ነሐሴ 1 ቀን የ2007 ዓ.ም. የጾመ ፍልሰታ ቃለ ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የምትገኙ፣ የእግዚአብሔርና የቅድስት ድንግል ማርያም ልጆች ምእመናንና ምእመናት፣ እንኳን ለሁለት ሺሕ ሰባት ዓመተ ምሕረት የቅድስት ድንግል ማርያም መዋዕለ ጾም በሰላም አደረሳችሁ፡፡

“ታዐብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር
ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች።”
(ሉቃ. 1፥47)

ቅድስት ድንግል ማርያም በቅዱስ ገብርኤል አብሣሪነት አካላዊ ቃለ እግዚአብሔርን ከፀነሰች በኋላ ወደ ቅድስት ኤልሳቤጥ ቤት ገብታ ሰላምታ ባቀረበች ጊዜ በኤልሳቤጥ ማሕፀን ያለው ፅንስ በድንግል ማርያም ማሕፀን ላለው ፅንስ ከመስገዱም በተጨማሪ ቅድስት ኤልሳቤጥ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልታ ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ብፅዕና በሰፊው መናገሯ በቅዱስ መጽሐፍ ተጽፎአል (ሉቃ. 1፥45)፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር በቅዱስ ገብርኤልና በቅድስት ኤልሳቤጥ በኩል ያስነገረላትን ታላቅ ክብርና ሞገስ በማድነቅ እግዚአብሔርን በከፍተኛ ደረጃ አመሰግናለች፤ ደስታዋንም ገልጻለች፡፡

ከዚህ ከቅድስት ድንግል ማርያም ምስጋና የምንማረው ዐቢይ ትምህርት እግዚአብሔር በየጊዜው ያደረገልንን መልካም ነገር ሁሉ በማሰብ ለእርሱ አምልኮና ምስጋና ማቅረብ ያለብን መሆኑን ነው፤ ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔርን ባመሰገነችበት በዚህ ክፍል በእርስዋና በክርስቲያኖች መካከል ያለው የዘለዓለም ግንኙነትና ትስስር ምን ዐይነት ገጽታ እንደሚኖረው በትንቢት ተናግራለች፤ እርሱም “ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል” የሚል ነው (ሉቃ. 1፥48)፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤

በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቅ የቤተ ክርስቲያን ተቀዳሚ ተግባር ቃለ እግዚአብሔርን መጠበቅና ማስጠበቅ እንደሆነ ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም፤ እግዚአብሔር ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ከተናገራቸው ኀይለ ቃላት መካከል “ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል፣ ባለሟልነትን አግኝተሻል፤ ጸጋን የተመላሽ ደስ ይበልሽ፤ እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ነው” የሚሉት በቀዳሚነት ተጠቃሽ ናቸው፤ (ሉቃ. 1፥28-30) በተለይም “ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል” የሚለው ቃል በቅድስት ድንግል ማርያም አንደበት የተነገረ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡

ይህ የእግዚአብሔር ቃል ቅድስት ድንግል ማርያምንና ምእመናንን እስከ ወዲያኛው ያስተሳሰረ የቃል ኪዳን ሐብል ነው፤ በየዓመቱ ከነሐሴ አንድ ቀን ጀምሮ እስከ ነሐሴ ዐሥራ አምስት ቀን በጾም፣ በጸሎት፣ በአምልኮ፣ በምሥጋና፣ በንስሓና በቍርባን ለእግዚአብሔር መገዛታችንና ቅድስት ድንግል ማርያምን መማፀናችን ባለሟልነትን አግኝተሻል የሚለውን ቃል መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ባለሟል ማለት በባለሥልጣን ዘንድ ተሰሚነት፣ ተደማጭነት፣ ተቀባይነት ያለው ቀራቢ ልዩ ወዳጅ ማለት እንደሆነ ለማንም ግልጽ ነው፡፡ በዚህ መሠረት ቀደምት ቅዱሳን አበውና ነቢያት በባለሟልነታቸው በሕይወት እያሉም ሆነ ከሞቱ በኋላ በዐጸደ ነፍስ ሆነው እግዚአብሔርን እየተማፀኑ እየማለዱና እየለመኑ ሰውን ያስምሩ እንደነበር ተጽፎአል፤ (ዘፀ. 32፥11-14፤ ኢዮ. 42፥7-9፤ ነገ.ቀዳ. 11፥10-13)፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ቅድስት ድንግል ማርያም በባለሟልነቷ ብቻ ሳይሆን እርሱን ፀንሳ የወለደችና ያሳደገች የጌታችን እናትና ልዩ ባለሟል በመሆኗ በጸሎትዋ፣ በልመናዋና በአማላጅነቷ አምነን ስንማፀናት እኛን ታስምራለች ብለን እናምናለን፤

የቅድስት ድንግል ማርያም ልመና ተቀባይነት ያለው ስለመሆኑ በቃና ዘገሊላ የሠርግ ቤት ያቀረበችው ምልጃና ልመና በሁኔታውም የተገኘው ውጤት ለኛ በቂ ማስረጃችን ነው፤ (ዮሐ. 2፡ 1-9) ከዚህም ጋር ራሱ ጌታችን በመስቀል ላይ ሆኖ እርስዋን የኛ እናት አድርጎ፣ እኛንም የእርስዋ ልጆች አድርጎ መስጠቱ ልጅ የሚፈልገውን ነገር ከእናቱ እንደሚሻ ሁሉ እኛም የምንሻውን ነገር ታሰጠን ዘንድ እንድንማፀናት ነው፡፡ እናትም አዛኝ፣ ርኅርኅት ተቆርቋሪ አሳቢ ሆና ለልጇ እንደምትጨነቅ እርስዋም ለኛ አዛኝ ርኅርኅትና ተቆርቋሪ በመሆን ዘወትር ስለእኛ እርሱን እንድትለምንልን ነው ከዚህ ውጭ ሌላ ትርጒም ሊኖረው አይችልም፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት ይህንን መሠረታዊ ትምህርት ተገንዝበውና የቅድስት ድንግል ማርያምን እናትነት ተቀብለው እርስዋን ለማግኘት ሲሉ በዚህ ወር በመጾምና እርስዋን በመማፀን ልጅነታቸውን በተግባር አሳይተዋል፤ በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሣውና የተላውያነ ሐዋርያት ትምህርትን በምልአት የተረዳው የቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ይህን አስመልክቶ እንዲህ ብሎአል ‹‹ወይብሉ ኵሎሙ ሐዋርያቲሁ ለእግዚእነ ሰአሊ ለነ ማርያም እምነ፤ የጌታችን ሐዋርያት ሁሉ እናታችን ማርያም ሆይ ለምኝልን ይላሉ›› በማለት በድጓው በብዙ ቦታ ላይ ጽፎአል፡፡ ጥንታዊው የሐዋርያት ትምህርት፣ ትውፊትና ባህል ያልተለያት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ከጌታችንና ከሐዋርያት የተቀበለችውን ሁሉ ሳትሸራርፍ እንዳለ ይዛ እነሆ አስካሁን ድረስ የቅድስት ድንግል ማርያምን ክብርና ብፅዕና እንደ ቃሉ ጠብቃ እየተጓዘች ነው፡፡ ለዚህም ዛሬ የምንጾመው የሁለት ሺሕ ሰባት ዓመተ ምሕረት የቅድስት ድንግል ማርያም ጾም ምስክር ነው፡፡

የሀገራችን ታላቅነትና ነፃነት፣ አንድነትና ሉዓላዊነት፣ ታሪክና ባህል፣ ቅዱስ ሥነ ምግባርና ሌላው ጸጋ ሁሉ ጠብቆ በማስጠበቅ ዛሬ በዓለም መካከል ልዩ አድናቆት ላላት ሀገር ባለቤት እንድንሆን ያስቻለን ይህ ሃይማኖታችን እንደሆነ ከቶ ሊዘነጋ አይገባም፤ አሁንም ከአባቶቻችን የወረስነው መልካም ዕሴት ለቀጣዩ ትውልድ በአስተማማኝ ለማስተላለፍ የሃይማኖታችንን እሴቶች ሁሉ በሚገባ መጠበቅ ይገባናል፤

‹‹ሰው እንደ ቤቱ እንጂ እንደ ጎረቤቱ አይኖርም›› እንደተባለው ሁሉ ከሃይማኖታችንና ከባህላችን እንደዚሁም ከቅዱሳት መጻሕፍት አስተምህሮና ከሕገ ተፈጥሮ ውጭ የሆነውን ነውረ ኀጢአት ከሌላው ሀገር ወደ ሀገራችን ለማጋባት የሚደረገው ተጽዕኖ የቤተ ክርስቲያናችን ምእመናንና ሁሉም ኢትዮጵያውያን አምርረው ሊታገሉትና ሊመክቱት ይገባል ፡፡

እኛ ኢትዮጵያውያን ነን፤ እኛ ‹‹እጆቻቸውን ወደ እግዚአብሔር ይዘረጋሉ›› ተብሎ የተነገረልን የእግዚአብሔር ሕዝቦች ነን፤ የእግዚአብሔር ሕዝብ የነውረ ኀጢአት ተገዥ ሊሆን ከቶ አይችልም ብለን በጽናት መቋቋም ይኖርብናል ፡፡ ጾም የተፈጠረው ከነውረ ኀጢአት ለመራቅ፣ በንጽሕና እና በቅድስና ከእግዚአብሔር ጋር ለመገናኘት፣ ለሰው ሁሉ የርኅራኄና የፍቅር ሥራ ለመሥራት ነው፡፡ በመሆኑም በዚህ የጾም ወቅት ያዘኑትን በማጽናናት፣ የተቸገሩትን በመርዳት፣ የተጎሳቈሉትን በመደገፍ፣ ፍጹም ርኅራኄን ለወገኖቻችን በማሳየት አካሄዳችንን ከእግዚአብሔር ጋር ማድረግ አለብን፣ በተለይም በአሁኑ ጊዜ በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች የዝናም እጥረት እንዳለ እየተሰማ ስለሆነ ሕዝበ ክርስቲያኑ በዚህ ሱባዔ በየቤተ ክርስቲያኑ እየተገኘ የምሕላ ጸሎት በማድረስ ፈጣሪውን በኀዘንና በጸሎት እንዲለምን፣ ቅድስት ድንግል ማርያምንም እንዲማፀን መልእክታችንን ከአደራ ጭምር እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር ጾሙን በሰላም ያስፈጽመን፤እግዚአብሔር ይባርካችሁ ይቀድሳችሁ፤አሜን፡፡