• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ጥር 11 ቀን 2012 ዓ.ም የጥምቀት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

“ሀለወክሙ ትትወለዱ ዳግመ
ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል፤”
(ዮሐ. 3፥7)

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ልደትንና አስፈላጊነቱን አስመልክቶ ያስተማረው ተቀዳሚ ትምህርት በዚህ ምዕራፍ ተጽፎ ይገኛል፡፡ ጌታችን በዚህ ትምህርቱ የልደት ዐይነት ሁለት እንደሆኑ እነሱም ሥጋዊና መንፈሳዊ ልደት እንደሚባሉ በአጽንዖት አስተምሮአል፡፡ ሥጋዊ ልደት ሰው ሁሉ ከእናቱና ከአባቱ በግዘፍ የሚወለደው ነው፤ ይህ ሁሉም የሚያየውና የሚያውቀው ስለሆነ ተጨማሪ ማብራርያ አያስፈልገውም፤ መንፈሳዊ ልደትን በምንመለከትበት ጊዜ ግን እንደ ስሙ መንፈሳዊ ወይም ረቂቅ ስለሆነ ማስተዋልን በእምነት መነጽር መመልከትን ይጠይቃል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ አስተምህሮው ሰው ሁሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የሚገባበትን ምሥጢር ገልጾአል፤ ቅዱስ መጽሐፍ ደጋግሞ እንደሚያስተምረን ሰው ለክብር የተፈጠረ ታላቅ ፍጡር ነው፤ ይህንንም ማስተዋል የምንችለው ከሰው በቀር በእግዚአብሔር መልክና አምሳል የተፈጠረ ፍጡር በሰማይም ሆነ በምድር የሌለ በመሆኑ ነው፤ ይህ መልክና አምሳል ውጫዊውን የመልክ ገጽታ ብቻ የሚያሳይ ሳይሆን በእግዚአብሔርና በሰው መካከል ያለውን ጥብቅ ግንኙነት የሚያመለክት ነው፤ ይህ ግንኙነት በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ በአባትና በልጅ፣ በባልና በሚስት፣ በወይን ግንድና በቅርንጫፍ ወ.ዘ.ተ… ምሳሌነት ተገልጾአል፡፡ እግዚአብሔር ሰውን አክብሮና ከራሱ ጋር አስተሳስሮ የፍጡራን ሁሉ አዛዥና አስተናባሪ አድርጎ እንደዚሁም በምድር ላይ ብቸኛ የእግዚአብሔር ምስለኔና እንደራሴ አድርጎ መሾሙ በቅዱስ መጽሐፍ ተጽፎአል፡፡

ይሁን እንጂ ይህ ግንኙነት በምክረ ሰይጣን ስለተቋረጠ ሰው በጣም አሳዛኝ በሆነ ሁኔታ ወደቀ፤ በዚህም ውድቀት የሰው ሁለንተና ሕይወቱ ተናጋ፤ ሥጋዊ ሕይወቱ በመከራ አረም ሙሉ በሙሉ ከመዋጡም ሌላ፣ ንጹሕ አእምሮው ተቃወሰ፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ መውጫውንና መግቢያውን ትንፋሹንም ጭምር ከያዘና ሁሉን ከሚችል ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር ልጅነት ተገለለ፤ ህላዌው ሁሉ በጨለማ የተዋጠ ሆነ፤ ሰው በዚህ ዓለም የሚቆይበት ሕይወት ተጠናቅቆ ሥጋው ወደ መቃብር ሲወርድ ነፍሱ ደግሞ ወደ መከራና ሥቃይ ቦታ ወደ ሲኦል ጒድጓድ መጣል ዕጣ ፈንታው ሆነ፡፡ ይህ ሁሉ አሰቃቂ ሕይወት ሊከሠት የቻለው ሰው የእግዚአብሔርን ምክር ንቆና ትቶ፣ የሰይጣንን ምክር አምኖና ተቀብሎ በፈጸመው ስሕተት ጠንቅ ነው፤ የበደለን መቅጣት፣ የታመነን መሸለም በፍጡር የማይጣስ ሕገ መለኮት ነውና ጥፋተኛ የሆነው የሰው ልጅ ከመቀጣት በቀር የሚያገኘው ሽልማት አልነበረውም፤ ሰውም ያለውድ በግድ ቅጣቱን ተቀብሎ መራራ ኑሮውን በሰማይም በምድርም ቀጠለ፤ ይህ ሁኔታ ጌታችን በሞቱ እስኪያስወግደው ድረስ ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመናት ያህል ዘልቆአል፤ ከጌታችን ሞት በኋላ ግን ለሰው ልጆች እንደገና አዲስ ጒዞ ተጀምሮአል፤ እሱም በጌታችን ደም የሰው ልጅ በደል በመሠረዙ ምክንያት ከሞት በኋላ የሰው ነፍስ ጒዞ ወደ ሲኦል ጉድጓድ ሳይሆን ወደ ገነት ሆኖአል፤ ይህንንም ጌታችን በመስቀል ላይ ሳለ አምኖ ንስሐ ለገባው ወንበዴ “ ዛሬውኑ ከኔ ጋር በገነት ትኖራለህ” ባለው የማይሻር ቃሉ አረጋገጠው፤ በገነት መኖር ማለት አዳም ከመውደቁ በፊት ወደ ነበረው ጣዕመ ሕይወትና ቦታ እንደገና መመለስ ማለት ነው፡፡

እንግዲህ በአሁኑ ጊዜ የሰው ልጅ ሁሉ ትልቁ ጥያቄ ይህንን ገነታዊ ጣዕመ ሕይወት እንዴት እናግኝ የሚል ነው፤ ጥያቄው ትክክለኛና የአስተዋይ ሰው ሁሉ ጥያቄ ነው፤ ነገር ግን ጥያቄው የዛሬ ሁለት ሺሕ ዓመት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አስተምህሮ አጥጋቢና እውነተኛ መልስ ያገኘ በመሆኑ እሱን በሚገባ መረዳትና መፈጸም ያሻል፡፡ ጌታችን አንድ የአይሁድ መምህርና ዐዋቂ፣ ሊቅና አስተዋይ ካቀረበው ጥያቄ ተነሥቶ ሲመልስ፡-“ እውነት እውነት እልሃለሁ፡- ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያያትም” ብሎአል፤ ጌታችን በዚህ ትምህርቱ የእግዚአብሔር መንግሥት በማለት የገለጸው ቦታ፣ ቃል ሊገልጸው ከሚችል በላይ ለኑሮ በጣም ምቹ የሆነና ራሱ በመስቀል ላይ ሳለ ገነት በሚል ስያሜ የጠራው ቦታ ነው፤ ማንኛውም ሰው ወደዚህ ቦታ ለመግባት ከሁሉ በፊት ዳግመኛ መወለድ ያስፈልገዋል፡፡ ዳግመኛ ካልተወለደ ግን መግባት ይቅርና በዐይን አሻግሮ ማየት እንኳ አይችልም፤ ጌታችን አያያትም ብሎአልና፡፡ ከዚህ አንጻር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት የሚቻለው እንዴት ነው ለሚለው ጥያቄ መልሱ “ዳግመኛ በመወለድ ነው” የሚል መልስ ከጌታችን ተሰጥቶአል፤ ነገር ግን አእምሮው ውሱን የሆነው የሰው ልጅ አሁንም ጥያቄውን በማራዘም ሰው ካደገ በኋላ እንደገና ተመልሶ ወደ እናቱ ማሕፀን ሊገባና ዳግመኛ ሊወለድ እንዴት ይችላል በማለት ጠይቆአል፤ነገር ግን ጌታችን ለዚህም ሰፊ ማብራሪያና መልስ ጥልቅ ትምህርትም ሰጥቶአል፡፡ ጌታችን ይህንን አስመልክቶ በሰጠው ትምህርት ሰው ዳግመኛ ለመወለድ እንደገና ወደ እናት ማሕፀን መግባት አያስፈልገውም፤ ዳግመኛ መወለድ የሚቻለው ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ነው ብሎአል፡፡

ጌታችን ዳግመኛ መወለድ የሚቻለው ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ነው ሲል፣ በውኃና በመንፈስ ቅዱስ በመጠመቅ ዳግመኛ መወለድ ይቻላል ማለቱ እንደሆነ ግልጽ ነው፤ እግዚአብሔር በጌታችን ሞት መነሻነት በዘረጋው ሰዎችን የማዳን አሠራር ሰዎች በፍጹም ልባቸው ሲያምኑ፣ በውኃ ሲጠመቁና በመንፈስ ቅዱስ ሲቀቡ ዳግመኛ ተወለዱ ማለት ነው፤ ዳግመኛ ልደት የሚፈጸመው በዚህ አኳኋን ነው፤ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት ዳግመኛ መወለድ ለምን አስፈለገ የሚል ጥያቄ ቢነሣ፣ ከሁሉ በፊት ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት ከኀጢአት መንጻት አለበት፤ ከዚያም በመንፈስ ቅዱስ ከብሮ መታተም አለበት፤ይህ ሲፈጸም እግዚአብሔር ተጠማቂውን ሰው በልጅነት ይቀበለዋል፤ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ተጠማቂው ሰው የእግዚአብሔር ልጅና የእግዚአብሔር የሆነውን ሁሉ ወራሽ ነው ማለትም የእግዚአብሔር የሆነውን መንግሥተ ሰማያትንና በውስጡ የሚገኙ ሕይወታዊ ስጦታዎችን ሁሉ ያገኛል፤ ይወርሳልም፤ በአንጻሩ ደግሞ ማንኛውም ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው የእግዚአብሔር ልጅ መሆን አይችልም፤ በመንግሥተ ሰማያትና በውስጡ ያሉትን ስጦታዎችም ሊያገኝ አይችልም፤ ምክንያቱም ሰውየው ከሥጋ ብቻ የተወለደ ሥጋዊ እንጂ ከመንፈስ ያልተወለደ ነው፤ ከመንፈስ ሳይወለድም የመንፈስ የሆነውን ነገር ሊያገኝ አይችልም፤ ምክንያቱም ከሥጋ፣ የተወለደ ሥጋ፣ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና የመንፈስ የሆነውን ነገር ለማግኘት ከመንፈስ መወለድ የግድ ስለሆነ ነው፤ በዚህ ምክንያት ከውኃና ከመንፈስ መወለድ ግድ በመሆኑ ጌታችን ትምህርቱን ሲያጠቃልል “ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል” ብሎ አትሞአል፡፡

ሰው በጥምቀት የሚያገኘው ሰማያዊ ሀብተ ርስት ይህን ያህል ታላቅና ለሰው ልጅ ሁሉ አስፈላጊ በመሆኑ ጌታችን ራሱ ለሁላችን መሪና አርኣያ በመሆን በእደ ዮሐንስ፣ በፈለገ ዮርዳኖስ ተጠምቋል፡፡ ጌታችን በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀ ጊዜ ሰማይ ተከፍቶአል፤ መንፈስ ቅዱስም በነጭ ርግብ አምሳል ከሰማየ ሰማያት ወርዶ በላዩ ተቀምጦአል፤ አብም በደመና ሆኖ “ይህ የምወደው ልጄ ነው” ሲል መስክሮአል፡፡ ይህ ክሥተት በእግዚአብሔር ማንነትና በሰው ልጅነት ምሥጢር ላይ ያነጣጠረ እውነታ እንደሚያንጸባርቅ ከድርጊቱ መረዳት ይቻላል፤ ይኸውም ከእግዚአብሔር ማንነት አንጻር ሲታይ እግዚአብሔር ሦስት አካላት እንዳሉት፣ የአካላት አስማትም አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ እንደ ሚባሉ፣ በእግዚአብሔር ዘንድ አባት፣ ልጅ፣ መንፈስ፣ የሚባሉ ሦስት ህልዋን አካላት እንዳሉ ግልጽ ሆኖአል፡፡ ከሰው ልጅነት አንጻር ሲታይ ደግሞ ሰው አምኖ ሲጠመቅ እግዚአብሔር በልጅነት እንደሚቀበለው፣ ሰማያዊ በሩንም ከፍቶ ወደ ዘለዓለማዊ መንግሥቱ እንደሚያስገባው ክሥተቱ ያመለክታል፤ በመሆኑም የእግዚአብሔር ማንነት ማለትም አንድነቱ እና ሦስትነቱ የተገለጸበት፣ የጌታችንም የልጅነቱ ክዋኔ የተረጋገጠበት፣ በዚያው አንጻርም የሰው መንፈሳዊ ልደት የተመሠጠረበት ዕለት በመሆኑ በዓለ ጥምቀት በግሪክ ቋንቋ ኤጲፋንያ፣ በግእዝ አስተርእዮ፣ በአማርኛ መገለጥ ይባላል፡፡ ምክንያቱም በዓለ ጥምቀተ ክርስቶስ እግዚአብሔር ስለራሱ ማንነት፣ ስለክርስቶስ አምላክነት እንደዚሁም ስለ ሰው ልጅ ልጅነት የተገለጠበትና እግዚአብሔር ወሳኝ መልእክቱን ያስተላለፈበት ዕለት ነውና፡፡

በሌላ በኩል ጥምቀት ለሰው ልጆች ድኅነት በጣም ወሳኝ ነገር መሆኑን ከምናውቅባቸው ዐበይት ነገሮች መካከል፣ ጥምቀት ለጌታችን ትምህርት መነሻና መድረሻ ወይም ርእስና መደምደሚያ ሆኖ መሰጠቱ ነው፤ ጌታችን የማዳን ትምህርቱንና ሥራውን የጀመረው በዕለተ ጥምቀት፣ በፈለገ ዮርዳኖስ በፈጸመው ድርጊት ነው፤ ያጠናቀቀውም ሊያርግ ሲል በአስተላለፈው ገዢ የጥምቀት ትምህርት ነው፤ ይኸውም ጌታችን ሞትንና መቃብርን ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ ወደ ሰማይ የሚያርግበት ቀን ሲቀርብ፣ ለደቀ መዛሙርቱ ያስተላለፈው የመጨረሻ ትእዛዝና ትምህርት “አሕዛብን ሁሉ አስተምሩ፤ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስምም አጥምቋቸው፤ ያመነ የተጠመቀ ይድናል፤ ያላመነ ግን ይፈረድበታል” የሚል ነው፤ ስለሆነም ጌታችን ትምህርቱን የጀመረና ያጠናቀቀ በነገረ ጥምቀት መሆኑን ስናስተውል፣ ጥምቀት ለድኅነታችን ያለው ቦታ ከፍተኛ መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ እንግዲህ ጥምቀት የድኅነታችን ቊልፍ ምስጢር መሆኑን ካየን ከእኛስ ምን ይጠበቃል የሚለውን ማየት ይኖርብናል፤ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን የሰው ልጅ ድኅነት የሁለትዮሽ ውጤት ነው፤ ይህም ማለት በእግዚአብሔርና በሰው ጥምር ተግባር የሚከናወን ነው ማለት ነው፤ ሰዎች ወደዱም ጠሉም፣ ተቀበሉም አልተቀበሉም ይህ የእግዚአብሔር መለኮታዊ አሠራር ነው፤ ጌታችን ሰዎችን ከልዩ ልዩ በሽታ ሲፈውስ በራሱ ፈቃድ ብቻ አልነበረም፤ የበሽተኛው ፈቃድም የተጠበቀ ነበረ እንጂ፤ ለመዳን በሽተኛው ቢያንስ ፍላጎቱን ወይም ዝንባሌውን ማሳየትና መግለጽ ይጠበቅበታል፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን ልትድን ትወዳለህን ? ይህንን እንደማደርግ ታምናለህን? ምን ላደርግልህ ትወዳለህ? እያለ ሰዎችን ሲጠይቅ የምናየው፤ ጌታችን ይህንን የሚያደርገው እውን ሰዎች የሚፈልጉትን የማያውቅ ሆኖ ነውን? ወይስ የሚጠቅማቸው ምን እንደሆነ ያውቅ የለምን? ለምን ይጠይቃቸዋል ተብሎ ቢጠየቅ መልሱ ያውቃል ነው፤ ነገር ግን በእርሱ ዘንድ የሰው ኅሊናዊ ነፃነት የተጠበቀ መሆኑንና ምርጫው የግለሰቡ መሆኑን፣ መዳን ቢሆንም ከምርጫው ውጭ በግድ መፈጸም አግባብ አለመሆኑን ለማሳየት እየጠየቀና እያስፈቀደ ያድን ነበረ፡፡

ይህ ሁሉ የሚያስገነዝበን ነገር ቢኖር መዳን በዳኑና በአዳኙ የጋራ ፈቃድ የሚከናወን መሆኑን ነው፡፡
ይህም ማለት ፍላጎት፣ ዝንባሌ፣ ተነሳሽነት፣ ታዛዥነትና በእምነት ራስን ለእግዚአብሔር ንጹሕ መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ ከሰው ይፈለጋል፤ በይቅርታና በምሕረት ተቀብሎ ማንጻት ማክበርና ተጠማቂውን በልጅነት መቀበል ደግሞ ከእግዚአብሔር ይጠበቃል፤ እነዚህ አንድ ላይ ተጣምረው ሰውን ለድኅነት ያበቁታል ማለት ነው፤ እንግዲህ የድኅነት መንገድ ይህ ከሆነ እያንዳንዳችን ክርስቲያኖች እኔስ የት ነው ያለሁ ብለን ራሳችንን በራሳችን መጠየቅና ያለንበትን ተጨባጭ ሕይወት የት እንደሆነ ማወቅ ይገባናል፤ ሕይወታችንን በዚህ አቅጣጫ ካየነው ያለንበትን ሁኔታ በትክክል እንድናውቅ ያደርገናል፤ ማወቅ ብቻም ሳይሆን በንስሐ እየታደስን ለእግዚአብሔር ልጅነታችን በሚመጥን ሃይማኖትና ሥነ ምግባር ጸንተን እንድንኖር ያስችለናል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጥምቀትን በዓል በየዓመቱ በታላቅ ሥነ ሥርዐት የምታከብረው ይህንን የመዳን አስተምህሮ እንዳይረሳና የሰው ልጆች ወደ አጥፊ ጎዳና እንዳይጓዙ ለማድረግ ነው፤ ስለሆነም የጥምቀትን በዓል ስናከብር የመዳናችንን ነገር በማሰብ፣ በእሱ ለመጠቀምም የኅሊና ዝግጅት በማድረግና እሱን ለመተግበር ቁርጥ ውሳኔ በማሳለፍ እንጂ ሥነ በዓሉ ስለማረከን፣ ወይም ባህላዊ ገጽታው ስለሚስብ፣ ወይም ሆታውና እልልታው፣ መዝሙሩና ግብዣው ስለናፈቀን መሆን የለበትም፤ የእግዚአብሔር ፈቃድ አንድ ስንኳ እንዳይጠፋ ነውና እንደፈቃዱ መኖር ይገባናል፤ የፈቃዱ ተጋሪዎች በመሆንም ራሳችንን ከጥፋት ለማዳን ዘወትር መትጋት ይኖርብናል፡፡

መልካም የጥምቀት በዓል እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32020-01-19 13:59:022025-01-28 13:59:53ጥር 11 ቀን 2012 ዓ.ም የጥምቀት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ታኅሣሥ 28 ቀን 2012 ዓ.ም፡ የበዓለ ልደት ቃለ በረከት አስተላልፈዋል Link to: ታኅሣሥ 28 ቀን 2012 ዓ.ም፡ የበዓለ ልደት ቃለ በረከት አስተላልፈዋል ታኅሣሥ 28 ቀን 2012 ዓ.ም፡ የበዓለ ልደት ቃለ በረከት... Link to: የካቲት 11 ቀን 2012 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የእነ ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን ሥልጣነ ክህነት በውሳኔ ማገዱን ቅዱስነታቸው እንደሚከተለው ገልጸዋል፡፡ Link to: የካቲት 11 ቀን 2012 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የእነ ሊቀ አእላፍ ቀሲስ በላይ መኮንን ሥልጣነ ክህነት በውሳኔ ማገዱን ቅዱስነታቸው እንደሚከተለው ገልጸዋል፡፡ የካቲት 11 ቀን 2012 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top