• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 21 ቀን 2011 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡

አንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፣ አንድ ቅዱስ ሲኖዶስ

ከጥቅምት 11-21 ቀን 2011 ዓ.ም. የተደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በሀገር ውስጥና በውጭ ያለችው ቤተ ክርስቲያን በአንድ ቀኖናና ማእከል እንድትመራ ሲወስን፣ በቤተ ክርስቲያን፣ በካህናትና በምእመናን ላይ እየደረሰ ያለው ከፍተኛ ጥቃት በማውገዝ ጥቃቱ እንዲቆም መንግሥትን ጠይቋል፡፡ ይኽንንና ሌሎች ውሳኔዎችን በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት እንደሚከለተው አሰምተዋል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቍጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልአተ ጉባኤው የመክፈቻው ሥርዐተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከጥቅምት 11 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ጥቅምት 21 ቀን 2011 ዓ.ም ድረስ የተለመደውን ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ ሲያካሂድ ሰንብቶ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሚበጁ ውሳኔዎችን አሳልፎአል፡፡ በዚሁ መሠረት፤

1. ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በቀረበው አጀንዳ ተራ ቊጥር አንድ ላይ በተገለጸው የጉባኤ መክፈቻ ንግግር የተመዘገበው ፍሬ ሐሳብ የበጀት ዓመቱ መመሪያ ሆኖ ያገልግል ዘንድ ምልአተ ጉባኤው ተቀብሎታል።
2. የብፁዓን አባቶች የሥራ ምደባና ዝውውር በማስፈለጉ ቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን ሁኔታ ከመረመረ በኋላ ዝውውሩን አከናውኗል፤ አዲስ የሥራ ምደባም ተካሂዷል፡፡
3. በሀገራችን ኢትዮጵያ በአንዳንድ ክልሎችና ዞኖች ተከሥቶ የነበረው ኅልፈተ ሕይወት፣ የአብያተ ክርስቲያናት መቃጠልና የንብረት መውደም የዜጎች መፈናቀል ይገታ ዘንድ በመደጋገም የተላለፈው ጥያቄ በኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ መንግሥት በኩል ተቀባይነትን ያገኘ ቢሆንም፤ አሁንም በሀገሪቱ አንዳንድ ችግሮች እንዳሉ እየተሰማ ነው፡፡ ስለዚህ ከየአቅጣጫው እየተሰማ ላለው ችግር አስቸኳይ መፍትሄ ተፈልጎ እንዲገታ ካልተደረገ እየሰፋና እያደገ ሊሄድ ስለሚችል መንግሥት ከዐቅም በላይ እየሆነ ለሚታየው ችግር አጽንዖት ሰጥቶ አስፈላጊውን ሕጋዊ መፍትሄ እንዲገኝ በማድረግ ተገቢውን እንዲፈጸም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በድጋሚ ያሳስባል፡፡
4. የዘንድሮውን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ልዩ ታሪካዊ ጉባኤ ከሚያደርጉት መካከል፣ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አራተኛ ፓትርያርክ፣ አብረዋቸው ከነበሩት አባቶች ጋር ወደ እናት ሀገራቸው ኢትዮጵያ የመመለሳቸው ጉዳይ አንዱ እንደሆነ አያጠያይቅም፤
5. ለኢትዮጵያ ምእመናን ከኤርትራ ምእመናን፤ ለኤርትራ ቤተ ክርስቲያን ከኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን፣ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም የኤርትራ ቤተ ክርስቲያን የመፈቃቀርና የአንድነት እንዲሁም የበለጠ የክፉ ቀን ደራሽ ይኖራል ተብሎ አይገመትም፡፡ ስለዚህ በሁሉም መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ዘርፍ ተቀራርቦ እየሠሩ መረዳዳት ይቻል ዘንድ ከወዲሁ ሁኔታዎችን የሚያመቻች የጋራ ኮሚቴ እንዲቋቋም ምልአተ ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
6. በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የጸደቀው ሠላሳ ሰባተኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የጋራ መግለጫ በአፈጻጸም ዙሪያ የሚከሠት ችግር ካጋጠመው በቋሚ ሲኖዶስ እየተመረመረ ለውጤት ይበቃ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ተስማምቶ መመሪያ አስተላልፏል፤
7. በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን ኢትዮጵያ በአንዳንድ አካባቢዎች እየታየ ያለው የሰላም ዕጦት ችግር በቀላሉ የሚገታ ሆኖ ካልተገኘ ወደፊት አስቸጋሪ ሁኔታዎች ሊከሠቱ ይችላሉ የሚል ሥጋት አለ፤ ስለዚህ እንደ ቤተ ክርስቲያናችን ቀኖናዊ ሥርዐት የወንጌል ስምሪት ተዘጋጅቶ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ትምህርተ ወንጌል ተጠናክሮ እንዲሰጥ ሆኖ ከዚህም ጋር ከኅዳር 1 እስከ ኅዳር 7 ቀን 2011 ዓ.ም. ድረስ በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ጸሎተ ምሕላ እንዲደረግ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መመሪያውን አስተላልፎአል፤
8. በተቀረጸው አጀንዳ መሠረት አቤቱታ የቀረበባቸውን አህጉረ ስብከቶች በተመለከተ መርምሮና አጣርቶ መፍትሔን የሰጠ ሲሆን በአንጻሩ ከቅን አስተዳደር የሚጠበቅ ድርሻ ስለሆነ አስተዳደራዊ ችግር ያጋጠማቸው አህጉረ ስብከት ተመርምረው ውጤታቸው ተፋጥኖ ይቀርብ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያን ሰጥቷል፡፡
9. በበጀትና ሒሳብ መምሪያ በኩል የቀረበው የዘመኑ ገቢና ወጭ ሒሳብ ሪፖርት ከተሰማ በኋላ ገቢው በትክክል እንዲመዘገብ ሆኖ፤ የወጭው አርእስት ተጠብቆ በበጀት ዓመቱ እንዲሠራበት ቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያን ሰጥቷል፡፡
10. በጥንታዊት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በመንፈሳዊውም ሆነ በማኅበራዊው ረገድ ከፍተኛ ሥራ መሠራቱን ቅዱስ ሲኖዶስ ገምግሟል፡፡ በቀጣይም የቤተ ክርስቲያኒቱን ተልእኮ ለማስፋት በቤተ ክርስቲያኒቱ ከላይ እስከታች የሚተገበር የቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ ችግርና መሪ ዕቅድ ተዘጋጅቶ የቀረበ በመሆኑ ለዚሁ ተግባር በተከፈተው ጽ/ቤት ሥራው እንዲቀጥል፣ በውጭ አገር ለምትገኘውም ቤተ ክርስቲያናችን የየአገሮቹን ሕገ መንግሥት ባገናዘበ መልኩ ቃለ ዐዋዲ እንዲዘጋጅና ሁሉም አብያተ ክርስቲያናት በመዋቅራዊ አስተዳደር እንዲመራ ተወስኖአል፡፡
11. አሁን በቤተ ክርስቲያናችን ቅዱስ ሲኖዶስ መካከል የተፈጠረው አንድነት ለቀጣይ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሥራችን መቃናት በር ከፋች በመሆኑ ከአሁን በኋላ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭው ዓለም ያለችው ቤተ ክርስቲያን በአንዲት ቀኖናዊት ቤተ ክርስቲያን በማእከል እንድትመራ ወስኗል፡፡
12. ከሐምሌ ወር በዋሽንግተን ዲሲ የሁለቱ ሲኖዶስ ልኡካን የስምምነቱን ሰነድ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ተቀበሎ በማጽደቅ በሰነድነት እንዲቀመጥ ወስኗል፡፡
13. በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በዴር ሡልጣን ገዳማችን ይዞታ ላይ እየታየ ያለው ችግር ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ ከመሄዱ የተነሣ ችግሩ ይፈታ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ በጽሑፍም ሆነ በቃል ለሚመለከተው ሁሉ በአካል ቀርቦ ከማመልከት የተገታበት ጊዜ እንደሌለ ይታወቃል፤ ታሪካዊ እውነትን ለመሻር በማይገባ ሁኔታ የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በሌላት ርስትና መብት የዴር ሡልጣን ገዳማችን ባለቤትነታችንን ለማሳጣት ብዙ የፈጠራ ወሬዎችን በመንዛት የተሰማሩት ግብጻውያን ኮፕቲኮች ሊያውቁት የሚገባ ትልቁ ጉዳይ በማን ርስት ማን ያዝዛል? ኢትዮጵያውያን ለዘመናት ሕይወታቸውን ሳይቀር መሥዋዕት በማድረግ ሃይማኖታቸውንና ጥንታዊ ታሪካቸውን ጠብቀው ለእኛ አስረክበውናል፤ እኛም ጠብቀን ለትውልዱ የማስረከብ ኀላፊነታችንን እንወጣለን፡፡ የግብጽ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ በይዞታችን ላይ አግባብነት የሌለው ሥራን የማደናቀፍና በታሪክም ሆነ በማንኛውም የሰነድ መረጃ የሌለው የባለቤትነት ጥያቄ በማንሣት እየተፈጠረ ያለውን አላስፈላጊ ሁከትና ብጥብጥ ማቆም አለባቸው፤ ዴር ሡልጣን ትናትም ዛሬም ነገም የኢትዮጵያ ገዳም ነው፡፡ ዳሩ ግን መፍትሔውን ከማስገኘት ይልቅ እየደረሰ ያለው ተጽዕኖ እየሰፋና እየከበደ መጥቶ በአሁኑ ወቅት ገዳሙን በሚጠብቁና በሚቈጣጠሩ መነኮሳት ላይ በኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን አማካኝነት ያልተጠበቀ ከፍተኛ ችግር እየደረሰ ስለሆነ የችግሩን አስገዳጅነት አስመልክቶ የኢትዮጵያ መንግሥት የጉዳዩ ባለቤት እንደመሆኑ አስፈላጊውን መፍትሔ እንዲያስገኝልን እንጠይቃለን፡፡
14. የቦታቸው ታላቅነትና የታሪካቸው ስፋት ዓለም ዐቀፍ ዕውቅናን ባስገኘላቸው በርእሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን እየተገነባ ላለው ሙዝየምና፣ የመሰነጣጠቅ አደጋ ለሚታይበት ለቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ለጥገናና ለግንባታ አገልግሎት የሚውል ገንዘብ ተፈቅዷል፤ በዚሁ መሠረት፤ ለርእሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ሥራ ማከናወኛ ብር 20,000,000 /ሃያ ሚሊዮን ብር/ ለቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ማስጠገኛ፤ ብር 20,000,000 /ሃያ ሚሊዮን ብር/ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ወጭ ሆኖ እንዲሰጥ ተወስኗል፤
15. አንዳንድ ግለሰዎች በግልና በቡድን በመደራጀት የቤተ ክርስቲያኗ መብትና ቀኖና እየተጋፉ መሆናቸውን ከቀረበው ሪፖርት ጉባኤው ተገንዝቧል፡፡ ስለዚህ መንግሥት በዚህ ተግባር ላይ የተሰማሩትን የሕግ ከለላ እንዲያደርግ እንጠይቃለን፡፡
ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ በላይ በተጠቀሱትና በሌሎችም ዐበይት ጉዳዮች ላይ ለ11 ቀናት ያህል በአገር ዐቀፍና በዓለም ዐቀፍ ጉዳዮች በስፋትና በጥልቀት ሲወያይ ሰንብቶ ስብሰባውን በጸሎት አጠናቅቋል፡፡ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

የግብጽ ኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን በዴር ሡልጣን ገዳማችን የምታደርገው
ከታሪክ የወጣና ሕገ ወጥ እንቅስቃሴ የተወገዘ ነው፡፡

ከጥቅምት 11-21 ቀን 2011 ዓ/ም የተደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልአተ ጉባኤ የኢትዮጵያ ይዞታ በሆነው በዴር ሡልጣን ገዳም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ መቅደስ እድሳት ወቅት የግብጽ እስክንድርያ ኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን ያሳየችውን ሕገ ወጥ ተቃውሞ አውግዟል፤ ይህንንና ሌሎች ውሳኔዎች በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት እንደሚከለተው አስታውቀዋል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
የኢትዮጵያውያን ይዞታ በሆነው በዴር ሡልጣን ገዳም የቅዱስ ሚካኤል ቤተ መቅደስ እድሳት ላይ የግብጽ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባላት ያሳዩትን ሕገ ወጥ ተቃውሞ አስመልክቶ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ መግለጫ፤

ሁላችሁም እንደምታውቁት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኢየሩሳሌም ካሏት ጥንታውያንና ታሪካውያን ቅዱሳት መካናት ውስጥ አንዱና ዋናው በዴር ሡልጣን የሚገኘው የመድኀኔዓለም፣ የአርባዕቱ እንስሳ እና የቅዱስ ሚካኤል ገዳማት ናቸው፡፡ ከታሪክ እንደምንረዳው ኢትዮጵያውያን በምድረ እስራኤል የነበራቸው ርስት ከሦስት ሽህ ዓመት በላይ ያስቈጠረ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን የአሁኗ ኢትዮጵያ መልክዐ ምድራዊ መገኛዋን ከዐባይ ምንጭ ጋር በማያያዝ ያለምንም ማሳሳት ከአርባ ጊዜ በላይ የተመዘገበች፤ በታሪክ፣ በእምነትና በማኅበራዊ ትስስር ከእስራኤል ጋር የጸና ግንኙነት ያላት ሀገር ናት፡፡

ከንግሥተ ሳባ የኢየሩሳሌም ጒብኝት ጀምሮ ኢትዮጵያውያን ወደ ቅድስት ሀገር ያለማቋረጥ በየዓመቱ በዓለ ፋሲካን ለማክበር፣ ዓመታዊ አምልኮተ እግዚአብሔርን ለመፈጸም፣ በርስት የተሰጣቸውን ይዞታ ለማስከበርና በንግድ ሥራዎች ይጓዙ እንደነበር በታሪክም በቅዱሳት መጻሕፍትም የተረጋገጠ እውነት ነው፡፡ ለዚህም በሐዲስ ኪዳን ክርስትና ወደ ኢትዮጵያ ለመግባቱ ምክንያት የሆነውና በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ 8 ከቍጥር 26 እስከ 40 የተጻፈው የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ታሪክ አንዱ ማሳያ ነው፡፡

ኢትዮጵያውያን ወደ ኢየሩሳሌም በሚያደርጉት ጒዞ፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ትስስርን ከማጠናከር ባሻገር በዴር ሡልጣን እና በብዙ መካናት ቋሚ ይዞታን በማቋቋም በርካታ ገዳማትንና አድባራትን መሥርተዋል፣ መንበረ ጵጵስናም አቋቁመዋል፡፡ ይህም ድርጊት ኢትዮጵያ በኢየሩሳሌም የሕዝቦቿ ምልክትና መመኪያ እድትሆን አድርጓታል፡፡ ይሁን እንጅ ነባሩን ታሪካዊ እውነት ለመሻርና በማይገባ ሁኔታ ግብጻውያን በሌላቸው መብትና ሕጋዊ ባልሆነ የፈጠራ መረጃ ኢትዮጵያን ከኢየሩሳሌም የዴር ሡልጣን ገዳም ባለቤትነቷን ለማሳጣት ብዙ ጥረቶች ሲደረጉ ቢቆዩም ኢትዮጵያውያን ሕይወታቸውን ሳይቀር መሥዋዕት በማድረግ ሃይማኖታቸውንና ጥንታዊ ገዳማቸውን ጠብቀው እስከ አሁን ቆይተዋል፡፡

የኢትዮጵያውያን የኢየሩሳሌም ይዞታ ከቅዱሳት መጻሕፍት ማስረጃነት በተጨማሪ ኢየሩሳሌምን ይገዙ በነበሩ መሪዎች የግብርና የመንግሥት አዋጅ መዛግብት፣ ኢየሩሳሌም ድረስ ተጕዘው ታሪክ በጻፉ ምሁራን፣ በኢየሩሳሌም ተሳላሚዎች የግል ማስታወሻ እና በዓለም ዐቀፍ መዛግብት ሳይቀር የተመዘገበ ሐቅ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህልም እንደነ አባ ጀሮም ያሉ የላቲን ታሪክ ጸሐፊዎች፣ እንደነ ከሊፋ ዑመርና ሳላሐዲን ባሉ ገዥዎች፣ በኢየሩሳሌም ተመሳሳይ ይዞታ ባላቸው በአርመንና በሶርያ ኦሬንታል ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት፣ በግሪክና በራሽያ የምሥራቅ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት እንዲሁም በካቶሊክ ቤተክርስቲያን ልዩ ልዩ ገዳማት መዛግብት የተመሰከረ ነው፡፡ ይሁን እንጅ ግብጻውያን በሚፈጥሩት ግፍና ኢሰብኣዊ ድርጊት በይዞታችን ያለውን ገዳም ከጉዳት ለመጠበቅና ለማደስ አንኳ ሳንችል በመቅረታችን እየፈራረሰ ይገኛል፡፡

በመሆኑም ቤተክርስቲያኒቱ ስታሰማ በነበረው ተደጋጋሚ አቤቱታና የኢትዮጵያ መንግሥት ባቀረበው ሕጋዊ የመብት ጥያቄ መሠረት የእስራኤል መንግሥት ገዳሙን ለማደስ ቃል በመግባቱ እና በዚሁ መሠረት መንግሥት ቃሉን በመጠበቅ በቅርቡ ጉዳት ከደረሰበት ከቅዱስ ሚካኤል ቤተመቅደስ እድሳቱ በመጀመሩ የተሰማንን ከፍተኛ ደስታ በቅድስት ቤተክርስቲያን እና በመላው ኢትዮጵያውያን ስም በመግለጽ ልባዊ ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡ የተጀመረው እድሳት በዴርሡልጣን የሚገኙ እና እጅግ በአስከፊ ጉዳት ላይ ያሉ ሁሉንም የኢትዮጵያ ይዞታዎች በማዳረስ ገዳሙ ጥንታዊ ይዞታውን ጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍ እንደሚደረግልን እናምናለን፡፡

አሁን እየተደረገ ያለውን ጥገና አስመልክቶ የኢትዮጵያ መንግሥትም ሆነ በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ለእስራኤል መንግሥት ምስጋናችሁን እንድታቀርቡልን የግብጽ ቤተክርስቲያንን መሠረት የለሽ ክስና ሁከት በመቃወም ገዳማችሁን በመጠበቅ የበኩላችሁን እንድትወጡ፣ ወደ ፊትም ከግብጽ ያልተመለሱ ይዞታዎቻችንን ለማስመለስ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ እንድታደርጉ ጥሪ እናደርጋለን፡፡

በዚሁ አጋጣሚ የግብጽ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባላት በይዞታችን ላይ አግባብነት የሌለው ሥራን የማደናቀፍና በታሪክም ሆነ በማንኛውም የሰነድ ማስረጃ መሠረት የሌለው የባለቤትንት ጥያቄ በማንሣት እየፈጠሩት ያለውን አላስፈላጊ ሁከትና ብጥብጥ እንዲያቆሙ፣ ዴርሡልጣን የኢትዮጵያ ገዳም ምንጊዜም ቢሆን የኢትዮጵያ የነበረና ወደፊትም የኢትዮጵያ ሆኖ የሚቆይ ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ቅርሳችን፣ የኢትዮጵያውያን በኢየሩሳሌም ቅድስት ሀገር በሁሉም ዘመን በቋሚነት ለመገኘታቸው ምስክር ስለሆነ ከዚህ የተሳሳተ ትንኮሳና ሁከት እንዲታቀቡ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም የተጀመረው የእድሳት ሥራ ተጠናክሮ በመቀጠል ሁሉንም የኢትዮጵያ የዴር ሡልጣን ይዞታዎች በአግባቡ እንዲጠገኑልን፣ በኢትዮጵያ መንግሥትም ሆነ የሰው ልጅ ቅርስ ጥበቃ ለሚያሳስባቸው በጎ አድራጊዎች ሁሉ ጥሪያችንን እያስተላለፍን እድሳቱ ያለምንም ዕንቅፋትና ሁከት ከፍጻሜ እንዲደርስ ጸሎታችንና ምኞታችን መሆኑን እናስታውቃለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፣ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/007-3.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32018-10-31 09:21:572025-01-27 09:25:44ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 21 ቀን 2011 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ... Link to: ታኅሣሥ 29 ቀን 2011 ዓ.ም የልደት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ታኅሣሥ 29 ቀን 2011 ዓ.ም የልደት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ታኅሣሥ 29 ቀን 2011 ዓ.ም የልደት በዓል ቃለ ምዕዳንና...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top