ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ: ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ በኢትዮጵያ የጣልያን አምባሳደር ሆነው የተሾሙትን አምባሳደር ሴም ፋብሪዚ (Sem Fabrizi) በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በኢትዮጵያ አዲሱ የኢጣልያ አምባሳደር ሴም ፋብሪዚ በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ።
በውይይቱ ወቅት ቅዱስ ፓትርያርኩ ለአዲሱ ተሿሚ አምባሳደር ሴም ፋብሪዚ የእንኳን ደህና መጡ መልእክት ካስተላለፉ በኋላ፣ መልካም የሥራ ዘመን እንዲሆንላቸው ተመኝተዋል። ቅዱስነታቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጥንታዊትና ታሪካዊት መሆኗን ጠቅሰው፣ ከጣልያን ጋር ያሏት ታሪካዊ ግንኙነቶች ይበልጥ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።
ቅዱስነታቸው በውይይቱ ወቅት ባስተላለፉት ጥልቅ የሰላም እና የሰብአዊነት መልእክት፤ ዓለማችን ማንኛውም ፍጡር የሃይማኖት ልዩነት ሳይኖርበት በእኩልነት፣ በመከባበር እና በሰብአዊነት አስተሳሰብ ሊኖርባት የተሰጠች መሆኗን ገልጸዋል። በመሆኑም ሕይወታችንን በሰላማዊ መንገድ መምራት እንደሚገባ ጠቅሰው፤ “እኛ የሃይማኖት አባቶች ሁሌም በትጋት በሀገራችን ብሎም በመላው ዓለም ሰላምና ፍቅር እንዲሰፍን እንጸልያለን” ብለዋል።
አምባሳደር ሴም ፋብሪዚ ከቆይታቸው በኋላ ለብዙኃን መገናኛ ድርጅት ጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጋር መወያየታቸው እንዳስደሰታቸው ጠቁመው፣ ውይይቱ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ጥንታዊና ታሪካዊ ግንኙነት ይበልጥ የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸዋል።
አምባሳደሩ አክለውም፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በሀገሪቱ ማኅበራዊ ትስስር እና የታሪክ ግንባታ ውስጥ ያላትን ሚና ከፍተኛ ግምት እንደሚሰጡት ተናግረዋል።
እንዲሁም አምባሳደሩ ይህንን የቆየ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ጣሊያን በሰላምና በልማት ዘርፎች ላይ ከቤተክርስቲያኗ ጋር በትብብር ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗን ጠቁመዋል። በተለይም ከሀገራቸው መንግሥት ጋር በመሆን በዘላቂ ሰላም ዙሪያ ይበልጥ እንደሚሠሩ አመላክተዋል።