• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

መጋቢት 30 ቀን 2010 ዓ.ም. የትንሣኤ በዓል ሙሉ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

በትንሣኤው ኀይል ማኅለቅትና ፍጻሜ የሌለው ሕይወተ ትንሣኤን ያደለን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ።

ወእመሰ ንትአመን ከመ ተንሥአ ክርስቶስ እሙታን ከማሁ ያነሥኦሙ እግዚአብሔር ለሙታን፤ ክርስቶስ ከሙታን እንደተነሣ ካመን እንደዚሁ እግዚአብሔር ሙታንን ያነሣቸዋል፡፡ ( 1ተሰ. 4፥13)

ለሰው ልጆች በፊታችን ተጠብቆልን ያለ ትልቅ ተስፋ፣ ትንሣኤ ሙታን ነው፤ ለሰው ልጅ የመጨረሻው የክብር ዘውድና የሕይወት ጕልላት፣ ከመቃብር ታድሶ መነሣትና እሱን ተከትሎ በሚመጣው በቀዋሚው የእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ መኖር ነው፤ እግዚአብሔር የፍቅር አምላክ ነውና ፍጥረቱን በፍቅር ፈጥሮ በፍቅር ያስተዳድራል፤ እግዚአብሔር የክብር አምላክ በመሆኑ ፍጥረቱን ለማክበር ሁሌም ዝግጁ ነው፤ እግዚአብሔር ለፍጥረቱ ያለውን ፍቅርና ክብር ለመረዳት በየዕለቱ በሕይወታችን ላይ የሚፈጽመውን ጥበቃና ምግብና ማየቱ በቂ ነው፡፡እግዚአብሔር በፍጹም ፍቅሩና ማኅለቅት በሌለው ልግስናው በምንኖርባት ምድር ለፍጡራኑ ኑሮ አስፈላጊ የሆኑትን ነገሮች በበቂ ሁኔታ አሟልቶ መስጠቱ ሌላው የታላቅ ፍቅሩ ማስረጃ ነው፤ እግዚአብሔር ለፍጥረቱ ያለውን ታላቅ ፍቅርና አክብሮት በይበልጥ የገለጸበት ዐቢይ ክንውን አንድ ልጁ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስን ለፍጥረቱ ቤዛ እንዲሆን ለመከራና ለሞት አሳልፎ መስጠቱ ነው፤ ይህ ድርጊት እግዚአብሔር ፍጥረቱን ምን ያህል እንደሚወድ ያሳየበት የፍቅሩ ጣራ ወይም ጫፍ ነው፡፡

እግዚአብሔር ለማያልቅ ኀይለ ሕይወት በመልኩና በአምሳሉ የፈጠረን እኛ ከተቀመጠልን የሕይወት ድንበር ወጥተን ወደ ሞት ሀገር በመቀላቀላችን ምክንያት በብቸኝነትና በአሠቃቂ መከራ ስንማቅቅ ኖረናል ፤ ይሁን እንጂ እንዲህ ሆነን ስንኖር ዝም ብሎ ማየት፣ ወሰን የለሽ ርኅራኄ ላለው ለእግዚአብሔር አምላካችን የሚቻል አልሆነም፤ በመሆኑም የመከራችንን ታሪክ በመለወጥ ያድነን ዘንድ በፈቀደ ጊዜ በአካል የሚተካከለው፣ በመለኮትና በቅድምና ከእሱ ጋር አንድ ህላዌ የሆነ የባሕርይ ልጁን ወደኛ ላከ፤ ቃሉ፣ ኀይሉና ጥበቡ የሆነ ወልድ ዋሕድ ሥጋችንን እና ነፍሳችንን ተዋሕዶ በእኛ አካል በዚህ ዓለም ተገለጸ፤ እሱ በዚህ ዓለም በቆየበት ጊዜ የሕይወት መንገድን በቅዱስ ወንጌል አስተማረን፣ የሰው ልጅ ሁሉ ብቸኛ አዳኝ መሆኑን ሕሙማንን በመፈወስ፣ ሙታንን በማንሣት፣ ኅብስትን በማበርከት አሳየን፤ ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱሰ ክርስቶስ በዚህ አምላካዊ ኀይሉ ማለትም ደምሳሴ ኀጢአት በመሆኑ፣ ሙታንን በማንሣቱ፣ አጋንንትን በማውጣቱ፣ ለሕሙማን ፈውስን በመስጠቱ፤ በኀጢአት፣ በሞት፣ በዲያብሎስና በበሽታዎች ሁሉ ላይ ላዕላዊ ሥልጣን ያለው እንደሆነ፣ ሕገ ተፈጥሮም በቊጥጥሩ ሥር መሆኑን አሳየን፤ ከዚህ በኋላ ለሰው ልጅ ሁሉ ቤዛ ሆኖ በመስቀል ላይ መሥዋዕትነትን በመክፈል ኀጢአታችንን አስወገደ፤ በሞቱ ሞታችንን አስቀረ፣ በትንሣኤው ሕያውነታችንን አበሠረ፤ በዚህም ተግባሩ የመዳናችንን ምሥጢር ፈጸመ፣ በጨለማና በሞት ጥላ ለነበሩም ነፃነትን ሰበከላቸው፤

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤

የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ የእኛ ትንሣኤ ማሳያና አስረጅ በመሆኑ በእኛ መጻኢ ዕድል ላይ ያለው ትርጒም ከሁሉም የላቀ ነው፤ የእኛ ሕይወት እንደ ቅጽበተ ዐይን ግልጥ ብላ ጥፍት በምትል በዚህች ምድራዊ ዕድሜአችን የተገደበች አይደለችም፤ ሕይወታችን ማኅለቅትና ፍጻሜ፣ ማርጀትና ኅልፈት የሌለው ህላዌ ገና ይጠብቃታል፤ ይህ ጸጋ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሞቱ ያዘጋጀልን፣ በትንሣኤው ያበሠረን የወዲያኛው ሕይወት ሀልዎትና ወሰን የለሽ ዕድሜ ነው፤ እሱ እኛን ከኀጢአትና ከሞት ለመገላገል እንደሞተ፣ እኛም ማሕየዊ ሞቱ ያስገኘልንን ድኅነት ለመቀዳጀት በመጠመቃችን የሞቱ ተባባሪዎች ሆነናል፤ እሱ ዳግም የማይሞትና ለዘለዓለም ሕያው መሆኑን ለማብሠር ሞትንና መቃብርን ድል ነሥቶ በአሸናፊነት እንደተነሣ፣ እኛም ዳግም ላንሞት ይልቁኑም የማያልቅ የኀይለ ሕይወት ባለቤቶች እንሆን ዘንድ በመጠመቃችን የትንሣኤው ተባባሪዎች ሆነናል፤ በሌላ አገላለጽ በእሱ ስም በመጠመቅ የሞቱም የትንሣኤውም ተባባሪዎች ሆነናል፤ እሱ ሞትንና መቃብርን ድል ነሥቶ እንደተነሣ፣ እኛም በጥምቀት ከእሱ ጋር በመተባበራችን ምክንያት እሱ በከፈተልን መንገድ ሞትንና መቃብርን ድል ነሥተን ከእርሱ ጋር ወደ ሰማያዊው መንግሥት እንነጠቃለን፤ በዚያም በማያልቅ ኀይለ ሕይወት ከእርሱ ጋር ፍጻሜና ማኅለቅት፣ ማርጀትና ኅልፈት በሌለበት ህላዌ እንኖራለን፤ ሰው ወዳጅ የሆነ፤ ፍቅሩና ክብሩ ማለቂያ የሌለው እግዚአብሔር አምላካችን ለእኛ ያዘጋጀው መጻኢ ዕድል ይኸው ነው፤ ስለሆነም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞቶ የተነሣው ለራሱ ሳይሆን ለእኛ ሲል ነውና ክርስቶስ ሞቶ ተነሣ ማለት ምሥጢራዊ ትርጉሙ ሰዎችን ከፍዳ ኀጢአትና ከመርገም አላቀቀ፤ ሞትንና ሙስና መቃብርን ከሰው አራቀ፤ ሰውን በዘለዓለማዊ ሕይወት ለማኖር እንደገና አበቃ ማለት ነውና የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ከሰጠን ጥቅም አኳያ ሙሉ በሙሉ የእኛ ትንሣኤ እንደሆነ መረዳት ይገባናል፤ በሞቱ ድኅነታችንን፣ በትንሣኤው ሕይወታችንን መመለሱን በትንሣኤው ተግባራዊ አዋጅ ተነግሮናል፤ የመጨረሻ አፈጻጸሙ ግን ጌታችን እንደገና ተመልሶ ሲመጣ ይከናወናል፤ ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ክርስቶስ ከሞት እንደተነሣ በተመሳሳይ ሁኔታ እግዚአብሔር ሙታንን ያነሣቸዋል ሲል ያስተማረን ይህንን ሲገልጽ ነው፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸን፡ ትልቁና ዋናው የትንሣኤያችን ሕይወት በጌታችን ዳግም ምጽአት ይረጋገጣል ቢባልም ውጥኑ አሐዱ ተብሎ የሚጀመረው አሁን ነው፤ እያንዳንዷ የዕድሜያችን ሰዓት የትንሣኤ ሥራን የምናከናውንባት ዕለተ ትንሣኤ ናት፤ እግዚአብሔርን የምናመልክባትና የምናመሰግንባት ቀን ዕለተ ትንሣኤ ናት፤ ወንድም ከወንድሙ ጋር በፍቅርና በሰላም፣ በመቻቻልና በመከባበር የሚያሳልፋት ቀን ዕለተ ትንሣኤ ናት፤ ስለ ሀገርና ስለ ሕዝብ አንድነት፣ ስለ ሕዝብ አእምሮኣዊና ምጣኔ ሀብታዊ ልማት በመሥራት የምናሳልፋት ቀን ዕለተ ትንሣኤ ናት፣ በአጠቃላይ ለትልቁና ለዋናው ትንሣኤ ተሸላሚዎች አድርጎ የሚያቀርበን በዚህ ዓለም በቆየንበት የዕድሜያችን ዘመን ሁሉ በበጎ ኅሊና ተነሣሥተን የምንፈጽመው የሃይማኖትና የማኅበራዊ ኑሮ የተግባር ትንሣኤ ድምር ውጤት ነው፡፡ በመሆኑም በዓለ ትንሣኤ የአዲስ ሕይወት ማብሠሪያ በዓል እንደመሆኑ መጠን የሀገራችን ሕዝቦች በዓሉን ሲያከብሩ ለአዲስ ወንድማዊ ፍቅር፣ ለጠንካራ ሀገራዊ አንድነት፣ ለፍጹም ሀገራዊ መግባባትና ለተሻለ የልማት ሥራ በአንድነት ለመነሣት ቃል በመግባት ሊሆን ይገባል፡፡

በመጨረሻም፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት ባስተናገደችው ያላስፈላጊ ንትርክ ብዙ ነገርን እንዳጣች ኢትዮጵያውያን ሁላችን የምንስተው አይሆንም፤ ይህ ክሥተት ተስፋ ከተጣለበት የሀገሪቱ የሕዳሴ ፍኖተ ካርታ ጋር ፈጽሞ የማይሄድ ነው፤ ስለሆነም ያለፈውን ትተን ከዛሬ ጀምሮ በሠለጠነ የውይይት ዘዴና ከሁሉም በላይ ለሀገር እድገትና ለሕዝብ አንድነት ቅድሚያ በመስጠት ችግራችንን እየፈታን በልማትና፣ በእድገት ከበለጸጉት የዓለማችን ሀገራት ጋር እኩል ወደሚያደርገን ልማታዊ ሥራችን ፊታችንን እንድናዞር ለሁሉም ኢትዮጵያውያን ልጆቻችንና ወገኖቻችን አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

መልካም በዓለ ትንሣኤ ያድርግልን እግዚአብሔር አምላክ ሀገራቸንን ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32018-04-08 13:36:352025-01-28 13:37:43መጋቢት 30 ቀን 2010 ዓ.ም. የትንሣኤ በዓል ሙሉ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: የካቲት 5 ቀን 2010 ዓ.ም የዐቢይ ጾም መግቢያ ቃለ ምዕዳንና ቃለ ቡራኬ Link to: የካቲት 5 ቀን 2010 ዓ.ም የዐቢይ ጾም መግቢያ ቃለ ምዕዳንና ቃለ ቡራኬ የካቲት 5 ቀን 2010 ዓ.ም የዐቢይ ጾም መግቢያ ቃለ ምዕዳንና... Link to: ሚያዝያ 24 ቀን 2010 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ሚያዝያ 24 ቀን 2010 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሚያዝያ 24 ቀን 2010 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top