• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

መስከረም 16 ቀን 2015 ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል የቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

“ወንስእለክሙ በክርስቶስ ከመ ታሥምርዎ ለእግዚአብሔር፤
ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን በክርስቶስ እንለምናችኋለን” (2ቆሮ. 5፥20)

ይህ አረፍተ ነገር ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እግዚአብሔር ዓለሙን በክርስቶስ እንዴት እንደታረቀው ባመሠጠረበት መልእክቱ የዕርቅን አስፈላጊነት አስመልክቶ የተናገረው ነው፤ ሁላችንም እንደምናውቀው እግዚአብሔር ፍጥረታትን ሲፈጥር መልካም አድርጎ እንደፈጠራቸው ቅዱስ መጽሐፍ ይገልጽልናል፤ ይሁንና እግዚአብሔር ፍጥረታትን ውብ አድርጎ ቢፈጥርም ከፍጥረታት መፈጠር ብዙም ሳይቈይ መጋጨትና አለመግባባት ሊጀመር ችሎአል፤ በመሆኑም የፍጥረታት መጋጨት በሰው ልጆች ብቻ ሳይሆን በሕያዋን ፍጥረታት ሁሉ በአራዊቱም ሆነ በእንስሳቱ፣ በአዕዋፉም ሆነ በዓሣው፣ በጥቃቅኑም ሆነ በግዙፋኑ ሲፈጸም ማየት የዕለት ተዕለት ክሥተት ሆኖ ቀጥሎአል፡፡

ይህም ሊሆን የቻለው ቀደም ሲል ሳጥናኤል የተባለው መልአክ ቀጥሎም በእግዚአብሔር መልክና አምሳል የተፈጠረው አዳም በፈጸሙት ጥፋት ሲረገሙና ሲቀጡ፣ ፍጥረታትም አብረው የመርገሙና የቅጣቱ ተሸካሚ ለመሆን ስለተገደዱ ነው፡፡ ምክንያቱም አምላካችን እግዚአብሔር አዳምን በመርገም በቀጣበት ቀን “ርግምተ ትኩን ምድር በእንቲኣከ፤ ምድር በአንተ ምክንያት የተረገመች ትሁን” ብሎ ምድርን ሲረግማት እንመለከታለንና ነው፡፡ ይህም ማለት አዳም ሲረገም ልጆቹ ሁሉ አብረው ተረግመዋል፣ ምድር ስትረገምም በውስጧ ያሉ ፍጥረታት ሁሉ አብረው ተረግመዋል ማለት ነው፡፡

ከመርገመ አዳም አንዱ “ሦክ ወአሜከላ ይውጋእከ እሾኽና አሜከላ ይውጋህ” የሚል ይገኝበታል፤ ይህ አገላለፅ ቅኔያዊ አገላለጽ ነውና በቁሙ እሾኽና አሜከላ ሳይሆን ጠቡንና ፍጅቱን ጨምሮ በአጠቃላይ በሰው ልጆች የሚደርሰውን መንፈሳዊና ሥጋዊ መከራን ሁሉ የሚያመለክት ነው፡፡ ይህም በመሆኑ ይኸውና ዛሬም ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ ፍጥረታት በሙሉ እርስ በእርስ ሲጣሉና ሲተረማመሱ ማየት ቀዋሚ ትዕይንት ሆኖ ይገኛል፤ ይሁንና ምንም እንኳ ችግሩ በፍጥረታት ሁሉ ላይ ሰፍኖ ቢገኝም መፍትሔ የሌለው ችግር ግን አይደለም፡፡

በየጊዜው በተግባር የተፈተነ ጠንካራና የማያወላውል መፍትሔው ይቅርታና ዕርቅ ነው፣ ለሰው ልጅ አለመግባባትን በዕርቅ ዘግቶ ሰላምንና አንድነትን መሥርቶ በመከባበርና በመተሳሰብ በመተዛዘንና በመተጋገዝ በመረዳዳትና በመቻቻል በፍቅርና በሰላም ከመኖር የተሻለ ሌላ አማራጭ የለውም፡፡ ይህም እውን ሊሆን የሚችለው ለኔ ለኔ የሚል የራስ ወዳድነትን አስተሳሰብ የሙጥኝ ብሎ በመያዝ ሳይሆን ለወንድሜ ለእኅቴ የሚል ቅን አስተሳሰብ አንግቦ ያም ባይሆን ለሁላችን የሚል የጋራ አስተሳሰብ በሰዎች ልቡና የበላይነት ሲያገኝ ነው፤ ከዚህ አንጻር መስቀላዊ የሆነ ንጻሬ በተላበሰ በዚህ የዕርቅ መንፈሳዊ ኀይል ጠብ ሲሸነፍ ብዙ ጊዜ አይተናል፡፡ በዕርቅ ላይ የተመሠረተ ይህ ዐይነቱ የችግር መፍትሔ በፈጣሪ ሕግም በዓለማዊ ሕግም በሞራላዊ ሕግም ፍጹም ተቀባይነት ያለው እንደሆነ የሚክድ ይኖራል ብለን አንገምትም።

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤

ሰው በጥንተ ፍጥረት ከፈጣሪ የተሰጠው የፈለገውን የመምረጥ ሙሉ ነፃነት ያለው ታላቅ ፍጡር ከመሆኑ የተነሣ በነፃ ምርጫው እንደተሰነካከለ ሁሉ ዛሬም በነፃ ምርጫው የመስተካከል ዕድልን እግዚአብሔር አልነፈገውምና ጠብን በዕርቅ፣ በደልን በይቅርታ፣ ድህነትን በልማት፣ ክሕደትን በሃይማኖት፣ እያረመ መኖር ይችላል፤ ሰው ራሱን በራሱ ካላሰነፈ በስተቀር ይህንን ለማድረግ ዐቅሙም ችሎታውም አለው፡፡

የሰው ልጅ ችግሮችን መፍታት የሚያስችለው ብቸኛ መፍትሔ ይቅርታና ዕርቅ ብቻ እንደሆነ ካለፈውም ካለውም የሰው ልጅ ታሪክ መረዳት አያዳግትም፣ ሰው ይቅርና እግዚአብሔርም ከሰው ጋር የነበረውን ጥልና መለያየት ያስወገደው በዕርቅና በይቅርታ ነው፤ ያውም የተበደለው እሱ ሆኖ ሳለ ለበደለው ፍጡር ሲል ቤዛ ሆኖ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ “የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” በማለት ሰውን ይቅር ማለቱ የይቅርታ ዋጋ በእግዚአብሔር ዘንድ ምን ያህል ተቀባይነትና ተፈላጊነት እንዳለው በጒልሕ አሳይቶአል፡፡ ይህንን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ነገረ መስቀልን በውል የተረዳ ፍጡር ይቅርታ ተጠይቆ ይቅርና በራሱ ተነሣሽነት ወደ በዳዩ ወገን ፈጥኖ በመሄድም ሆነ ይቅርታን በመስጠት ዕርቅን መፈጸም ተራራ አይሆንበትም፤ ችግሩ የሚከሠት ያለው የነገረ መስቀሉን ምሥጢር በጥልቀት ካለማወቅ የተነሣ ወይም ቢታወቅም በተሸናፊው የእልከኝነት መንፈስ በመሸነፍ ነው፤ ከዚህ አንጻር የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ነን የምንል ሁላችን ዕርቅንና ይቅርታን ቸል የምንል ከሆነ ከምሥጢረ መስቀሉ መራቃችንን፣ ለኀጢአትም መንበርከካችንን ልብ ብለን ልናስተውል ይገባል፡፡ ኀጢአት ደግሞ ጕዳትን እንጂ የሚያመጣልን አንዳችም ጥቅም እንደሌለ መገንዘብ ያሻል፤ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናችኋለን” ብሎ እነሆ በዛሬው ዕለት ሁላችንንም ይለምነናል፡፡

የሐዋርያው ጭብጥ መልእክት ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ” የሚል ነው፤ ይሁንና ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ማለት ምን ማለት እንደሆነ አንዳንዶቻችን ላንገነዘበው እንችላለን፤ ይህንን በተመለከተ ቅዱስ መጽሐፍ ሲያስተምር ከወንድም ጋር መታረቅ ማለት ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ማለት ነው ይለናል፡፡ ከዚህ አኳያ ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ የምንችለው ከወንድማችን ጋር ስንታረቅና ስንዋደድ እንደሆነ ሐዋርያው አበክሮ ያስተምራል፤ ለዚህም ነው ቅዱስ መጽሐፍ “በአጠገቡ ያለውን ወንድሙን የማይወድ እግዚአብሔርን እወደዋለሁ የሚል ሐሰተኛ ነው፤ በአጠገቡ ያለ የሚያየውን ወንድሙን ሳይወድ የማያየውን እግዚአብሔርን እንዴት ይወደዋል? በማለት የሚያስተምረን፣ ጌታችንም ይቅር ካላችሁ ይቅር ይባልላችኋል፤ ይቅር ካላላችሁ ግን ይቅር አይባልላችሁም ብሎ አስተምሮናል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤

እንግዲህ የመስቀልን በዓል በምናከብርበት በዚህ ቀን ከመስቀሉ መገኘት ባሻገር ማስታወስና ማሰብ ያለብን መስቀሉ ከእኛ የሚፈልገው ምንድን ነው? የሚለውን ነው፤ ትልቁ ቁም ነገርም እሱ ነው፤ የመስቀሉ ዐቢይ መልእክት በሰው ልጆች መካከል ፍጹም ሰላምና ፍቅር አንድነትና እኩልነት ይቅርታና ዕርቅ ምሕረትና አዘኔታ በምልአት ሰፍኖ፣ የሰው መንፈሳዊ፣ ሞራላዊና አካላዊ ህላዌውና ጤንነቱ ያለምንም እንከን ተጠብቆ እንዲኖር ነው፤ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ለዓለም ቤዛ እንዲሆን ሲሰጥ ፈቃዱ ይህ እንዲሆን ነው፡፡

ክርስቲያኖች ብሎም የዓለም ሕዝቦች ይልቁኑም የሃይማኖት መናኻሪያ በሆነችው በቅድስት ሀገር በኢትዮጵያ የምንኖር ክርስቲያኖችና ሃይማኖታውያን በሙሉ ይህንን የእግዚአብሔርን ፈቃድ የማወቅና የማመን የመቀበልና የመተግበር ሃይማኖታዊ ግዴታ አለብን፤ እግዚአብሔርን እናመልካለን ለሱም እንታዘዛለን ኢትዮጵያንም እንወዳለን ብለን የምንመሰክር ከሆነ የምናከናውነው ተግባር በሙሉ የእግዚአብሔርን ፈቃድና የመስቀሉን ምሥጢር የጠበቀ ሊሆን ይገባል፡፡

የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ የምንሻም ከሆነ ባለፉት ዘመናት የሆነውን ነገር ሁሉ እንደገና ከልብ በማጤንና ሰከን ብለን በማስተዋል ወደ እግዚአብሔር መለስ ብለን እሱን ማዳመጥ አለብን፤ እግዚአብሔር ሁል ጊዜ ይናገራል፤ ለሰው ልጆች ሁሉ የሚሰማና ግልጽና ግልጽ የሆነ ቋንቋም አለው፤ እሱም ታረቁ፤ ይቅር ይቅር ተባባሉ፤ እናንተ ይቅር ስትሉ እኔም ይቅር እላለሁ፤ እንደዚሁም በረከቱንና ልማቱን አብዝቼ እሰጣለሁ፤ የምድሩን ብቻ ሳይሆን የሰማዩንም አትረፍርፌ እሰጣለሁ የሚል ነው፤ ይህንን የእግዚአብሔር ድምፅ ያልሰማ ሰው በዓለም ይኖራል ብለን አንገምትም፤ ድምፁን ሰምቶ ጆሮ ዳባ ልበስ በማለት የሚኖር ግን ብዙ ሊሆን ይችላል፤ የእኛም የዕለቱ መልእክት ሐዋርያው እንደተናገረው ከእልከኛ አስተሳሰብ እንውጣና የእግዚአብሔርን ድምፅ እንስማ እንቀበል እናክብርም በተግባርም ፈጽመን እናሳይ የሚል ነው፡፡

በመጨረሻም እግዚአብሔር ግጭቱን አስወግዶ ሰላሙን ፍቅሩን፣ አንድነቱንና ስምምነቱን እንዲያመጣልን፤ እኛም የዕርቅና የይቅርታ ሰዎች ሆነን እንገኝ ዘንድ በርትተን እንድንጸልይ አባታዊና መንፈሳዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር መልካም የመስቀል በዓል ያድርግልን
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32022-09-26 14:26:162025-01-28 14:27:24መስከረም 16 ቀን 2015 ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል የቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: መስከረም 1 ቀን 2015 ዓ.ም ርዕሰ ዐውደ ዓመት የዘመን መለወጫ በዓል መግባትን አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ Link to: መስከረም 1 ቀን 2015 ዓ.ም ርዕሰ ዐውደ ዓመት የዘመን መለወጫ በዓል መግባትን አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ መስከረም 1 ቀን 2015 ዓ.ም ርዕሰ ዐውደ ዓመት የዘመን... Link to: ጥቅምት 7 ቀን 2015 ዓ.ም 41ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ Link to: ጥቅምት 7 ቀን 2015 ዓ.ም 41ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ ጥቅምት 7 ቀን 2015 ዓ.ም 41ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top