• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ጥር 11 ቀን 2008 ዓ.ም የበዓለ ጥምቀት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ክቡራን አምባሳደኖችና ኮር ዲፕሎማቶች፣ የተከበራችሁ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የተወደዳችሁ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች፣ በአጠቃላይ በዚህ ዐቢይ በዓል የተገኛችሁና በየአካባቢው ሆናችሁ በዓሉን በማክበር ላይ የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ በማየ ጥምቀት አማካኝነት ሀብተ ጽድቅንና ሀብተ መንፈስ ቅዱስን ያደለን እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ስምንት ዓመተ ምሕረት በዓለ ጥምቀተ ክርስቶስ በሰላም አደረሳችሁ፡፡

‹‹ወይደልወነ ከመ ንፈጽም ኵሎ ጽድቀ
እንግዲህ ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናል።››
(ማቴ.3፡15)

ከሁሉ በፊት በዓለ ጥምቀቱን ስናከብር ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተጠመቀበት ዕለት በቃልም ሆነ በድርጊት የፈጸማቸውንና ያስተማራቸውን ነገራተ ጽድቅ ሁሉ በልዩ ተመስጦና አንክሮ በማስታወስ ልናከብር ይገባል፡፡ ጌታችን በዚህ ቀን ከተናገራቸው ዐበይት ነገሮች አንዱ ‹‹ጽድቅን ሁሉ ልንፈጽም ይገባናል›› የሚለው ቃል ነው፤ ይህ መለኮታዊ ቃል ሰዎች በጥምቀት ሱታፌነት የእግዚአብሔርን ጽድቅ የሚያገኙበት ከመሆኑ አንጻር የማይታለፍ ጉዳይ እንደሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዮሐንስ አስረግጦ የተናገረው ኀይለ ቃል በመሆኑ የበዓሉ ዐቢይ ርእሰ – ትምህርት ነው፡፡ በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው ምግባረ ጽድቅ በሰማያውያኑም ሆነ በምድራውኑ ፍጡራን እንዲሁም በሥራዎቻቸው ሁሉ እጅግ አስፈላጊ ናት፤ ነገሮች ፈራቸውን ለቀው ወደመተረማመስ፣ ወደ ዐመፅ፣ ወደ ግጭት፣ ወደ ክፋት፣ ወደጭካኔ፣ ወደ ፍርድና ቅጣት እንዲያመሩ የሚገደዱበት ዋና ምክንያት ጽድቅ ስትዘነጋ ነው ፡፡

ጽድቅ የእግዚአብሔር ባሕርይ መገለጫ፣ የሥራውና የፍርዱ መለኪያ ሚዛን ናት፤ የውሳኔውም ቀዋሚ ድንበር ናት፤ ጽድቅ ከእግዚአብሔር ባሕርይ ውጭ የሆነች ባዕድ ነገር ሳትሆን፣ የባሕርይ ገንዘቡ ሆና የኖረችና የምትኖር ናት፡፡ ፍጡራን ከጽድቅ መንገድ ሲወጡ ከእግዚአብሔር ጋር ያላቸውን ግንኙነት ሁሉ ይቋረጣል ወይም ይቆማል፤ ፍጡራን ከጽድቅ መንገድ ሲወጡ ጽድቅ ራስዋ ትወቅሣቸዋለች፣ ካልተመለሱም ትፈርድባቸዋለች፣ ትቀጣቸውማለች፡፡ ጽድቅ የእግዚአብሔር ባሕርይ መገለጫና የፍርዱ መሣሪያ ስለሆነች ከእርሱ ተነጥላ አትታይምና ክፉውን ሁሉ ትጠላለች፤ እስከ መጨረሻም ትዋጋለች እንጂ፣ ከክፉ ነገር ጋር አትተባበርም፤ ፈጽማም አትስማማም፡፡

ፍጡራን ከጽድቅ ጋር ሲጣሉ ከእግዚአብሔር ጋር በቀጥታ ይጣላሉ፤ ለዚህ አስረጅ የሚሆኑ ብዙ ፍጡራን አሉ፤ በተለይም ከቀዳማውያን ፍጡራን ወገን የሆነው መልአክ እርሱም ሳጥናኤል ‹‹ወሐሰት ርእሰ ዐመፃ፤ ሐሰት የዐመፅ ሁሉ ራስ ናት›› ሲል ቅዱስ መጽሐፍ እንደተናገረ የዐመፅ ሁሉ ራስ የሆነችው ሐሰትን መርጦና ወዶ ከጽድቅ ጋራ በተጣላ ጊዜ በቀጥታ ከእግዚአብሔር ጋር ተጣልቶአል (መዝ. 26፥12፤ ዘፍ. 3፥1-16፤ ማቴ. 4፥10፤)፡፡ ከጽድቅ ጋር መጣላት ከእግዚአብሔር ጋር መጣላት እንደመሆኑ መጠን ከቅጣት ማምለጥ አይቻልምና ጽድቅ ራስዋ አጥፊን የመቅጣት ኀላፊነት ስላለባት አጥፊውን ፍጡር እርሱም ሳጥናኤልን ቀጥታለች፤ (ዘፍ. 3፡14፤ ቈላ.2፡15፤ ራእ. 12፡9፤)፡፡

ከጽድቅ ጋር የተጋጨ ሌላው ፍጡር የሰው ሁሉ አባት የሆነው አዳም ነው፤ እግዚአብሔር ጻድቅ ነውና የሚሰጠው ትእዛዝ ሁሉ ከጽድቅ ጋር የሚስማማ እንጂ የሚቃረን አይደለም፡፡ በመሆኑም አዳም ያለ ዐቅሙ አምላክነትን ሽቶ ከእግዚአብሔር የተሰጠውን የጽድቅ ትእዛዝ ስለተላለፈ ጽድቅ ወቀሠችው፤ ፈረደችበት፤ ቀጣችውም፤ በዚህም ምክንያት አዳም ከጽድቅ ጋር በመጋጨቱ እርሱም፣ ልጆቹም በአጠቃላይ ተቀጡ፤ (ዘፍ. 3፥16-24፤ ሮሜ 5፥12-14)፡፡ ነገር ግን ጽድቅ አስተዋይ ናትና በጭፍን ሳይሆን በትክክል ትፈርዳለች፤ ጽድቅ የሳጥናኤልና የአዳም ጥፋት ልዩነት እንዳላቸው አልዘነጋችም፤ ጽድቅ የሳጥናኤል ኀጢአት ሌላ አሳሳችና ገፊ ሳይኖረው በራሱ ነፃ ምርጫና ፍላጎት በሐሰት የፈጸመው ከባድ ጥፋት እንደሆነ ታውቃለች፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሳጥናኤል ወይም በግሪክ ስሙ ዲያብሎስ የስሕተት የአመፅና የሐሰት ምንጭ መሆኑን ሲገልጽ ‹‹እውነት በእርሱ ስለሌለ በእውነት አልቆመም፤ ሐሰትን ሲናገር ከራሱ ይናገራል፤ ሐሰተኛ የሐሰትም አባት ነውና›› ብሎአል፤ (ዮሐ. 8፥44)፡፡ በሌላ በኩል አዳም ጥፋትን ሊፈጽም የቻለው እንደ ዲያብሎስ ከራሱ አንቅቶ ወይም ሆን ብሎ ሳይሆን አምላክ ትሆናለህ በሚል ቅስቀሳ በዲያብሎስ ተገፋፍቶ እንደሆነ በግልጽ ተቀምጦአል፤ (ዘፍ.3. 1-5 ራእ.12፡9)

ስለሆነም የአዳም ጥፋት ከዲያብሎስ ጥፋት የተለየ በመሆኑ በምሕረት እንደሚታይ ጽድቅ ራስዋ ተስፋን ሰጠች፤ ተስፋውም ጽድቀ እግዚአብሔርንና ፍትሐ እግዚአብሔርን በማይቃረን መልኩ እንደሚፈጸም በረጅሙ አናገረች (ዘፍ. 3፥15፤ 22፥17፤ ኢሳ. 53፥፡11፤ ኤር. 23፥5-6)፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚነግሩን ጻድቅ ሳይሆኑ ጻድቅ ከሆነው እግዚአብሔር ጋር መገናኘት አይቻልም፤ (2ቆሮ.6፡14-16፤ ሮሜ.3፡20-24)፡፡

በመሆኑም ሰው ወደ እግዚአብሔር ሊቀርብ የሚችለው ጽድቅን ሲያገኝ ብቻ ነው፤ በዚህ ውስጥ መሠረታዊ ጥያቄ ሆኖ ሊነሣ የሚችለው ዐቢይ ነገር ሰው እንዴት ጽድቅን አግኝቶ ጻድቅ ሊሆን ይችላል? የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ ለዚህ ጥያቄ መልስ አለው፤ ይኸውም ሰው ጽድቅን ሊያገኝ የሚችለው በዋናነት ከእግዚአብሔር በሚያገኘው ወይም በሚሰጠው ጸጋ እንጂ በራሱ ጥረት ብቻ አይደለም የሚል ነው፤ (ሮሜ 3፥21-22)፡፡ የደሴተ ቆጵሮስ ኤጲስ ቆጶስ የነበረው ሊቁ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ በቅዳሴው ይህንን አስመልክቶ ሲናገር “ወሶበ ርእየ ከመ ኢበቊዐ ለአድኀኖ ዓለም ደመ ኵሎሙ ነቢያት ዘተክዕወ ዲበ ምድር እምደመ አቤል ጻድቅ እስከ ደመ ዘካርያስ ወልደ በራክዩ ፈነወ ለነ ወልዶ መድኅነ ማለትም ከጻድቁ አቤል ደም ጀምሮ እስከ በራክዩ ልጅ እስከ ዘካርያስ ድረስ በምድር ላይ የፈሰሰው የነቢያት ሁሉ ደም ዓለምን ለማዳን ወይም ለማጽደቅ እንዳልበቃ ባየ ጊዜ አዳኝ የሆነው ልጁን ላከልን” ብሎአል፡፡

ከዚህ አንጻር ከጽድቀ እግዚአብሔር በስተቀር ሌላ ማጽደቂያ ያልተገኘለት የሰው ልጅ የእርሱ ጽድቅ ለእኛ ተቈጥሮልን በእርሱ የጽድቅ ስጦታ ጻድቃን እንሆን ዘንድ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለመሥዋዕትነት ተሰጠን፤ (2ቆሮ. 5፥21)፡፡ በእርሱ መሥዋዕትነት በተገኘው ቤዛነት የእርሱ ሕይወት ለእኛ ተሰጠ፤ የእኛ ሞት ደግሞ ለእርሱ ሆነ፤ የምሥራቃውያን ዐምደ ሃይማኖት የሆነው ሶርያዊው ሊቅ ቅዱስ ኤፍሬም ይህንን ሲገልጽ ‹‹ዘዚኣነ ሞተ ነሥአ ወእንቲኣሁ ሕይወተ ወሀበነ፤ የእኛን ሞት እርሱ ተቀበለ፤ የእርሱን ሕይወት ደግሞ ለኛ ሰጠን›› ብሏል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹ወበእንተ ኀጣውኢነ ውእቱ ተሰቅለ ዲበ ዕፅ በሥጋሁ ከመ ያውጽአነ እም ኃጣውኢነ ወበጽድቁ ያሕይወነ፤ ማለትም እርሱ ስለ ኀጢአታችን በዕንጨት ላይ በሥጋው ተሰቀለ፤ ከኀጢአታችን ነፃ ያወጣን ዘንድ፣ በእርሱ ጽድቅም ያድነን ዘንድ ብሎአል›› (1ጴጥ. 2፡24)፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ‹‹አነ ውእቱ ፍኖተ ጽድቅ ወሕይወት፣ የሕይወትና የጽድቅ መንገድ እኔ ነኝ፤ በእኔ የሚገባ ይድናል›› ብሎአል፤ (ዮሐ.14፡6) መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹ጸጋሰ ወጽድቅ በኢየሱስ ክርስቶስ ኮነ፤ ጸጋና ጽድቅ በኢየሱስ ክርስቶስ ሆነ›› በማለት ያረጋገጠው ይህንኑ ነው፤ (ዮሐ. 1፥17)፡፡ እንግዲህ ሰው ጽድቅን ሊያገኝ የሚችለው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በሆነው ቤዛነት እንደሆነ በዚህ ሁሉ እንገነዘባለን፤

የጽድቅ መገኛው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቢሆንም ለሰው ሊሰጠው የሚችል በሱታፌ ሃይማኖት ወምግባር እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ይናገራሉ፤ ጌታችን ሊጠመቅ ወደ ዮሐንስ በመጣ ጊዜ ‹‹ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናል›› ሲል የተናገረው ቃል በሱታፌ ጥምቀት ምክንያት የሚገኘው ጽድቀ እግዚአብሔርን ሲያመለክት ነበረ፡፡ ጽድቀ እግዚአብሔር በአንድ ጊዜ ተሰጥቶ የሚጠናቀቅ ሳይሆን በጥምቀት ተጀምሮ በእግዚአብሔር ጸጋና በሰው ሱታፌ እያደገ ሄዶ በዳግም ምጽአተ ክርስቶስ በግልጽ የሚታይና የሚፈጸም ነው፡፡ ጌታችን ጽድቅን ሁሉ መፈጸም ይገባናል ማለቱ እርሱ በመምህርነትና በመሪነት፣ ሰው በተጠምቆ ሱታፌነት፣ እግዚአብሔር አብ በጽድቅ ሰጪነት እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስም በአንጽሖና በአክብሮ፣ የሚገናኙበት የጽድቅ መንገድ ምሥጢረ ጥምቀት መሆኑን ሲያመለክት ነው ፡፡

ሰው ከመጠመቁ በፊት ጽድቅን አያገኝም፤ አይሰጠውምም፤ ምክንያቱም ኀጢአተኛ ነውና፤ ነገር ግን ከጥምቀት በኋላ በተሳትፎ – ጥምቀት የእግዚአብሔርን ጽድቅ ይሰጠዋል፡፡ ከዚህ በኋላ የጽድቅ ሕይወት አንድ ብሎ ይጀምራል፤ በይቀጥላልም ሰው በሱታፌነቱ ከእግዚአብሔር ጋር ሆኖ በሃይማኖት ብቻ ሳይሆን በሥነ ምግባርም ጭምር ጽድቅን እያሰፋና እያሳደገ ከሠላሳ ወደ ስድሳ፣ ከስድሳ ወደ መቶ ደረጃ ያደርሳል፤ ከበዓለ ጥምቀት የምንማረው ዐቢይ ሃይማኖታዊ ትምህርት ይህ ነው (ማቴ.13፡23)፡፡ እዚህ ላይ ክርስቲያኖች ሁሉ ሊገነዘቡት የሚገባ ዐቢይ ነገር እግዚአብሔር በሁሉም ነገር አሳታፊ አምላክ መሆኑን ነው፤ እግዚአብሔር ምንም እንኳ የሚሳነው ነገር የሌለና ሁሉን የሚችል አምላክ ቢሆንም፣ በሥራው ሁሉ ፍጡራንን በአጠቀላይ፣ በተለይም ሰው የሥራው ተሳታፊ እንዲሆን በተፈጥሮ ሳይቀር ጸጋውን አብዝቶ ሰጥቶታል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ሕይወት ያላቸው ፍጡራን ሁሉ በዘር እንዲባዙ ማድረጉን እናውቃለን፤ ሆኖም መባዛት ያለተባትና እንስት ተሳትፎ እንዲሆን አላደረገውም፤ ቀጣይ የሆነ ዘር ወይም ትውልድ እንዲኖር የተባትና የእንስት ፆታዊ ተሳትፎ ወይም ውሕደት የግድ ያስፈልጋል፤ ይህ የሚያሳየው እግዚአብሔር በሥራው አሳታፊ አምላክ መሆኑን ነው፡፡ የሰው ጽድቅም ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነው፤ እግዚአብሔር ጽድቅን በጸጋው ቢሰጥም ያለሰው ተሳትፎ ግን የሚገኝ አይደለም፤ የእግዚአብሔርን ጽድቅ ለማግኘት ሰው የግድ ማመን አለበት፣ የግድ መጠመቅ አለበት፣ የግድ መቊረብ አለበት፣ የግድ በሥነ ምግባር አጊጦ መኖር አለበት፣ በሌላ አገላለጽ በሃይማኖትና በሥነ ምግባር ጸንቶ መኖር አለበት፣ ማለት ነው፤ ይህ ከሆነ ሰው በጽድቀ እግዚአብሔር ተሳትፎ አድርጎአል ማለት ነው፤ በመሆኑም ሰው በዚህ ብቻ ጻድቅ ሆኖ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ይችላል፡፡ በሃይማኖት ላይ የሥነ ምግባር ተሳትፎ ከሌለ ግን ጽድቅ የለም፤ ጻድቅ መሆንም አይቻልም፤ ሥነ ምግባር ከሌለ ሃይማኖቱ ራሱ የሞተ ይሆናል ማለትም ጽድቅን አያስገኝም ተብሎ ተጽፎአልና፤ ጽድቅም ከሌለ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ የለም ይህ ደግሞ የሞት ሞት ነው (ያዕ.2፡18-26፤ ማቴ25፤1-46)፡፡ በዚህ ክርስቶሳዊ አስተምህሮና ሐዋርያዊ ትውፊት መሠረት ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ነገረ ድኅነትን በተመለከተ ሃይማኖትና ሥነ ምግባር የማይነጣጠሉና የአንድ ሳንቲም ገጽታዎች እንደሆኑ በማስረገጥ ሰው ሃይማኖትና ሥነ ምግባርን ጠብቆ በመኖር ይጸድቃል ብላ ታስተምራለች ፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጽድቅን ሁሉ ለመፈጸም በፈለገ ዮርዳኖስ በእደ ዮሐንስ በተጠመቀበት ዕለት የተላለፈው መለኮታዊ ትምህርት ሰው ሃይማኖትንና ሥነ ምግባርን አንድ አድርጎ መያዝ እንዳለበት የሚያመለክት ነው፤ በዕለተ ጥምቀት ቃል በቃል የተላለፈው የእግዚአብሔር አስተምህሮ ‹‹ይህ ልጄ ነው፤ የሚላችሁን ስሙ›› የሚል ነው፤ (ማቴ3፡17፤ 17፡5)፤ ከዚህ መለኮታዊ ቃል እንደምንገነዘበው ‹‹ይህ ልጄ ነው›› የሚለው ኀይለ ቃል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር መሆኑን አምነን እንድንቀበል የሚያስገነዝብ ሲሆን ይዘቱ ሃይማኖትን ይመለከታል፤ (ዮሐ.1፡3)፤ ‹‹የሚላችሁን ስሙ›› የሚለው ቃል ደግሞ ሃይማኖትንና ሥነ ምግባርን የሚመለከት ሆኖ ጌታችን ‹‹በእኔ እመኑ፤ በአባቴም እመኑ፤ መልካም የሠሩ ወደዘለዓለም ሕይወት፣ ክፉ የሠሩ ግን ወደ ዘለዓለም ኵነኔ ይሄዳሉ›› በማለት ሃይማኖትንና ሥነ ምግባርን የጽድቅ ምሰሶ አድርጎ ያስተማረውን ሰምተን በተግባር እንድንፈጽም የሚያስገነዝብ ኀይለ ቃል ነው፤ (ዮሐ. 14፥1፤ 5፥29)፡፡

በመሆኑም ታላቁና ተወዳጁ የጥምቀት በዓላችን ዛሬ ስናከብር የሃይማኖትና የሥነ ምግባር ዋና መገለጫ የሆነውን ‹‹ፍቅረ እግዚአብሔርና ፍቅረ ቢጽን (ባልእንጀራ መውደድን)›› በሕይወታችን ዘመን ሁሉ በተግባር ለመፈጸም ቃል በመግባት ሊሆን ይገባል፡፡ እግዚአብሔርን መውደዳችንን የምንገልጸው ለቅዱስ ቃሉ ታዛዥ በመሆን ብቻ ነው፤ ባልጀራችንን መውደዳችን የምንገልጸው ደግሞ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ ‹‹ያለውን ለሌለው ያካፍል›› ብሎ ያስተማረውን በመቀበልና በተግባር በመፈጸም ባልንጀሮቻችንን እንደራሳችን አድርገን በመውደድ ነው፡፡ ዛሬ ብዙ ባልንጀሮቻችን የሚለብሱትና የሚጎርሱት፣ የሚጠጡትም ጭምር አጥተው በከባድ ችግር ላይ እንደሚገኙ እየሰማንና እያየን ነው፡፡ በመሆኑም ለነዚህ ባልንጀሮቻችን ወገናዊና ወንድማዊ የሆነ ድጋፍ ይዘን በወቅቱ በፍጥነት ልንደርስላቸው ይገባል፤ ይህም ሌላው የበዓለ ጥምቀት ዐቢይ አስተምህሮና ተቀዳሚ መልእክት ነው ፡፡

በዓለ ጥምቀት ተራራው ዝቅ ይበል፤ ጎድጓዳው ይሙላ፤ ሁሉም ትክክል ይሁን እያለ እኩልነትን፣ በደመወዛችሁ ኑሩ እንጂ ማንንም አትቀሙ እያለ ግብረ ሙስና መጸየፍን፣ ነፍስ ሁሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ይመልከት እያለ በሃይማኖት መዳንን፣ ለንስሓ የሚሆን ሥራ ሥሩ እያለ የሥራና የአእምሮ ልማትን፣ ግብር ሰብሳቢውም፣ ወታደሩም፣ ፈሪሳዊውም፣ ሌዋዊውም፣ ሕዝቡም ሁሉ በአንድነት በማገናኘት አንድነትን፣ የሰላም ምልክት በሆነች በነጭ ርግብ አምሳል መንፈስ ቅዱስን በመግለጽ ፍጹም ሰላምን ያስተማረን፣ የሃይማኖት፣ የልማት፣ የእኩልነት፣ የአንድነትና የሰላም መምህራችን ነው፡፡ ስለሆነም ጽድቀ እግዚአብሔርን በሃይማኖትና በሥነ ምግባር ተቀብለን፣ የልማት ሥራችንን አጎልብተን፣ የአንድነት፣ የሰላም፣ የእኩልነት፣ የመከባበር፣ የመተማመንና የወንድማማችነት ነባር ዕሤቶቻችንን ጠብቀን የተራቡ ወገኖቻችንን በማገዝና በመርዳት በዓሉን ልናከብር ይገባል፤ ጽድቅን ሁሉ ልንፈጽም ይገባናልና፡፡

በመጨረሻም፡ ጥምቀት ማለት በመንፈስ ቅዱስ መታደስ ማለት ስለሆነ በዓለ ጥምቀቱን ስናከብር ሀገራችንን በልማትና በሰላም – ሕዳሴ ለመገንባት የጀመርነው ሁለተኛው የእድገትና የትራንስፎርሜሽን መርሐ ግብር በተያዘለት አቅጣጫ በስኬት ለማጠናቀቅ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገር የሚገኙ መላ ኢትዮጵያውያን በሁሉም የሥራ መስክ በትጋትና በንቃት እንዲረባረቡ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ መልካም በዓለ ጥምቀት ያድርግልን ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32016-01-20 12:59:042025-01-28 13:00:15ጥር 11 ቀን 2008 ዓ.ም የበዓለ ጥምቀት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ታህሣሥ 28 ቀን 2008 ዓ.ም የበዓለ ልደት መልእከት፣ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ታህሣሥ 28 ቀን 2008 ዓ.ም የበዓለ ልደት መልእከት፣ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ታህሣሥ 28 ቀን 2008 ዓ.ም የበዓለ ልደት መልእከት፣... Link to: የካቲት 28 ቀን 2008 ዓ.ም የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: የካቲት 28 ቀን 2008 ዓ.ም የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ የካቲት 28 ቀን 2008 ዓ.ም የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top