጋ ኮነ
ያ ቃል ሥጋ ሆነ፤”
(ዮሐ. 1፥14)

ቅዱስ እግዚአብሔር በአንድነት በሦስትነት ኖላዊው፣ ጥንት በሌለው ጥንት የነበረ፣ አሁንም ያለ፣ ወደፊትም ፍጻሜ በሌለው ህላዌ የሚኖር አምላክ ነው፡፡ከሦስቱ አካላት “ቃል” ተብሎ የተገለጸው አንዱ አካል ማለትም እግዚአብሔር ወልድ በተለየ አካሉ በብሥራተ ገብርኤል፣ በግብረ መንፈስ ቅዱስ መጋቢት ሃያ ዘጠኝ ቀን በአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመተ ዓለም በቅድስት ድንግል ማርያም ማሕፀን ተፀነሰ፡ ፡“በመጀመሪያው ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ” ቃል እግዚአብሔር ነበረ” ተብሎ ማንነቱ በቅዱስ ወንጌል የተረጋገጠለት “እግዚአብሔር ቃል” በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከቅድሰት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍስዋ ነፍስን ነሥቶ በመዋሐድ እንደኛ ፍጹም ሰው ሆነ፡፡

“እግዚአብሔር ቃል” ሰው ከሆነበት ቅጽበት አንሥቶ መለኮትነቱ ከሰውነቱ፣ ሰውነቱም ከመለኮትነቱ ባለ መለያየት፣ ባለ መጠፋፋት፣ ባለ መለዋወጥ፣ ባለ መከፋፈልና ባለ መቀላቀል አንድ አካል አንድ ባሕርይ ሆነ፡፡ ከሁለት አካል አንድ አካል፣ ከሁለት ባሕርይ አንድ ባሕርይ በመሆን የተፈጸመው የአምላካችን ምሥጢረ ተዋሕዶ ለዘለዓለሙ የጸና ነው፡፡ ይህ ምሥጢረ ተዋሕዶ እግዚአብሔር ለሰው ያለው የፍቅር ጥግ ያሳየ አምላካዊ ድርጊት ነው፡፡ ይህ አምላካዊ ፍቅር ሰውነትን ከባርነት ነፃ ማውጣት ብቻ ሳይሆን፣ ሰውነት በተዋሐደው መለኮት ምክንያት በመንበረ ጸባኦት ተቀምጦ የፍጥረት ሁሉ ገዢ እስከ መሆን ያበቃ ስለሆነ፣ ተመሳሳይም ሆነ ተነፃጻሪ ምሳሌ የማይገኝለት፣ ፍቅር ሁሉ የሚበልጥ የእግዚአብሔር ታላቅ ፍቅር ነው” ለዚህም ነው “እግዚአብሔር ፍቅር ነው” እያለ ቅዱስ መጽሐፍ የሚያስተምረን። የአምላክና የሰው ተዋሕዶ በማሕፀነ ድንግል ማርያም ከተፈጸመበት ጊዜ አንሥቶ መለኮትነቱንና ሰውነቱን በሚገልጹ ስሞች አማኑኤል፣ ኢየሱስ፣ መሲሕ፣ ክርስቶስ፣ መድኀኔ ዓለም እየተባለ ይጠራል፡፡ እነኝህ ስሞች መለኮትነትን ብቻ፣ ወይም ደግሞ ሰውነትን ብቻ የሚያመለክቱ ሳይሆን የመለኮትና የሰውነት ተዋሕዶን በምሥጢር የሚያመለክቱ ናቸው፡፡ በመሆኑም በዛሬው ዕለት ታኅሣሥ ሃያ ዘጠኝ ቀን የተወለደው ሕፃን ፍጹም አምላክ፣ ፍጹም ሰው እንጂ ሰው ብቻም አይደለም፣ አምላክ ብቻም አይደለም። ይህም በመሆኑ ነው በቤተ ልሔም በተወለደ ጊዜ “ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር፣ ለሰውም በጎ ፈቃድ” ተብሎ ለእግዚአብሔር ካልሆነ በቀር ለፍጡር የማይቀርብ ክብርና ምስጋና ከሰማይ ሠራዊተ መላእክት የቀረበለት፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤

ሁሉ በእርሱ የሆነ፣ ያለ እርሱ ምንም ምን የሆነ የሌለ “እግዚአብሔር ቃል” ሰው ሊሆን የቻለው ሰውን ለማዳን ነው፡፡ ሰውን ለማዳን ሲባል የተፈጸመው ይህ ተዋሕዶ፣ በአምላክ ዘንድ ሰውን ማዳን ምን ያህል ታላቅ ነገር እንደሆነ ማስተዋል ለሰው ልጆች ሁሉ እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ምሥጢር ይልቅ ዓለምን ያዳነበት እንደሚበልጥ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስተምሩናል፡፡ ይህ የአምላካችን አድራጎት እኛም ሰውን ከማዳን የበለጠ ሥራ ሊኖረን እንደማይገባ የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ከጌታችን ልደት ምሥጢራዊ መልእክት እንደምናስተውለው አንድነትን፣ ፍጹም ፍቅርን፣ ምሉእ ሰላምን፣ እግዚአብሔርን በመዝሙር ማመስገንን እና ማምለክን፣ ከተቸገሩት ማኅበረሰብ መካከል ተገኝቶ የሰውን ችግር ተካፋይ መሆንን ከአምላክ የተቸረን ፍጹም በረከት እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡ ምሥጢረ ተዋሕዶ፣ ዝማሬ መላእክቱ፣ በከብቶች በረት መወለዱ፣ ለእረኞች መገለጡ፣ በዕለተ ልደቱ ከተገለጡ ዐበይት ክሥተቶች ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በዚህም ቤተ ልሔም የእግዚአብሔር ክብር የበራላት፣ የመላእክትና የእረኞች መዝሙር የደመቀላት፣ እግዚአብሔር፣ መላእክትና ሰዎች በአንድነት የተገኙላት የእውነተኛዪቱ መንግሥተ እግዚአብሔር ማሳያ ሁና ተገኝታለች፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤

በቤተ ልሔም የታየው አምላካዊ መገለጥ ተኣምረ አምላክ ብቻ ሳይሆን፣ በዕለቱ ከታየው ጣዕመ ሕይወት ትምህርት ወስደን እሱን እንድንለማመድ ብሎም እንድንከተል የሚያስገነዝብ አምላካዊ መልእክት የተላለፈበት መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ እግዚአብሔር ሰው ሆኖ በመካከላችን የተገኘበት ዐቢይ ምሥጢር በአንድነት፣ በሰላምና በፍቅር የተወደደ እንደ ዕለተ ልደት ያለ ጣዕመ ሕይወት እንዲኖረን ብሎ እንደሆነ ልናውቅ ይገባል፡፡ ይኸውም እሱ እንደ ተዋሐደን እኛም እርስ በርሳችን ተዋሕደንና አንድ ሆነን በፍቅርና በሰላም እንድንኖር ነው፡፡ ይህንን ስናደርግ በዚህ ከእርሱ ጋር እንዋሃዳለን፤ ለወደፊቱም እግዚአብሔር ሁሉን አዋሕዶ በሚመጣው ዓለመ መንግሥቱ እውን የሚያደርገው ጣዕመ ሕይወት ይኸው እንደሆነ መገንዘብ አለብን፣ መላእክት በቤተ ልሔም ለተወለደው ሕፃን ምስጋናና አምልኮ እንዳቀረቡ እኛም ለምስጋናና ለአምልኮ ተጠርተናል። እሱ ዓለመ ፍጥረትን በእጁ ጨብጦ የያዘ አምላክ ሲሆን፣ በከብቶች በረት ከእረኞች ጋር ውሎውና አዳሩ እንዳደረገ፣ እኛም ሁሌም ውሎአችንና አዳራችን ከምስኪኑ የኅብረተሰብ ክፍል ጋር በማድረግ የተራበውን በማብላት፣ የተጠማውን በማጠጣት፣ የታረዘውን በማልበስ፣ የታመመውንና የታሠረውን በመጠየቅ የጣፈጠ ጣዕመ ሕይወትን መምራት ይኖርብናል፡፡ ዛሬ ሀገራችን በመከራ እየተፈተነች ያለችበት ወቅት ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ብዙ የተፈናቀሉ፣ የተጐዱና ኑሮ የተመሰቃቀለባቸው ወገኖች በየአካባቢው በብዛት መኖራቸው ይታወቃል፣ በቤተ ልሔም የተወለደው ሕፃን ክርስቶስም ከእነርሱ እንደ አንዱ ሆኖ በመካከላቸው እንደሚገኝ እሱ ራሱ ነግሮናል፣ ታድያ እኛም እዚያው ተገኝተን እንድናስተናግደው የወቅቱ ዐቢይ ጥሪያችንና መልእክታችን ነው፡፡

በመጨረሻም፤ በቤተ ልሔም ዙሪያ የጐረፈው የእግዚአብሔር ክብርና ብርሃን፣ ሰላምና ዕርቅ፣ ተዋሕዶና ምስጋና በሀገራችንም ሰፍኖ ወደ ፍጹም ሰላምና አንድነት እንደርስ ዘንድ፣ እግዚአብሔርን በጸሎት ከመለመን ጋር ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለሰላም ለፍቅርና ለአንድነት ያላሰለሰ ጥረት እናደርግ ዘንድ አባታዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

መልካም በዓለ ልደት ያድርግልን
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ይቀድስ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32022-01-07 14:17:552025-01-28 14:18:33ታኅሣሥ 29 ቀን 2014 ዓ.ም የልደት በዓልን መግባት አስመልክተው ያስተላለፉት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 18 ቀን 2014 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ Link to: ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 18 ቀን 2014 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 18 ቀን 2014 ዓ.ም የተካሄደው... Link to: ጥር 11 ቀን 2014 ዓ.ም የጥምቀት በዓልን በማስመልከት በጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀት በተወካያቸው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል። Link to: ጥር 11 ቀን 2014 ዓ.ም የጥምቀት በዓልን በማስመልከት በጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀት በተወካያቸው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል። ጥር 11 ቀን 2014 ዓ.ም የጥምቀት በዓልን በማስመልከት...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top