መስከረም 16 ቀን 2015 ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል የቅዱስነታቸው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
“ወንስእለክሙ በክርስቶስ ከመ ታሥምርዎ ለእግዚአብሔር፤
ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን በክርስቶስ እንለምናችኋለን” (2ቆሮ. 5፥20)
ይህ አረፍተ ነገር ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እግዚአብሔር ዓለሙን በክርስቶስ እንዴት እንደታረቀው ባመሠጠረበት መልእክቱ የዕርቅን አስፈላጊነት አስመልክቶ የተናገረው ነው፤ ሁላችንም እንደምናውቀው እግዚአብሔር ፍጥረታትን ሲፈጥር መልካም አድርጎ እንደፈጠራቸው ቅዱስ መጽሐፍ ይገልጽልናል፤ ይሁንና እግዚአብሔር ፍጥረታትን ውብ አድርጎ ቢፈጥርም ከፍጥረታት መፈጠር ብዙም ሳይቈይ መጋጨትና አለመግባባት ሊጀመር ችሎአል፤ በመሆኑም የፍጥረታት መጋጨት በሰው ልጆች ብቻ ሳይሆን በሕያዋን ፍጥረታት ሁሉ በአራዊቱም ሆነ በእንስሳቱ፣ በአዕዋፉም ሆነ በዓሣው፣ በጥቃቅኑም ሆነ በግዙፋኑ ሲፈጸም ማየት የዕለት ተዕለት ክሥተት ሆኖ ቀጥሎአል፡፡
ይህም ሊሆን የቻለው ቀደም ሲል ሳጥናኤል የተባለው መልአክ ቀጥሎም በእግዚአብሔር መልክና አምሳል የተፈጠረው አዳም በፈጸሙት ጥፋት ሲረገሙና ሲቀጡ፣ ፍጥረታትም አብረው የመርገሙና የቅጣቱ ተሸካሚ ለመሆን ስለተገደዱ ነው፡፡ ምክንያቱም አምላካችን እግዚአብሔር አዳምን በመርገም በቀጣበት ቀን “ርግምተ ትኩን ምድር በእንቲኣከ፤ ምድር በአንተ ምክንያት የተረገመች ትሁን” ብሎ ምድርን ሲረግማት እንመለከታለንና ነው፡፡ ይህም ማለት አዳም ሲረገም ልጆቹ ሁሉ አብረው ተረግመዋል፣ ምድር ስትረገምም በውስጧ ያሉ ፍጥረታት ሁሉ አብረው ተረግመዋል ማለት ነው፡፡
ከመርገመ አዳም አንዱ “ሦክ ወአሜከላ ይውጋእከ እሾኽና አሜከላ ይውጋህ” የሚል ይገኝበታል፤ ይህ አገላለፅ ቅኔያዊ አገላለጽ ነውና በቁሙ እሾኽና አሜከላ ሳይሆን ጠቡንና ፍጅቱን ጨምሮ በአጠቃላይ በሰው ልጆች የሚደርሰውን መንፈሳዊና ሥጋዊ መከራን ሁሉ የሚያመለክት ነው፡፡ ይህም በመሆኑ ይኸውና ዛሬም ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ ፍጥረታት በሙሉ እርስ በእርስ ሲጣሉና ሲተረማመሱ ማየት ቀዋሚ ትዕይንት ሆኖ ይገኛል፤ ይሁንና ምንም እንኳ ችግሩ በፍጥረታት ሁሉ ላይ ሰፍኖ ቢገኝም መፍትሔ የሌለው ችግር ግን አይደለም፡፡
በየጊዜው በተግባር የተፈተነ ጠንካራና የማያወላውል መፍትሔው ይቅርታና ዕርቅ ነው፣ ለሰው ልጅ አለመግባባትን በዕርቅ ዘግቶ ሰላምንና አንድነትን መሥርቶ በመከባበርና በመተሳሰብ በመተዛዘንና በመተጋገዝ በመረዳዳትና በመቻቻል በፍቅርና በሰላም ከመኖር የተሻለ ሌላ አማራጭ የለውም፡፡ ይህም እውን ሊሆን የሚችለው ለኔ ለኔ የሚል የራስ ወዳድነትን አስተሳሰብ የሙጥኝ ብሎ በመያዝ ሳይሆን ለወንድሜ ለእኅቴ የሚል ቅን አስተሳሰብ አንግቦ ያም ባይሆን ለሁላችን የሚል የጋራ አስተሳሰብ በሰዎች ልቡና የበላይነት ሲያገኝ ነው፤ ከዚህ አንጻር መስቀላዊ የሆነ ንጻሬ በተላበሰ በዚህ የዕርቅ መንፈሳዊ ኀይል ጠብ ሲሸነፍ ብዙ ጊዜ አይተናል፡፡ በዕርቅ ላይ የተመሠረተ ይህ ዐይነቱ የችግር መፍትሔ በፈጣሪ ሕግም በዓለማዊ ሕግም በሞራላዊ ሕግም ፍጹም ተቀባይነት ያለው እንደሆነ የሚክድ ይኖራል ብለን አንገምትም።
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤
ሰው በጥንተ ፍጥረት ከፈጣሪ የተሰጠው የፈለገውን የመምረጥ ሙሉ ነፃነት ያለው ታላቅ ፍጡር ከመሆኑ የተነሣ በነፃ ምርጫው እንደተሰነካከለ ሁሉ ዛሬም በነፃ ምርጫው የመስተካከል ዕድልን እግዚአብሔር አልነፈገውምና ጠብን በዕርቅ፣ በደልን በይቅርታ፣ ድህነትን በልማት፣ ክሕደትን በሃይማኖት፣ እያረመ መኖር ይችላል፤ ሰው ራሱን በራሱ ካላሰነፈ በስተቀር ይህንን ለማድረግ ዐቅሙም ችሎታውም አለው፡፡
የሰው ልጅ ችግሮችን መፍታት የሚያስችለው ብቸኛ መፍትሔ ይቅርታና ዕርቅ ብቻ እንደሆነ ካለፈውም ካለውም የሰው ልጅ ታሪክ መረዳት አያዳግትም፣ ሰው ይቅርና እግዚአብሔርም ከሰው ጋር የነበረውን ጥልና መለያየት ያስወገደው በዕርቅና በይቅርታ ነው፤ ያውም የተበደለው እሱ ሆኖ ሳለ ለበደለው ፍጡር ሲል ቤዛ ሆኖ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ “የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” በማለት ሰውን ይቅር ማለቱ የይቅርታ ዋጋ በእግዚአብሔር ዘንድ ምን ያህል ተቀባይነትና ተፈላጊነት እንዳለው በጒልሕ አሳይቶአል፡፡ ይህንን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ነገረ መስቀልን በውል የተረዳ ፍጡር ይቅርታ ተጠይቆ ይቅርና በራሱ ተነሣሽነት ወደ በዳዩ ወገን ፈጥኖ በመሄድም ሆነ ይቅርታን በመስጠት ዕርቅን መፈጸም ተራራ አይሆንበትም፤ ችግሩ የሚከሠት ያለው የነገረ መስቀሉን ምሥጢር በጥልቀት ካለማወቅ የተነሣ ወይም ቢታወቅም በተሸናፊው የእልከኝነት መንፈስ በመሸነፍ ነው፤ ከዚህ አንጻር የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ነን የምንል ሁላችን ዕርቅንና ይቅርታን ቸል የምንል ከሆነ ከምሥጢረ መስቀሉ መራቃችንን፣ ለኀጢአትም መንበርከካችንን ልብ ብለን ልናስተውል ይገባል፡፡ ኀጢአት ደግሞ ጕዳትን እንጂ የሚያመጣልን አንዳችም ጥቅም እንደሌለ መገንዘብ ያሻል፤ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናችኋለን” ብሎ እነሆ በዛሬው ዕለት ሁላችንንም ይለምነናል፡፡
የሐዋርያው ጭብጥ መልእክት ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ” የሚል ነው፤ ይሁንና ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ማለት ምን ማለት እንደሆነ አንዳንዶቻችን ላንገነዘበው እንችላለን፤ ይህንን በተመለከተ ቅዱስ መጽሐፍ ሲያስተምር ከወንድም ጋር መታረቅ ማለት ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ማለት ነው ይለናል፡፡ ከዚህ አኳያ ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ የምንችለው ከወንድማችን ጋር ስንታረቅና ስንዋደድ እንደሆነ ሐዋርያው አበክሮ ያስተምራል፤ ለዚህም ነው ቅዱስ መጽሐፍ “በአጠገቡ ያለውን ወንድሙን የማይወድ እግዚአብሔርን እወደዋለሁ የሚል ሐሰተኛ ነው፤ በአጠገቡ ያለ የሚያየውን ወንድሙን ሳይወድ የማያየውን እግዚአብሔርን እንዴት ይወደዋል? በማለት የሚያስተምረን፣ ጌታችንም ይቅር ካላችሁ ይቅር ይባልላችኋል፤ ይቅር ካላላችሁ ግን ይቅር አይባልላችሁም ብሎ አስተምሮናል፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤
እንግዲህ የመስቀልን በዓል በምናከብርበት በዚህ ቀን ከመስቀሉ መገኘት ባሻገር ማስታወስና ማሰብ ያለብን መስቀሉ ከእኛ የሚፈልገው ምንድን ነው? የሚለውን ነው፤ ትልቁ ቁም ነገርም እሱ ነው፤ የመስቀሉ ዐቢይ መልእክት በሰው ልጆች መካከል ፍጹም ሰላምና ፍቅር አንድነትና እኩልነት ይቅርታና ዕርቅ ምሕረትና አዘኔታ በምልአት ሰፍኖ፣ የሰው መንፈሳዊ፣ ሞራላዊና አካላዊ ህላዌውና ጤንነቱ ያለምንም እንከን ተጠብቆ እንዲኖር ነው፤ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ለዓለም ቤዛ እንዲሆን ሲሰጥ ፈቃዱ ይህ እንዲሆን ነው፡፡
ክርስቲያኖች ብሎም የዓለም ሕዝቦች ይልቁኑም የሃይማኖት መናኻሪያ በሆነችው በቅድስት ሀገር በኢትዮጵያ የምንኖር ክርስቲያኖችና ሃይማኖታውያን በሙሉ ይህንን የእግዚአብሔርን ፈቃድ የማወቅና የማመን የመቀበልና የመተግበር ሃይማኖታዊ ግዴታ አለብን፤ እግዚአብሔርን እናመልካለን ለሱም እንታዘዛለን ኢትዮጵያንም እንወዳለን ብለን የምንመሰክር ከሆነ የምናከናውነው ተግባር በሙሉ የእግዚአብሔርን ፈቃድና የመስቀሉን ምሥጢር የጠበቀ ሊሆን ይገባል፡፡
የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅ የምንሻም ከሆነ ባለፉት ዘመናት የሆነውን ነገር ሁሉ እንደገና ከልብ በማጤንና ሰከን ብለን በማስተዋል ወደ እግዚአብሔር መለስ ብለን እሱን ማዳመጥ አለብን፤ እግዚአብሔር ሁል ጊዜ ይናገራል፤ ለሰው ልጆች ሁሉ የሚሰማና ግልጽና ግልጽ የሆነ ቋንቋም አለው፤ እሱም ታረቁ፤ ይቅር ይቅር ተባባሉ፤ እናንተ ይቅር ስትሉ እኔም ይቅር እላለሁ፤ እንደዚሁም በረከቱንና ልማቱን አብዝቼ እሰጣለሁ፤ የምድሩን ብቻ ሳይሆን የሰማዩንም አትረፍርፌ እሰጣለሁ የሚል ነው፤ ይህንን የእግዚአብሔር ድምፅ ያልሰማ ሰው በዓለም ይኖራል ብለን አንገምትም፤ ድምፁን ሰምቶ ጆሮ ዳባ ልበስ በማለት የሚኖር ግን ብዙ ሊሆን ይችላል፤ የእኛም የዕለቱ መልእክት ሐዋርያው እንደተናገረው ከእልከኛ አስተሳሰብ እንውጣና የእግዚአብሔርን ድምፅ እንስማ እንቀበል እናክብርም በተግባርም ፈጽመን እናሳይ የሚል ነው፡፡
በመጨረሻም እግዚአብሔር ግጭቱን አስወግዶ ሰላሙን ፍቅሩን፣ አንድነቱንና ስምምነቱን እንዲያመጣልን፤ እኛም የዕርቅና የይቅርታ ሰዎች ሆነን እንገኝ ዘንድ በርትተን እንድንጸልይ አባታዊና መንፈሳዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡
እግዚአብሔር መልካም የመስቀል በዓል ያድርግልን
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡