ጥቅምት 11 ቀን እስከ 16 ቀን 2009 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡

በስመ አብ ወወልድ ለመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ፣ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቍጥር 164 በተደነገገው መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የመክፈቻው ሥርዓተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከጥቅምት 11 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ጥቅምት 16 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባን በማካሄድ፣ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለኅብረተሰባችን የሚጠቅመውን፣ ለሀገርና ለዓለም ሰላም የሚበጀውን አጀንዳ በማመቻቸት በስፋትና በጥልቀት ተወያይቶ የሚከተለውን ውሳኔ አሳልፏል፡፡

“ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር – ኢትዮጵያ ኢትዮጵያውያን ኢትዮጵያውያት እጆቻቸቸውን ወደ እግዚአብሐር ይዘረጋሉ” ይላል ነቢየ እግዚብሔር ዳዊት (መዝ. 67፣31)

ኢትዮጵያ በአፍሪካ ክፍለ ዓለም፣ በአፍሪካ ቀንድ በሰሜን ምሥራቅ አፍሪካ በዐባይ ሸለቆ ዙሪያ በቀይ-ባሕር አካባቢ የምትገኝ ሀገር ናት፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ የነፃነት፣ የአንድነት ዕድሜ የተቈጠረላት በዚህም ረዥም የነፃነትና የአንድነት ዕድሜዋ ብዙ አገልግሎት ያበረከተች ሰፊ ታሪክ ያስመዘገበች ሉዓላዊት ሀገር ናት፡፡

አገራችን ኢትዮጵያ ባሳለፈችው ረዥም ዘመኗ በርካታ ደጋግ መልካም ሥራና ስም የነበራቸው ታላላቅ ሰዎች አልፈውባታል፡፡ ለታሪኳ፣ ለቅርሷ፣ ለባህሏ፣ ለዕድገቷ፣ ለድንበሯ ለአንድነቷ፣ ለነፃነቷ፣ ለክብሯ በሚገርም ወኔና ጀግንነት ደማቸውን ያፈሰሱላት፣ አጥንቶቻቸውን የከሰከሱላት ጀግኖች እንደነበሩአት አሁንም እንዳሏት በታሪክ ተመዝግቧል፡፡ ይህም በመሆኑ ኢትዮጵያውያን አባቶቻችን በዘመናቸው እርስ በርሳቸው በመከባበር የተራበውን በማብላት፣ የተጠማውን በማጠጣት፣ የታረዘውን በማልበስ፣ ያለማውን በማልማት፣ ቤት የእግዚአብሔር ነው በሚል አገራዊ ትውፊት እንግዳ እየተቀበሉ እግር እያጠቡ ቤት ያፈራውን ተካፍለው በመብላት ተከባብረው በመኖር የታወቁ ደጋግ አባቶች ልጆች መሆናችን ይታወቃል፡፡

ሀገራችን ኢትዮጵያ የተለያየ ቋንቋ ተናጋሪ የኅብረተሰብ ክፍሎች ለአያሌ ዘመናት የኖሩባትና አሁንም የሚኖሩባት በአርኣያነት ልትጠቀስ የሚገባት ብቸኛ ሀገር መሆኗ ከማንም ግንዛቤ የተሠወረ አይደለም፡፡ ይሁንና በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን፣ የሰዎች ሕይወት እየጠፋ መሆኑ፣ የአገር ሀብትና ንብረት እየወደመ መታየቱ፣ ከነበሩበት እና ከኖሩበት ቦታ የሕዝቦችን ፍልሰት ማስከተሉ፣ በእነዚህም እየታዩ ባሉ ችግሮች ምክንያት በሰላማዊው ኅብረተሰብ ዘንድ ከፍተኛ ሥጋት እየሰፈነ መምጣቱና ልማታዊ ሥራዎችም ሊስተጓጐሉ እንደሚችሉ መገንዘብ ተችሏል፡፡ ስለዚህ የዚሁ የጥቅምቱ 2009 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በአገሪቱ እየታየ ባለው የሰላም ችግር ላይ በሰፊው በመወያየትና በመነጋገር የሚከተለውን መግለጫ አውጥቷል፡፡

1ኛ. በአገራችን ውስጥ ለአገራችን ዕድገት ሲባል ምላሽ የሚያሻቸው ጥያቄዎች አሉን የሚሉ ወገኖች ሁሉ እንደ ጥንት አባቶቻችን ኢትዮጵያዊነትን በተላበሰ፣ በሰከነና በተረጋጋ ሁኔታ ጥያቄያቸውን ጉዳዩ ለሚመለከተው አካል እንዲያቀርቡ፣
2ኛ. መንግሥት በአንድ አገር ውስጥ ለሚኖሩና ለሚያስተዳድራቸው ዜጎች እንደቤት ኀላፊና ልጆቹን እንደሚያስተዳድር መሪ እንደመሆኑ መጠን በሰከነና በተረጋጋ መልኩ ከዜጎች የሚቀርቡ ጥያቄዎችን በአግባቡ በመፈተሽና በማጥናት ለአገርና ለወገን የሚጠቅመውን ምላሽ እንዲሰጥባቸው ለሕዝቡ የገባውንም ቃል በተግባር አውሎ በሥራ እንዲተረጐም፣
3ኛ. የነገድ፣ የሃይማኖትና የጾታ ልዩነት ሳይኖር ለጋራ ህልውና፣ ለጋራ ልማትና ለጋራ ብልጽግና ለሀገራችን ኢትዮጵያና ለጐረቤት አህጉር ብሩህ ተስፋ ሠንቆ እንደሚመጣ የተነገረለት የሕዳሴው ግንባታ ፕሮጀክት ኢትዮጵያዊነቱን እያስመሰከረ ስለሆነ እንዲሁም በዘመናችን የምንታወቅበት ዐቢይ ታሪካችን የዐባይ ሕዳሴ ግንባታ ግድብ የመሆኑን ያህል አሁንም ፕሮጀክቱ ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ በማንኛውም አቅጣጫ በሁሉም ወገን ያለ ኢትዮጵያዊ ሁሉ በአንድነት ለግንባታው በመሰለፍ አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርግ፣
4ኛ. ባለፈው ዓመት በነበረው የዝናም እጥረት ምክንያት በአገራችን ደርሶ የነበረው ድርቅ በመንግሥትና በመላው ኢትዮጵያዊ ሙሉ ድጋፍ ያለምንም የውጭ ርዳታ ችግሩን መወጣታችን ይታወቃል፡፡ ሆኖም በቀጣዩ ዜጎችን ለረሀብና ለስደት የሚዳርግ እንዲህ ዐይነት አስከፊ አደጋ በአገራችን እንዳይከሠት አገራችን እግዚአብሔር ባደላትና በሚያድላት የተፈጥሮ ጸጋ ምድሪቱን እየተንከባከብን ሁላችንም ኢትዮጵያውያን ለልማቱ በመነሣት ምርታማነትን በማሳደግ ለዕድገት እንድንበቃ ተግተን የሥራ ባህላችንን ልናዳብር ይገባል፡፡
5ኛ. ሥር ነቀል የግንባታ ሥራ እየተካሄደባት ያለች ሀገራችን ኢትዮጵያንና ጥቅሞቿን በማይጻረር በሰላማዊ መንገድ ተቀራርቦ በክብ ጠረጴዛ የጋራ ውይይት በማካሄድ ችግሮችን መፍታት አግባብነት ያለው አሠራር ስለሆነ የሀገር ጉዳይ የጋራና የውስጥ ጉዳይ እንጂ ድንበር ተሻጋሪ እንዳልሆነ በአገሪቱ የሚገኙ የፖለቲካ ተቃዋሚዎች ግንዛቤን ወስደው የበኩላቸውን ድርሻ መፈጸም ይችሉ ዘንድ የራሳቸው የሆነውን አመለካከት ይዘው ሀገሪቱን ከሚመራው መንግሥት ጋር በክብ ጠረጴዛ እንዲወያዩ፣
6ኛ. ቀደምት አበው ኢትዮጵያውያን ዐረፍተ ዘመን እስከገታቸው ድረስ ሀገራቸውን ጠብቀው ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያን ታሪክ ለቀጣዩ ታሪክ ተረካቢ ትውልድ ማቆየታቸው የሚታወቅ ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ወጣቱ ትውልድ ከቀደምት አበው የወረሰውን ትውፊት በመከተል፡- ለሀገራችን የሚጠቅሙትን፣ ለልማትና ለሰላም የሚበጁትን፣ በሀገር ውስጥ ያሉ እና ከሀገር ውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን አንድነትና ኅብረት የሚጠናከርበትን ሁኔታ በመሻት የበኩሉን ድርሻ ማበርከት ይጠበቅበታል፡፡
7ኛ. አገራችን ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ ራሷን ከወራሪ ጠላት በመከላከል ነፃነቷንና ክብሯን፣ ሰላሟንም ጭምር ጠብቃ ይዛ የቈየች መሆኑ ይታወቃል፡፡ ሆኖም ግን በየዘመናቱ የውጭ ወራሪዎችና ጣልቃ ገቦች አገጣሚዎችን እየተጠቀሙ ሕዝቧን ሰላም ለመንሳት ሙከራ ሲያደርጉ እንደቈዩና በመንግሥትና በሕዝቡ አንድነት አስፈላጊው አገራዊ ጥበቃ እየተደረገ ሳየሳካላቸው በነፃነት ኑራለች፡፡ አሁንም በአገራችን እየታየ ያለው የሰላም መታጣት አንዳንድ የውጭ ጣልቃ ገቦች እጅ እንዳለበት በርካታ አመላካች ሁኔታዎች እየታየ ሲሆን እነዚህ ከአገራችን ውጭ በአገራችን ጉዳይ ጣልቃ የሚገቡ ሰላም የሚነሱ የውጭ ዜጎች ከአጥፊ ተልእኳቸው እንዲገቱ ቤተ ክርስቲያን አጥብቃ በማሳሰብ ድርጊቱን ትቃወማለች፡፡
8ኛ. ቤተ ክርስቲያናችን ለአገራችን ኢትዮጵያና ለሕዝቦቿ ባለውለታ በመሆን ሕዝቡን የሰላም ወንጌል በማስተማር የተጣላ በማስታረቅ የተለያየውን አንድ የማድረግ ተልእኮዋን በመፈጸም የቈየች እንደመሆኗ አሁንም ዕለት በዕለት ከምታከናውነው መንፈሳዊ አገልግሎት ባልተናነሰ መልኩ ከቅዱስ ሲኖዶሱ ጀምሮ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት በሕጓና በሥርዐቷ መላው ካህናትና አገልጋዮች በዕለተ ሰንበት ለሚገኘው ሕዝበ ክርስቲያን፣ በማታ ጉባኤ፣ በወርኃዊና ዓመታዊ በዓላት ሁሉ ሕዝበ ክርስቲያኑ በሥነ-ምግባር ታንጾ በፈረሃ እግዚአብሔር በግብረ-ገብነት ለአገሩ ሰላምና ለሕዝቡ አንድነት ተባብሮ እንዲቆም የሚያስችል ትምህርት እንዲሰጡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መመሪያን ያስተላልፋል፣
9ኛ. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እስከዛሬ ባደረገው ስብሰባ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ተዘጋጅቶ በቀረበው የ2009 ዓ.ም. በጀት ላይ ተወያይቶ በሙሉ ድምፅ አጽድቋል፡፡
10ኛ. ከጥቅምት 7-10 ቀን 2009 ዓ.ም.በተካሄደው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የቀረበው የጋራ መግለጫ ላይ ተወያያቶ አንዳንድ ማሻሻዎችን በማድረግ የ2009 ዓ.ም. በጀት ዓመት የሥራ መመሪያ በማድረግ አጽድቋል፡፡
11ኛ. ለተዋሕዶ ሃይማኖታቸው ለሀገራቸው ልዕልናና ነፃነት በ1928 ዓ.ም.ከአርበኞች ጎን በመሆን ለሀገራቸው ነፃነት ጠንክረው እንዲዋጉ ሲያስተምሩ በነበረበት ወቅት በኢጣልያ ፋሽስታዊ መንግሥት በጎሬ ከተማ በ1929 ዓ.ም. በግፍ በሰማዕትነት የተገደሉት ብፁዕ አቡነ ሚካኤል ሰማዕት ተብለው እንዲጠሩ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ወስኗል፡፡
12ኛ. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ከጥቅምት 12- 16 ለአምስት ቀናት ባደረገው መደበኛ ስብሰባ ከላይ በተጠቀሱትና በሌሎችም በቤተ ክርስቲያኒቱ ልዩ ልዩ ጉዳዮች ላይ ሲወያይ ሰንብቶ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት አጠናቋል፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ አሜን፡፡

ጥቅምት 12 ቀን 2009 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፡ ከየሀገረ ስብከታችን አሰባስቦና በዚህ ቅዱስ ስፍራ አገናኝቶ ስለአጠቃላይ መንፈሳዊ ተልእኮአችን ለመወያየት ያገናኘን እግዚአብሔር አምላካችንን እናመሰግነዋለን፡፡

“ኦ አባ ቅዱስ ዕቀቦሙ በስምከ ለእለ ወሀብከኒ ከመይኩኑ አሐደ ብነ ከማነ፤ ቅዱስ አባት ሆይ እነዚህን የሰጠኸኝን እንደ እኛ አንድ እንዲሆኑ በስምህ ጠብቃቸው” (ዮሐ17፡11)፡፡

በቃለ እግዚአብሔርም ሆነ በገሃዳዊው ዓለም ተጨባጭ አኗኗር እንደሚታየው የፍጡራን አንድነት ተፈጥሮኣዊ ጸጋ ከመሆን አልፎ አስገዳጅ የህልውና ዋስትናም እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል፡፡ የአንድነት አስፈላጊነት በተመሳሳይ ዘርዐ ፍጡራን ብቻ የሚወሰንም አይደለም፤ በምንኖርባት ዓለም የሚገኙ የሚንቀሳቀሱና የማይንቀሳቀሱ ፍጡራን በአጠቃላይ፣ አንድነት ኖሮአቸው እርስ በርስ የማይመጋገቡ ከሆነ ህልውና ጣዕም አይኖረውም ብቻ ሳይሆን ጭራሽኑ መኖር እንደማይችሉ ግልጽ ነው፡፡

እግዚአብሔር በከሃሊነቱ እርስ በርስ አቆራኝቶ አስተሳስሮና ተመጋጋቢ አድርጎ የፈጠራቸውን ፍጡራን በሰው ሠራሽ ምክንያት ለማለያየት መጣር፣ ሙከራ ከመሆን አልፎ ዘላቂ የሆነ ተቀባይነት ሊኖረው አይችልም፤ ምክንያቱም ፍጡራን ሁሉ ማኅበራውያንም አሐዳውያንም ሆነው ሊኖሩ በአምላክ ጸጋ ተፈጥረዋልና ነው፤ ዛሬ ዓለም በአጠቃላይ በኢኮኖሚና በማኅበራዊ ሕይወት እንደ አንድ መንደር እየሆነች የመጣችው በራስዋ ጥበብ ሳይሆን እግዚአብሔር ጥንቱም ማኅበራዊ ሆና እንድትኖር አድርጎ ስለፈጠራት ነው፡፡

ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ወደዚህ ዓለም የመጣው በፍጡራን መካከል ጠንካራ ኅብረትና አንድነት እንዲኖር ለማድረግ ነው፤ ጌታችን በትምህርትም በተግባርም ያረጋገጠውም ይኸው ነው፡፡ ጌታችን ለፍጡራን በአጠቃላይ፣ በተለይም ለሰው ልጅ ያስተማረው የአንድነት ትምህርት ከራሱና ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ ጋር ካለው መለኮታዊና ባሕርያዊ አንድነት ጋር በማነጻጸር መሆኑንም የአንድነት አስፈላጊነት ምን ያህል ትልቅ ስፍራ እንዳለው የሚያሳይ ነው፡፡

የጌታችን ትልቁ ጸሎትና ትምህርት የሰዎች አንድ መሆን እንደሆነ ከቅዱስ ወንጌል ተምረናል፣ አውቀናልም፤ በመሆኑም ክርስቶሳዊ፣ ሐዋርያዊና ዐቢይ የሆነው ይህ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ፣ የጌታችንን ትምህርትና ትእዛዝ የመጠበቅና የማስጠበቅ የመፈጸምና የማስፈጸም ኀላፊነት እንዳለበት መዘንጋት የለብንም፡፡

እኛ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሕዝብን አንድነት ለመጠበቅ ሕዝብን የሚያስማማና የሚያግባባ ትምህርት ማስተማር ይገባናል፣ ማስተማርም ያለብን ምንም ምን ያልተቀላቀለበት ንጹሕ የእግዚአብሔር ቃል ሊሆን ይገባል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ሁሉንም ያስማማል ሁሉንም ያግባባል በመስማማት ላይ የተመሠረተ አንድነትም ፍሬ ሰላምን ያፈራል፡፡

እኛ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሰላም ሐዋርያት ሆነን በጌታችን ተሹመናል፤ ለሕዝቡ ሁሉ የእግዚአብሔርን ሰላም እንድናደርስም “ሰላማችሁ ይድረስለት” ተብለን ሰላመ እግዚአብሔር በእኛ በኩል ለሕዝቡ ተልኮአል፤ አሁን ጥያቄው የሰላም ተልእኮውን ለሕዝቡ እንድናደርስ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠንን አደራ በሚገባ እያደረስን ነው ወይ? የሚለው ነው፤ መልሱ አጭርና ግልጽ፣ እየታየም ያለ ይመስለናል፡፡

እኛ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በዚህ ዓለም ንጹሕ የሆነውን የእግዚአብሔር ቃል እንዳናስተምርና ሕዝቡን አስማምተን አንድ እንዳናደርግ የሚከለክለን እንደሌለ እናውቃለን፣ ነገር ግን ማስተማር የሚያስችል ምቹ ሁኔታ እያለ በሚገባ ባለማስተማራችን ሕዝቡ ግራ ከተጋባ የጎደለ ነገር አለ ማለት ነው፤ እርግጥ ነው ይህን ስንል ሥራ አልተሠራም ትምህርትም አልተሰጠም ማለታችን አይደለም፤ነገር ግን እኛ ማየት ያለብን ጌታችን “ወገቢረክሙ ኵሎ በሉ አግብርት ፅሩዓን ንሕነ” ብሎ ያስተማረውን ነው፡፡

ዛሬ ሌሎች፣ ከእኛ ጉድለት አለ፤ እኛ አስተካክለን መሥራት የሚገባንን አልሠራንም እያሉ ለበለጠ ሥራ ሲዘጋጁ፣ የቃሉ መልእክተኞች የሆን እኛ ይህንን እውነተኛ የጌታችን ቃል ልናልፈው አይገባም፣ እየሆነ ያለው ሁኔታም ሲታይ ሕዝቡ የስምምነት፣ የአንድነት፣ የሰላምና የፍቅር ሕዝብ እንዲሆን ለማድረግ የሚቀረን ሥራ እንዳለ ያመለክታል፡፡ ሕዝቡ የእግዚአብሔር ማእደ ሰላም ከሆነች ቤተ ክርስቲያኑ የሰላምን ማእድ መቋደስና ማጣጣም እንዲችል ያለማቋረጥ ስለ ሰላምና ስለፍቅር ጠንክረን ማስተማርና መሥራት ይገባናል፡፡

በተለይም በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን የተከሠቱ ግጭቶችና ሁከቶች ለዘላለም ተፈቃቅረውና ተዋደው ለዘመናት በአንድነት የኖሩትን የሀገራችን ሕዝቦች እርስ በርስ እንዲቃቃሩ ከማድረጉም ባሻገር የሕይወት ጥፋትና የንብረት ውድመት አስከትሎአል፣ የልማት አውታሮችን ጎድቶአል፤ ብዙ ዜጎችንን ያለሥራ አስቀርቷል በሕዝቦች መካከል የኅሊና ስብራት ፈጥሮአል፤ ይህ ለቤተ ክርስቲያናችንም ሆነ ለሀገራችን አሳዛኝ ክሥተት ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን የሕዝብ ሁሉ እናት ናት፤ እናት ከሁሉ በፊት ለልጇ ደራሽ እንደመሆኗ መጠን ቤተ ክርስቲያናችንም ችግሩ ከተከሠተበት ጊዜ አንሥቶ ኀዘኗንና የሰላም ጥሪዋና በተደጋጋሚ ስትገልጽ ቆይታለች፡፡ ይሁንና አሁንም የተከሠተው የሰላም መደፍረስና የኅሊና ስብራት ቀላል ስላልሆነ ሰላሙ አስተማማኝ እስኪሆንና የኅሊና ስብራቱም ተጠግኖ እስኪሽር ድረስ በሰላም መጠናከር ዙርያ መጠነ ሰፊ የሆነ ሥራ መሥራት ይኖርብናል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን የሁሉም እናት ነች ስንል የኢትዮጵያ ሕዝቦችም በሙሉ ልጆችዋ ናቸው ማለታችን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ወደዚህም ወደዚያም ሳትል ማእከላዊና ገለልተኛ ሆና የሰላም መልእክቷን ብቻ ለሁሉም ማድረስ ይገባታል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ዘላቂና ብዙኃኑን የሚጠቅም የሰላም ህልውናን ለማረጋገጥ በሚደረግ ማንኛውም እንቅስቃሴ ተሳትፎዋን በማሳደግ ለሕዝብና ለሀገር ደኅንነት መሥራት ይኖርባታል፡፡ በተለይም ዘርን በመለየት የሀገርን አንድነት በመፈታተንና በሃይማኖት አመክንዮ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ሕዝባችንን ሀገራችንንና ሃይኖታችንን በእጅጉ የሚጎዱ ስለሆኑ ሕዝቡ እንዲጠነቀቅባቸውና በአርቆ አስተዋይነት እንዲመለከታቸው በልዩ ትኵረት ማስተማር ይኖርብናል፡፡

ሕዝቦቻችን በተለይም ወጣት ልጆቻችን ለአደጋ እየተጋለጡበት ያለው ክፍተት የሥራ አጥነት ችግር እንደሆነ እየሰማን ነው፤ ሁሉም በልቶ ካደረ ችግሩ ሊቀንስ እንደሚችል ጥርጥር የለንም፡፡ ሆኖም የዚህ ቊልፍ መፍትሔ ልማትን በማስፋፋት ዕድገትን ማምጣት ነው፡፡ ዕድገቱን ሊያመጣው የሚችል ደግሞ እኛ እየመራነውና እያስተማርነው ያለው ሕዝብ ነው፡፡ ስለሆነም ሕዝቡ ዐቅሙን ሁሉ አስተባብሮ ወደ ልማት እንዲሠማራ ያለ መታከት ማስተማር ያለብን እኛው ብፁዓን ሊቃ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ካህናት ሰባክያነ ወንጌል ነን፤ ነገር ግን አስተማሪዎች ብቻ ሳንሆን ሠርተን የምናሳይም መሆን ስላለብን ቤተ ክርስቲያናችን በሁሉም አቅጣጫ ልማትን በማስፋፋትና ለወጣቱ ትውልድ የሥራ ዕድልን በመፍጠር እናትነትዋን በተጨባጭ ማሳየት አለባት፤

ስለሆነም በዚህ ቅዱስ ዓመታዊ ጉባኤያችን በሰላም መጠናከርና መጠበቅ ዙርያ፣ በልማት ሥራ መስፋፋትና በስብከተ ወንጌል መጠናከር ላይ ሰፊና ጥልቅ ውይይት በማድረግ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሕዝባችን እንደዚሁም ለሀገራችን በአጠቃላይ የሚጠቅሙ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ጉባኤውን እንድናጠናቅቅ በማሳሰብ፣ ለስኬቱም ያለንን ልባዊ ምኞትና ጸሎት በመግለጽ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዕለት በይፋ መከፈቱን እናበስራለን፡፡

እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

በ35ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ የሰበካ ጉባኤ ጥቅምት 7 ቀን 2009 ዓ.ም. አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤ ክቡራን የየመምሪያውና የየድርጅቱ ኀላፊዎች፣ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ ከሚገኙ አህጉረ ስብከት የመጣችሁ ሥራ አስኪያጆችና ተወካዮች፣ የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎችና ተወካዮች፣ በአጠቃላይ በዚህ ዓመታዊና ዓለም አቀፋዊ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የተገኛችሁ ተሳታፊዎች በሙሉ፤

የምሕረት አባትና የሰላም ባለቤት የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን ለዚህ ዓመታዊ የቤተ ክርስቲያናችን ዐቢይ ጉባኤ ስላደረሰን በቅድሚያ ክብርና ምስጋና ለእርሱ እናቀርባለን፡፡ እናንተንም እንኳን አደረሳችሁ እንኳንም በደኅና መጣችሁ እንላለን፡፡

“እንዘ አልብነ ኵሉ ብነ
አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የኛ ነው፤”
(2ቆሮ. 6፥10)፡፡

የሃይማኖት ጉዞ ሁሉ የመንፈስ ጒዞ ነውና በመንፈስ ጀምሮ በመንፈስ የሚጠናቀቅ እንጂ እንደገና ተመልሶ ወደ ግዙፉና ዓለማዊው ነገር የሚዘፈቅ አይደለም፤ እንደዚህ የሚሞከር ከሆነም ዐላማውን ስቶ ይወድቃል እንጂ ውጤታማ መሆን ፈጽሞ አይችልም፡፡

የሃይማኖት ሥራ በዋነኛነት የሚከናወነው በካህናት እንደሆነ ለሁሉም ግልጽ ነው፤ ካህናትም በትምህርተ ሃይማኖት ጸንተው፣ በኀይለ መንፈስ ቅዱስ ጎልብተው ዓለምንና በውስጡ ያለውን እየተዋጉ በማሸነፍ በድል አድራጊነት ወደፊት እንዲገሠግሡ እንጂ እንደገና በፍትወታት እኩያት ተሸንፈው ወደ ዓለማዊው አስተሳሰብና አኗኗር እንዲቀላቀሉ አልተፈቀደም፤ ካህናት የቆሙበት ስፍራና የተሸከሙት ኀላፊነት መለኮታዊ መንፈሳዊና ዘላለማዊ ነውና፤ ይሁን እንጂ ካህናት የመንፈስ ተቃራኒ የሆነውን አካለ ሥጋ የለበሱ በመሆናቸው ለሥጋዊ ኑሮአቸው የሚያስፈልግ ሁሉ በምእመናን እንዲሟላላቸው በብሉይ ኪዳንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን በእግዚአብሔር ታዞአል፡፡

ካህናት እንደ ሐዲስ ኪዳኑ ሁሉ በብሉይ ኪዳንም በደብተራ ኦሪትና በዙርያው በነበረው የግብረ ክህነት አገልግሎት ሌት ተቀን ፅሙድ እንደ በሬ ቅኑት እንደ ገበሬ ሆነው በትጋት መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን ያከናውኑ እንደነበር እናውቃለን፡፡ ይሁንና ለኑሮአቸው የሚያስፈልገውን በተመለከተ የተፈቀደላቸው ቢኖር የዓለም የሆነውን ርስተ መሬት ሳይሆን ርስታቸው ራሱ እግዚአብሔር እንደሆነ ቅዱስ መጽሐፍ ያረጋግጣል ፤ ይህንንም አስመልክቶ ቅዱስ መጽሐፍ እንደዚህ ይላል “እግዚአብሔር አሮንን አለው፡- በምድራቸው ርስት በመካከላቸውም ድርሻ አይሆንልህም፤ በእስራኤል ልጆች መካከል ድርሻህና ርስትህ እኔ ነኝ”፤ (ዘኍ. 18፥20)፡፡ ይህም ማለት የካህናት ሥጋዊ ኑሮ በርስተ መሬት ላይ ሳይሆን በሃይማኖተ ምእመናን ላይ በተመሠረተ ቃለ እግዚአብሔር ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በሌላ አባባል፡- እግዚአብሔር ለካህናት የፈቀደው ርስት መሬታዊ ሳይሆን ዐሥራቱ፣ ቀዳምያቱና በኵራቱ ከምእመናን በነቂስ እየተከፈለ ለካህናት መተዳደሪያ ይሆን ዘንድ ለቤተ እግዚአብሔር እንዲሰጥ አድርጎአል ማለት ነው፤ (ዘፀ. 13፥2፣ ዘኍ. 18፥20-24፣ ዘሌ. 23፥9-14)፡፡ በዘመነ ሐዲስም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያንኑ የኦሪቱን ዐስበ ካህን በማጽናት “ይደልዎ ዓስቡ ለዘይትቀነይ፤ ለሠራተኛ ደመወዙ ይገባዋል” ብሎአል (ማቴ.10፥10)፡፡

ከጥንት ጀምሮ ካህናተ እግዚአብሔር ይህ ነው ተብሎ የሚነገርና ግዙፍ የሆነ ምድራዊ ሀብት እንደሌላቸው ከላይ በተገለጸው ቃለ እግዚአብሔር ዋቢነት ማወቅ ይቻላል፤ ይሁን እንጂ ካህናት ኀላፊና ጠፊ የሆነው ምድራዊ ሀብት አይኑራቸው እንጂ የማያልፍና ተቈጥሮ የማያልቅ መለኮታዊ ሀብት በምድር ሳይቀር እንዳላቸው በቅዱሳት መጻሕፍት አስተምህሮም ሆነ በተግባር ታይቶአል ፡፡ ከዚህም የተነሣ ነው “ አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የእኛ ነው” ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ የተነገረው፤ነገሩም እውነት ነው ፤አንድ ካህን ብዙ ገንዘብ ወይም ሌላ ሀብት ላይኖረው ይችላል ፤ ነገር ግን በብዙ የሚቀጠሩ ምእመናን አሉት፡፡

ከዚህ አኳያ ካህን ምንም የሌለው ቢመስልም አያያዙን ካወቀበት ብዙ ሀብት ያለው ነው ብንል ፍጹም እውነት እንጂ ሽንገላ ሊሆን አይችልም፤ ሁላችንም ከምር ማወቅና መቀበል ያለ ብን ዐቢይ ጉዳይ ሀብት ማለት የገንዘብና የእንስሳት ብዛት ወይም የመሬት ይዞታ ስፋት ሳይሆን የሰው ብዛት መሆኑን ነው ፤ምክንያቱም የሰው ሀብት ካለ ሌላው ሁሉ ከሰው ዘንድ ይገኛልና ነው፤ ለእኛም ለካህናት ትልቁና ቋሚው ሀብታችን የሰው ሀብት ነውና አንዳች የሀብት ወረት የሌለን ስንሆን እንደ እግዚአብሔር ቃል ብዙ የሰው ሀብት አለን፡፡

ከዚህ አንጻር የቤተ ክርስቲያን ቀዋሚ ሀብቶች ምእመናን በመሆናቸው በየጊዜው ብዙ ችግሮች ሲያጋጥሙአት በምእመናን ድጋፍ ሁሉንም ስትወጣው ቆይታለች ፤የሩቁን ትተን ከዛሬ አርባ ዓመታት በፊት የሆነውን እንኳ ብንመለከት የነበራት የመሬት ሀብት ሁሉ በጊዜው በነበረው መንግሥት ሲወረስ የማይነጥፉና ቀዋሚ ሀብቶች ሆነው የደረሱላት ምእመናን ብቻ ነበሩ፡፡ በወቅቱ የቤተ ክርስቲያን ቀዋሚና የማይነጥፍ ሀብት ምእመናን ብቻ መሆናቸውን የተረዱት ቀደምት ቅዱሳን አበው በተለይም ሁለተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ምእመናንን በቃለ ዐዋዲ አደራጅተው ተገቢውን አስተዋፅኦ እንዲከፍሉ በማድረጋቸው በአሁኑ ጊዜ ከሞላ ጎደል ቤተ ክርስቲያናችን ተልእኮዋ በአግባቡ እንድትወጣ፣ የካህናት ኑሮም እንዲሻሻል ለማድረግ ተችሎአል፡፡

ይሁን እንጂ ጌታችን “ማእረሩ ብዙኅ ውእቱ ወገባሩሰ ኅዳጥ ውእቱ፤ አዝመራው ወይም መከሩ ብዙ ነው፤ ሠራተኛው ግን ጥቂት ነው” (ማቴ 9፡37) እንዳለው ዛሬም አዝመራው ብዙ ሆኖ ሳለ ሠራተኛው ጥቂት በመሆኑ ቀላል የማይባል ክፍተት ይስተዋላል፤ ይህም ማለት የሰው ኀይል እጥረት ባይኖር እንኳ ከአስተሳሰብና አሠራር ክፍተት የተነሣ አዝመራው በሚገባ ሳይያዝና ሳይጠበቅ እየቀረ ሌሎች ወፎች እየለቃቀሙት እንደሆነ በግልጽ ይታያል፡፡ ይህ ባይሆን ኖሮ ከኃምሳ ሚሊየን ያላነሱ ምእመናን ያሏት ቤተ ክርስቲያን በአሁኑ ጊዜ በመቶ ሚሊዮን ሳይሆን በቢሊየኖች የሚቈጠር የገንዘብ ሀብት አሰባስባ ትላልቅ መንፈሳዊ ተቅዋማትን ትገነባ ነበር፤ በዚህም ሀብትዋ ተጠቅማ አረጋውያንንና አሳዳጊ አልባ ሕፃናትን፣ በየማእከሉ ሰብስባ በሚገባ ትረዳ ነበር፣ የትምህርትና የጤና ተቅማዋት የመሳሰሉትን ማኅበራዊና መንፈሳዊ ተቅዋማትንም በብዛት ከፍታ ለሕዝቡ ችግር መቃለል ፈጥኖ ደራሽ መሆን ትችል ነበር፡፡

ዛሬም ጊዜው እየነጋ እንጂ እየመሸ አይደለምና አሁንም ከሁሉ በፊት ሀብታችን ያለበትን አካባቢ በውል ማወቅ ይኖርብናል ሀብታችን ያለው በምእመናን ልቡና ውስጥ ነው፡፡ እሱን በእግዚአብሔር ቃል አለስልሰን፤ በሥነ ምግባር ኰትኵተን ለመልካም ፍሬና ለጥሩ ምርት ማብቃት አለብን፤ ከአያያዝና ከትምህርት ጒድለት አንድ ምእመን ከበረታችን በተወሰደ ቍጥር ሀብታችን እየቀነሰ መሆኑን በውል እንገንዘብ ፤ምእመናን እስከ በዙና እስከተጠበቁ ድረስ ካህናት ሀብታሞች ነን ፤ ምእመናን እየቀነሱ በሄዱ ቊጥር ግን መደኽየታችን የማይቀር ነው፡፡ ስለዚህ እኛ ካህናት ሁሌም መጨነቅ ያለብን ስለ ሀብት ድልብ ሳይሆን ስለምእመናን ድልብ ነው፤ ምእመናን ካሉ ሀብቱ አለና፤ ከኃምሳ ሚሊዮን በላይ ምእመናን ካሉንና በእነርሱ ላይ ተገቢ ጥበቃና አገልግሎት ካበረከትን የሚጎድልብን አንዳች ነገር አይኖርም፤ የሰበካ ጉባኤ ዐቢይ ተልእኮም ይኸው ነው፤ እስካሁን በሚታየው ተጨባጭ እውነታ የሰበካ ጉባኤ ዐላማ እኛ ካህናት ሀብታሞች መሆናችንን ያረጋገጠ ወንጌላዊ መሣሪያ እንደ ሆነ ከቶውኑ ልንዘነጋ አይገባም፡፡

ሰበካ ጉባኤ ትልቅና አስተማማኝ የሀብት ምንጭ እንደሆነ ተረጋግጦ ባለበት ሁኔታ እድገቱ አዝጋሚ ሆኖ መታየቱ ችግሩ የእኛ እንጂ የመሠረተ ዐላማው አለመሆኑን በሚገባ መታወቅ ይኖርበታል፡፡ ዛሬም፣ ነገም፣ ቤተ ክርስቲያናችንን ወደ ላቀ መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ የእድገት ደረጃ ለማሸጋገር ብቸኛውና ዋነኛው ቊልፍ ሰበካ ጉባኤ መሆኑን ሁላችንም ልናሠምርበት ይገባል፤ ስለሆነም እኛ ካህናት ሌት ተቀን በመሥራት፤ ምእመናንን እንደ እግዚአብሔር ቃል በመጠበቅና በመንከባከብ እንደዚሁም የሚጠበቅብንን መልካም ሥነ ምግባር ሁሉ ለምእመናን በማሳየት የቤተ ክርስቲያናችንን እድገትና ሉዓላዊ ክብር እስከ መጨረሻው ማስከበር ይጠበቅብናል፤

የካህናት መደበኛ ሥራ ምእመናንን ከማንኛውም ጒዳት መጠበቅ እንደሆነ የማይካድ ነው፤ የምእመናን ጥበቃም የተሟላ እንዲሆን በሀገር ዐቀፍ ደረጃ ከዚያም አልፎ በዓለም ዐቀፍ ደረጃ የተሟላ ሰላም መኖር የግድ ይላል፤ የመጀመሪያው ጥበቃም ማተኰር ያለበት በሰላም መረጋገጥ ላይ ነው፤ ምክንያቱም ሰላም ከሌለ ምእመናን የሚጠመቁበትና የሚቈርቡበት ቤተ ክርስቲያንም አደጋ ላይ ይወድቃል፤ በሰላም ወጥቶ ቤተ ክርስቲያን ደርሶና ከእግዚአብሔር ጋር ተገናኝቶ መመለስም ይቆማል፤ በዚህ ሁሉ ሃይማኖቱ ራሱ አደጋ ላይ ይወድቃል፤ ባለፉት ወራት በሀገራችን የተከሠተው የሰላም መደፍረስ አደጋ ያሳየን ነገር ቢኖር ይኸው የምእመናን ጒዳት ነው፡፡ በተለይም ዘርንና ሃይማኖትን ለይቶ የሀገርን አንድነት ለመናድ የሚደረገው ሙከራ ጎጅነቱ ወደር የማይገኝለት ነው፡፡ የኦሮሞ የኢሬቻ በዓል ላይ የደረሰው የሰው ዕልቂትም በኢትዮጵያውያን አእምሮ ውስጥ ቊስል አሳልፎ አልፏል፡፡ በዚህም ምክንያት ምእመናን ከተጎዱ ቤተ ክርስቲያን በቀጥታ ትጎዳለች፤ የሀገር ሰላም ከደፈረሰ ጒዞው ሁሉ ወደፊት መሆኑ ቀርቶ የኋልዮሽ ይሆናል፡፡ ታዲያ የኛ መምህርነትና አባትነት ለዚህ ጊዜ ያልሆነ ለመቼ ሊሆን ነው? እኛ አስተምረነው፣ መክረነው ታረቅ ብለነው የማይሰማን ሰው በዚህች ሀገር ይኖራል ብለን አናስብም፡፡

ስለሆነም ከላይ ጀምሮ እስከ ታች ያሉ የቤተ ክርስቲያናችን ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መምህራን ሊቃውንትና ካህናት በሙሉ የነበረን የሰላም ሀብት ልማታችንና እድገታችን በማይዋጥላቸው ባዕዳንና በሌሎች አካላት ሳይነጠቅ በነበረው ዐይነት ተጠብቆ እንዲቀጥል ለማድረግ ዙርያ መለስ ርብርብ ማድረግ ይገባናል፡፡ ሕዝባችን ሰላምን፣ እድገትን፣ አንድነትን፣ ልማትን፣ እኩልነትን፣ ፍትሓዊነትን፣ መልካም አስተዳደርን ብቻ እንደሚፈልግ እየነገረን ነው፡፡ ሕዝቡ ይህ ጥያቄ እንዲመለስለትና እውን እንዲሆንለት በመንግሥትና በሕዝቡ መካከል አገናኝ ድልድይ ሆነን መሥራት ይኖርብናል፤ ከእግዚአብሔር የተቀበልነው አደራና ተልእኮም ይኸው ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ በእሬቻ በዓልና በሌሎችም አካባቢዎች በተፈጠረው ሁከትና ግርግር ሕይወታቸውን ያጡ ወገኖቻችን ሁሉ እግዚአብሔር በመንግሥቱ እንዲቀበልልን፣ ለቤተሰቦቻቸውም መጽናናትን እንዲሰጥልን፣ወደፊትም ሕዝባችንን ከመሰል አደጋ እንዲጠብቅልን፣ ጸሎታችንን ወደ እግዚአብሔር እናቀርባለን፡፡

በመጨረሻም፡ ይህ ዐቢይ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያናችን ዐበይት ጉዳዮችና በሀገራዊ ሰላም መጠበቅ ዙሪያ በሰፊው ተወያይቶ የበኩሉን ለማድረግ ቃል በመግባት ስብሰባውን እንዲያጠናቅቅ እያሳሰብን ሠላሳ አምስተኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ በዛሬው ዕለት መከፈቱን እናበሥራለን፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡