• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ጥቅምት 7 ቀን 2015 ዓ.ም 41ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዕ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና በሰሜን አሜሪካ የኒዮርክ እና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳስት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤
የተከበራችሁ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የየመምሪያውና የየድርጅቱ ኀላፊዎች፤
የየአህጉረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጆችና የየክፍሉ ኀላፊዎች፤
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ኀላፊዎችና የየሀገረ ስብከቱ ተወካዮች፤
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፤ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣት ልጆቻችን፤
በውጭ አህጉር ከሚገኙ ልዩ ልዩ አህጉረ ስብከት የመጣችሁ እንግዶች፤
በአጠቃላይ በዚህ ዓለም ዐቀፍ ጉባኤ ለመሳተፍ በዚህ ቅዱስ ስፍራ የተገኛችሁ ክቡራንና ክቡራት፡-

ሁሉ የሚቻለው የሚሳነው ነገርም የሌለው አምላካችን እግዚአብሔር አርባ አንደኛውን ዓለም ዐቀፍ የሰበካ መንፈሳዊ ጠቅላላ ጉባኤ በዚህ ሰዓት እንድናካሂድ ስለፈቀደልን ክብርና ምስጋና አምልኮና ውዳሴ ለእሱ ይሁን፡፡ እናንተንም አቅፎ ደግፎ በሰላም ወደ ሀገራችሁና ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናችሁ መንፈሳዊ ጉባኤ ስላመጣልን በድጋሚ እሱን እያመሰገን እንኳን ደህና መጣችሁ በማለት ደስታችንን ልንገልፅላችሁ እንወዳለን፡፡

“ገሥጽዎሙ ለሕዝብየ ወአጽንዕዎሙ ይቤ እግዚአብሔር
አጽናኑ፣ ሕዝቤን አጽናኑ ይላል እግዚአብሔር”
(ኢሳ. 40፥1)

ይህ ቃል የኀያሉ አምላካችን የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ቃሉ እንደሚያመለክተው በዚህ ዓለም ያለው ሕዝብ ባለቤት ያለው መሆኑን ነው፡፡ ማንኛውም ፍጡር በራሱ ለራሱ የተፈጠረና በሕይወት የሚኖር የለም፡፡ ሁሉም በእግዚአብሔር ለእግዚአብሔር ተፈጠረ፥ ለእግዚአብሔርም በሕይወት ይኖራል፡፡

ሰው በዚህም ዓለም በወዲያኛውም ዓለም ለእግዚአብሔርና የእግዚአብሔር እንደ ሆነ ቅዱስ ጳውሎስ ሲነግረን፡- “ወአልቦ እምውስቴትነ ዘለርእሱ የሐዩ፣ ወዘለርእሱ ይመውት፤ እመኒ ሐየውነ ለእግዚአብሔር ነሐዩ፤ ወእመኒ ሞትነ ለእግዚአብሔር ንመውት፤ እመኒ ሐየውነ ወእመኒ ሞትነ ለእግዚአብሔር ንሕነ፡- ከእኛ አንድ ስንኳ ለራሱ የሚኖር የለምና ለራሱም የሚሞት የለምና፣ በሕይወት ብንኖር ለእግዚአብሔር እንኖራለን፤ ብንሞትም ለእግዚአብሔር እንሞታለን፤ በሕይወት ብንኖርም፣ ብንሞትም የእግዚአብሔር ነን ይለናል፡፡

ከዚህ ትምህርተ እግዚአብሔር እንደምንገነዘበው ሰው በዚህም ዓለም ሆነ በወዲያኛውም ዓለም፣ በሕይወት የሚኖር እንጂ የሚጠፋ አለመሆኑን፣ በዚህም ኖረ በዚያ ምን ጊዜም የእግዚአብሔር ገንዘብ መሆኑን፣ በዚህም ሆነ በዚያ ለእግዚአብሔር እንጂ ለራሱ እንዲኖር ያልተፈጠረ መሆኑን በግልጽ ያስረዳናል፡፡

ዋና ጭብጡ ሰው ፈቅዶ የፈጠረው ዛሬም ሆነ ለወደፊት የሚፈልገው ባለቤት ያለው መሆኑን፣ እሱም እግዚአብሔር እንደ ሆነ በውል ማስገንዘብ ነው፡፡ ይህም በመሆኑ ነው የሕዝቡ ፈጣሪና ባለቤት የሆነ እግዚአብሔር የእርሱ የሆነውን ሕዝብ እንከን እንዲነካው አልፈቀደም፤ ባለመፍቀዱም “ኢትግሥሡ መሲሓንየ፡- ማለት በልጅነት ያከበርኳቸውን ሕዝቤን አትንኩ” ብሎ ሲያስጠነቅቅ እንሰማለን፤ የሚነካም ካለ እናንተ “ሕዝቤን አጽናኑ” ብሎ አዝዞናል፡፡ የተነካውን ሕዝበ እግዚአብሔር ማጽናናት የእኛ ተቀዳሚ ተልእኮ እንደ ሆነ ይህ ዐቢይ ጉባኤ በአጽንዖት ሊቀበል ያስፈልጋል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፡ የተከበራችሁ እንግዶች!!
በዚህ አሁን ባለንበት ዘመን የእግዚአብሔር ሕዝብ በምን ሁኔታ ላይ ነው ያለው ብሎ መጠየቅ ከኛ ይጠበቃል፡፡ ሕዝባችን በአሁኑ ጊዜ ሕይወቱንና ንብረቱን፣ ልጁንና ሚስቱን፣ ቤተ ሰቡንና ሰላሙን እያጣ ነው፡፡ ያላጣው ነገር የለም፤ ሁለመናው ተነክቶአል፡፡ ይህ ሲሆን እኛ ማድረግ ያለብን ነገር ምን እንደሆነ ተነግሮናል፤ እርሱም ማጽናናት ነው፡፡ ከማጽናናትም አልፎ ቤዛ ሆኖ እስከ መሰጠት ድረስ መራመድ ነው፡፡

ያለንበት ጊዜ ይህንን ሁሉ እየጠየቀን ነው፡፡ ሕዝቡን ማጽናናት ከኛ ይጠበቃል፡፡ ሕዝቡን የምናጽናናው በቃላት ብቻ ሊሆን አይገባም፤ በመሐሉ ገብተን በመገሠጽና በመምከር፣ በማስተማርና በማሳመን፣ በማስታረቅና እፎይታን በማጐናጸፍ ሊሆን ይገባል፡፡ ሕዝቡ ሕዝባችን ነው፤ እኛም የእርሱ ነን፡፡ ሕዝባችን እርስ በርስ ነው እየተላለቀ ያለው፤ ሌላ ተጨማሪ ቢኖርም ከኛ በተፈጠረው ክፍተት እንጂ በሌላ አይደለም፡፡ ሕዝባችንን የሚያጣላና የሚያፋጅ፣ አሁን ከደረሰበት ደረጃም የሚያደርስ በቂ ምክንያት የለውም፡፡ ቢኖርም በውይይትና በምክክር፣ በፍቅርና ጊዜ ሰጥቶ በማሰላሰል መልክ ሊይዝ የሚችል ነው፡፡ መሬቱ እንደሆነ የትም አልሄደም፤ ሊሄድም አይችልም፤ እዚያው ከነበረበት ነው ያለው፡፡ ሕዝባችንን ግን ከነበረበት እያገኘነው አይደለንም፡፡ በዚህ ዓለም ድጋሚ ላናገኘው አግባብ በሌለው አኳኋን በየቀኑ እየተሰናበተን ነው፡፡ አሁን ጥያቄው ምን እናድርግ? ነው፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ክቡራን እንግዶቻችን፤

ዛሬ ተሰብስበን የምንነጋገረው ስለ ሰበካ ጉባኤ ነው? ወይስ ስለመልካም አስተዳደር? ሕዝቡ ከሌለ እኮ ሃይማኖቱም፣ ገቢውም፣ አስተዳደሩም ነገ ሊቆም ይችላል፡፡ እዚህም እዚያም በየቀኑ እንደቅጠል እየረገፈ ያለው እኮ በመስቀላችን ያጠመቅነው፣ ማዕተበ ክርስትና ያሰርንለት፣ ለእግዚአብሔር መንግሥት አጭተን ያዘጋጀነው፣ ቤተ ክርስቲያንን ተረክቦ ሊያስቀጥልልን ዐይናችንን የጣልንበትና ተስፋም ያደረግንበት ልጃችንና ወገናችን ነው፡፡ ዝም ብሎ ማየቱ አያስጠይቅም ትላላችሁ?

እኛ ግን በእግዚአብሔርም፣ በሰውም፣ በታሪክም፣ በሞራልም ያስጠይቃል ብለን እናምናለን፡፡ በዚህ ውስጥ እየተሳተፋ ያሉ ሁሉም ልጆቻችን ናቸው፡፡ የተጣሉበትንም ነገር በውል ማወቅ አንችልም፡፡ ነገር ግን አንድ ነገር እናውቃለን፤ እሱም ሁሉም የኛ ልጆች መሆናቸውን እና ሁሉም ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ነው፡፡ በመሆኑም ከነዚህ ውስጥ አንድስ እንኳ እንዲሞትብን ወይም እንዲጐድልብን አንፈልግም፡፡ ሁሉም በሕይወት፣ በሰላምና በጤና እንዲኖሩልን እንሻለን፡፡

ፍጅትና እልቂት ይጐዳናል እንጂ ማናችንንም አይጠቅምም፡፡ እስካሁን ጦርነት ይጠቅማል ብሎ ሲናገር የሰማነው አንድ ስንኳ የለም፡፡ ታድያ ለማይጠቅም ነገር ለምን እንለፋለን? ከኛ ውጭ ያለው ዓለም ግጭቱ ቆሞ ሰላማዊ ውይይት ይካሄድ ሲል፣ መንግሥትም ሲቀበል፣ በሌላ በኩል ያለው ወገናችንም ሲቀበል፣ እኛስ ይሄንን ደግፈን ድምፃችንን ለሕዝባችን፣ ለመንግሥት እና ለሰላም እየተጋ ላለው የዓለም ዐቀፍ ማበረሰብ ብናሰማ ተገቢ አይደለምን? ይህንን በተመለከተ የነገሩን አሳሳቢነት ከልብ ተገንዝቦ ይህ ጉባኤ የሚለው ነገር እንዲል እንጠብቃለን ፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ክቡራን እንግዶቻችን!!

መቼም “እምነ ረኃብ ይኄይስ—-” እንደተባለው ሞትም ቢሆን እየበሉ ቢሆን ነውና የሚሻለው፣ በሰበካ ጉባኤ ሕገ ደንባችን መሠረት የቤተ ክርስቲያናችንም ሆነ የሀገራችን ምጣኔ ሀብትን የማሳደግ፣ የመጠበቅና ፍትሓዊ የሆነ የሀብት ክፍፍል ማረጋገጥ የኛ ሌላኛው ተልእኮ ነው፡፡

ሰበካ ጉባኤ የተቋቋመውም ለዚህ ተብሎ እንደሆነ ሁላችሁም ታውቃላችሁ፤ ጠቃሚ ውጤቱም በተጨባጭ እየታየ ነው፡፡ ነገር ግን፡-

• የሰበካ ጉባኤ አመሠራረትና ጒዞው፣
• አሁን ያለበት ደረጃ ትክክል ነው ወይስ የሚቀረው አለ?
• የቀረው ካለስ ለምን አናስተካክለውም?
• ለወደፊትስ የሰበካ ጉባኤ ሀብተ በረከት እንደሚፈለገው በፍጥነት አድጎ ለሕዝቡ ተደራሽ እስከ መሆን ለምን አናደርሰውም? በሚል ትክክለኛና ሙያዊ ጥናት ተካሂዶ ለዚህ ጉባኤ ማቅረብ የሚቀርብን ይመስለናል፡፡

ይህ ነጥብ ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅና ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ በሁለቱም ጉባኤያት እንድናየው ቢደረግ መልካም ይመስለናል፡፡ ምስጋና ይድረሳቸውና ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስና ከጎናቸው የነበሩ ሊቃውንት አባቶች ለሰበካ ጉባኤ መመሥረትና ሥር መስደድ እስከ ሕይወት መሥዋዕትነት እንደከፈሉ ይህ ጉባኤ መርሳት የለበትም፡፡ የእነርሱ ክብርና ሕያው ታሪክ መጠበቅ ያለብን በጽሑፍና በንግግር ብቻ ሳይሆን የሰበካ ጉባኤ ዐላማ ሙሉ በሙሉ ግቡን መትቶ ቤተ ክርስቲያን ከገጠር እስከ ከተማ ራሷን ስትችል፣ ከዚያም አልፋ ተርፋ በየቤተ ክርስቲያኑ የአብነት ት/ቤቶችና የዘመናዊ ት/ቤቶች በብዛትና በጥራት ተከፍተው፣ የሕዝበ ክርስቲያኑ ልጆችንና ሌሎችንም አቅፋ ስታስተምር፣ ዕጓለ ማውታና አረጋውያን ስትጦር፣ ሕሙማንን ስትፈውስ በአጠቃላይ የሕዝበ እግዚአብሔር እናትነትዋን በሚገባ ስትወጣ በማሳየት ሊሆን ይገባል፡፡ እስካሁን ባለው እንቅስቃሴ በቅጡ ባይያዝም ከገቢ አንጻር በከተሞች አካባቢ የተሻለ የሰበካ ጉባኤ ሀብተ በረከት ይታያል፡፡

እሱም ቅዱሱ ሕዝበ እግዚአብሔር በሙዳየ ምጽዋት ከሚያኖረው በረከት እንጂ፣ አስተምረንና ተከታትለን፣ ቀስቅሰንና አሳምነን በቃለ ዐዋዲው መሠረት አስተዋፅኦውን እንዲከፍል አድርገን እንዳልሆነ ጥቆማ ይደርሳል፡፡ በገጠርም በተመሳሳይ ሁኔታ ኮታ እየተጣለ የሚሰበሰብ እንጂ እያንዳንዱ ምእመን አስተዋፅኦውን በትክክል እንዲከፍል እያደረግን እንዳልሆነ ይሰማል:: ከዚህም ጋር በየመንገዱ የሚንጠባጠበው በዚያው ልክ እንደ ሆነ ይደመጣል፡፡ ታድያ እንዲህ ሲሆን ዝም የምንል ከሆነ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ መንፈስ አይወቅሰንም? ለምንስ እንወቀሳለን? ጉባኤው ከተቀበለን አሁን አጥብቀን የምናሳስበው የሰበካ ጉባኤ ጉዛችን ምን እንደሚመስል በባለሙያዎች በትክክል ቢጠናና ቢገመገም፣ ከዚያም አይተነው ወደ ተሻለ የእድገት ጒዞ ብንራመድ እንላለን፡፡ ምክንያቱም አንድ ሥራ በየጊዜው እየተገመገመ፣ እየታረመና እየተስተካከለ ካልተሠራ የሚቀረው ነገር አይታጣምና ነው፡፡

ከዚህ በተረፈ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ቡራኬ ሰጭነትና መሪነት ደጋውን ወጥታችሁ፣ ቈላውን ወርዳችሁ ቤተ ክርስቲያንን በመጠበቅ አገልግሎቷን በማስቀጠል ሁላችሁም የቤተ ክርስቲያናችን ተጠሪዎች ላደረጋችሁት የላቀ አስተዋፅኦ ከፍ ያለ ልባዊ ምስጋናችንን እናቀርብላችኋለን፡፡

በመጨረሻም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አርባ አንደኛውን ዓለም ዐቀፍ አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በዛሬው ዕለት በእግዚአብሔር ፈቃድ የከፈትን መሆኑን ለሕዝበ ክርስቲያኑ እናበሥራለን፡፡

እግዚአብሔር የተባረከና የተቀደሰ ጉባኤ ያድርግልን፤
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ፤
ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32022-10-17 14:55:072025-01-28 14:56:06ጥቅምት 7 ቀን 2015 ዓ.ም 41ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: መስከረም 16 ቀን 2015 ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል የቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: መስከረም 16 ቀን 2015 ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል የቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ መስከረም 16 ቀን 2015 ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል የቅዱስነታቸው... Link to: ጥቅምት 12 ቀን 2015 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ጥቅምት 12 ቀን 2015 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ጥቅምት 12 ቀን 2015 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top