ጥቅምት 12 ቀን 2013 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ አራተኛው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ሥነ ሥርዐት የተገኛችሁ ሁሉ፤
በማያልቅ ፍቅሩ እየጠበቀ አገልግሎታችንንም እየባረከ ሁሌ በቸርነቱ ከዘመን ወደ ዘመን የሚያሸጋግረን እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለዓመታዊው የጥቅምት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ሁላችንንም በሰላም አደረሰን፤ አደረሳችሁ!!

“ብፁዓን ገባርያነ ሰላም እስመ እሙንቱ ውሉደ እግዚአብሔር ይሰመዩ
የሚያስታርቁ ብፁዓን ናቸው፤ እነሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና።”
(ማቴ. 5፥9)

ይህ ትምህርተ ብፅዕና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሰላም፣ ስለ አስታራቂዎችና ዋጋቸውን አስመልክቶ ያስተማረው የሕይወት ቃል ነው፤ በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው የሰላም ነገር በሰማይም ሆነ በምድር በፈጣሪም ሆነ በፍጡራን ዘንድ ያለው ዋጋ ተመጣጣኝም ሆነ ተወዳዳሪ አይገኝለትም፤ በሰማይና በምድር ሰላም በጠፋ ጊዜ ሰላምን ለማምጣት ሲባል አምላክ ሰው ሆኖአል፤ ዕርቅን ለማስፈን ሲባል አምላክ በሥጋ በመስቀል ተሰቅሏል፤ በዚህም ሰማይንና ምድርን ወደ ልጁ ኅብረት አምጥቶአል፤ ዕርቁንና ሰላሙንም አረጋግጦአል፡፡ እንግዲህ ይህ ከኅሊና በላይ የሆነውን የአምላክ ሥራ ስናስተውል ሰላምና ዕርቅ፣ ስምምነትና አንድነት በአምላክ ዘንድ ያላቸው ዋጋ ምን ያህል ትልቅ እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡ በሕዝብና በሕዝብ መካከል እንዲሁም በግለሰቦች መካከል የዕርቅ ተግባር እያከናወኑ ሰላምን የሚያወርዱ ሰዎችም ዋጋቸው የእግዚአብሔር ልጅ መሆንን እንደሆነ ተናግሮ የማይከዳው አምላክ ማረጋገጫ ቃሉ ሰጥቶአል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ!ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤
ሰላምና ዕርቅ የእግዚአብሔር ተቀዳሚ ተግባራት ናቸው፤ እነዚህ ተግባራት በየቀኑ መፈጸምና መከናወን ያለባቸው የእርሱ ሉዓላዊት መንግሥት በሆነችው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፤ የመንግሥቱ ተጠሪ ደግሞ ይህ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ነው፤ ይህ ጉባኤ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ ሆኖ ስለዕርቅና ሰላም አበክሮ እንዲሠራ “ጠብቅ፣ አሰማራ” ተብሎ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሥልጣን የተሰጠው አካል ነው፤ ምክንያቱም በሰዎች መካከል ሰላም ከሌለ ቤተ ክርስቲያንም ተጎጂ ናትና ነው፤ ቤተ ክርስቲያን ልጆቿ ጠባቂ እንደሌላቸው በጎች በሰላም ዕጦት ሕይታቸውንና ንብረታቸውን ሲያጡ ከማየት የበለጠ የቤተ ክርስቲያን ጥቃት የለምና፡፡ በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ ከምንም ጊዜ በላይ በጎቹን ለመጠበቅ የሚተጋበት ጊዜ ላይ መሆኑን በውል መገንዘብ ይገባል፤ ቅዱስ ሲኖዶስ የሁሉም በጎች እኩል ጠባቂ ነውና፤ የገለልተኝነትና የማእከላዊነት አቋሙን ጠብቆ የሁሉም ወገን አባትነቱን ሳያዛንፍ ለልጆቹ ዕርቅና ሰላም መረጋገጥ ሁሉንም በአባታዊ ፍቅር እያቀፈ ማስታረቅ በዚህ ዓመት የመጀመሪያ ተግባሩ ማድረግ ይኖርበታል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ!
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
ሁላችንም እንደምናየው በቃልም ይሁን በመሠረተ ሐሳብ ዕርቅንና ሰላምን የሚቃወም ወገን ፈጽሞ የለም፤ ነገር ግን በመጓጓዣ ሐዲዱ ላይ መግባባት እየጠፋ በሀገራችንም ሆነ በዓለማችን በአጠቃላይ ብዙ ጥፋት ተከሥቶአል፤ የሚያስገርመው ነገር ቢኖር ለውይይትና ለመቻቻል ሰፊ ዕድልና ጊዜ አለመስጠቱ ነው፡፡ ጉዳዩ እጅግ ግዙፍ የሆነ የሀገር ህልውና ጉዳይ ስለሆነ በጥልቀት፣ በስፋት፣ በሰከነ አእምሮና አስተሳሰብ በተረጋጋ መንፈስ ሊታይ የሚገባው ጉዳይ ነው፡፡ አሁን እየተካሄዱ ያሉት የግጭቶች አቅጣጫዎች የሚመስሉ ትንኰሳዎች የኋላ ኋላ ምን ያህል ፀፀት እንደሚያስከትሉ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ድብቅ ምሥጢር አይደሉም፡፡ ሳንግባባ ቀርተን ትናንትና ያጋጩን ነገሮች ብዙ አሳጥተውናል፤ ለማይመለስ ፀፀትም ዳርገውናል፤ አሁንም ተመሳሳይ ስሕተት ፈጽመን ፀፀት ላይ እንዳንወድቅ የፈለገውን ያህል ጊዜ ይውሰድ የፈለገውን ያህል ዋጋ ያስከፍል ያለአንዳች ግጭትና ደም መፍሰስ ሁሉም ነገር ወደዕርቅ፣ ወደሰላምና አንድነት ማምጣት አለብን፤ በነገሩ ላይ ሸማግሌ ከገባበት እግዚአብሔርም ከተጋበዘበት የውይይት ጊዜና ትዕግሥትም ከታከለበት ሁሉም ነገር እየዋለ እያደረ የሰላም ጎሕ እየፈነጠቀ መረጋጋት ሥር እየሰደደ፣ ጥላቻ እየተናደ እንደሚሄድ ጥርጥር የለውም፤ «ዕለት ለዕለት ትጐሥዕ ነቢበ፤ ወሌሊት ለሌሊት ታየድዕ ጥበበ — አንዷ ዕለት ለሌላኛዋ ዕለት መልካም ንግግርን፣ በጎ ሐሳብን ታመነጫለች፤ አንዷ ሌሊትም ለሌላኛዋ ሌሊት የበለጠ ጥበብና ማስተዋልን ትወልዳለች» የሚለው የእግዚአብሔር ቃልም ይህንን ያረጋግጣልና ነው፡፡ በዚህ መንፈስ ጠንክረን ከሠራን ፍሬ እናጣለን ተብሎ አይገመትም፤ ስለሆነም ይህ ዐቢይ ጉባኤ እንደካሁን ቀደሙ ኮሚቴ አቋቁሞ መለያየት ሳይሆን የሀገር ሰላም ጉዳይ በቀጥታ ይመለከተናል በሚል ቅን መንፈስ፣ በተቃርኖ ያሉ ኀይሎችን በግንባር በማግኘትና በማነጋገር የአንድ ሰው ሕይወት እንኳ እንዳይጠፋ ሁሉም የበኩላቸውን እንዲወጡ ጠንክሮ መማፀን አለበት፡፡ የሁሉም ምርጫ ውይይትና ውይይት ብቻ እንዲሆንም በርትቶ በመሥራት ሁሉንም ማሳመን አለበት፤ ከዐቅሙ በላይ ከሆነም ልምዱና ጥበቡ ያላቸው ሀገር ዐቀፍና ዓለም ዐቀፍ ገለልተኛ ወገኖችን በማሳተፍ የዕርቁና የሰላሙ ተልእኮ ግብ እንዲመታ ማድረግ አለበት፤ ይህ ተግባር ወቅቱ ኀላፊነት የጣለበት የቅዱስ ሲኖዶስ ተቀዳሚ ተግባር ነው፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ !
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያናችንን ለከፋ አደጋ የዳረጋት መሠረታዊ ምክንያት የአክራሪዎችና የተቃራኒዎች እንቅስቃሴ መሆኑ በውል ማወቅ አለብን፤ ይሁን እንጂ የእኛ አያያዝም በክፍተት የተሞላ በመሆኑ ከተቃራኒ አካላት ባልተናነሰ ሁኔታ እያስጠቃን ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን የሚታዩ ልዩ ልዩ የአሠራር ጒድለቶች ማለትም የአስተዳደር ስልታችን የፋይናንስና የንብረት አያያዛችን ምእመናንን እያበሳጩብን እንደሆነ አንዘንጋ፤ በመሆኑም እነዚህንና ሌሎች ችግሮቻችንን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማስተካከል ዕውቀቱ፣ ልምዱና ችሎታው ባላቸው ባለሙያዎች በጊዜያዊም ቢሆን መድበን በጥናት ላይ የተመሠረተ መሪ ዕቅድ ዘመናዊ አሠራርን አዘጋጅተው እንዲያቀርቡልን ማድረግ አለብን፡፡ በሠላሳ ዘጠነኛው የሰበካ ጉባኤ ስብሰባ ላይ እንደተጠቀሰው ቤተ ክርስቲያናችን በከባድ ፈተና ላይ መሆኗ ተገልጾአል፤ ስለሆነም ይህ የጥፋት ድርጊት እንዲቆም ሁነኛ መፍትሔ ማስቀመጥ ይኖርብናል፡፡
በመጨረሻም አዲሱ ዓመት ጠንካራ የዕርቅና የሰላም ሥራ ሠርተን ልጆቻችንን ከሥጋትና ከጥፋት የምንታደግበት ይሆን ዘንድ በርትተን እንድንሠራ ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሁሉ ልባዊ ጥሪያችንን በእግዚአብሔር ስም እያስተላለፍን፣ ዓመታዊውን የጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በዛሬው ዕለት ባርከን በጸሎት የከፈትን መሆናችንን እናበሥራለን፤ ጉባኤያችንን ጉባኤ ሐዋርያት፣ ጉባኤ አበው ቅዱሳን ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፤ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!!

ጥቅምት 3 ቀን 2013 ዓ.ም. 39ኛው ዓለም ዐቀፍ አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
ከልዩ ልዩ የሥራ ዘርፍ ተወክላችሁ በዚህ ዓመታዊና ዓለም አቀፋዊ ጉባኤ የተገኛችሁ ክቡራንና ክቡራት በአጠቃላይ፤ሁሉንም ማድረግ የሚችል እግዚአብሔር አምላካችን መከራውንና ፈተናውን አስችሎ በዚህ ታላቅ ጉባኤ ስለሰበሰበን ስሙ የተመሰገነ ይሁን!!
‹‹ወይኩን ቅኑተ ሐቌክሙ ወኅትወ መኃትዊክሙ
ወገባችሁ የታጠቀ፣ መብራታችሁም የበራ ይሁን።››
(ሉቃ. 12፥35)

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን ኀይለ ቃል የተናገረውና ያስተማረው ለቅዱሳን ሐዋርያት እንደሆነ ሁላችንም እናውቃለን፡፡ ትምህርቱ ለጊዜው አጠገቡ ለነበሩት ሐዋርያት የተነገረ ቢሆንም ፍጻሜው እስከ ዕለተ ምጽአት ለሚነሡ ደቀ መዛሙርት ሁሉ እንደሆነም እናውቃለን፤ ከእነሱ ውስጥ በአሁኑ ጊዜ በየደረጃው በኀላፊነት የምንገኝ ደቀ መዛሙርትም ቃሉ በቀጥታ እንደሚመለከተን አንዘነጋውም፡፡

በመሆኑም ከዚህ እውነታ ተነሥተን፣ ጌታችን ‹‹ወገባችሁ የታጠቀ፣ መብራታችሁም የበራ ይሁን›› ሲል እኛን ያዘዘበትና ያስተማረበት ምክንያት ምን ይሆን? የሚለውን ጥያቄ አንሥተን ማየት ከሁላችንም ይጠበቃል፡፡ ሁላችንም እንደምንገነዘበው የትጥቅ ነገር የሚነሣው ተቃራኒ ኀይል ራስን ወይም ወገንን ለማጥቃት እንደተዘጋጀ ሲታወቅ ነው፤ መብራትን ማብራት የሚያስፈልገውም ጨለማ መኖሩ ሲታወቅ ነው፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አፅራር ምንጊዜም የማይተኙ መሆናቸውን በአምላክነቱ ኀይል የሚያውቅ እግዚአብሔር አምላካችን ሁሌ ወገባችንን ታጥቀን መንጋውን እንድንጠብቅ አዞናል፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ብርሃናዊት፣ ሰማያዊትና ዘለዓለማዊት ብትሆንም ለጊዜው ያለችው ጠላት በብዛት ባለበትና በጨለማው ዓለም ውስጥ ነውና በጠላት እንዳትጠቃ በጨለማውም እንዳትዋጥ ሁልጊዜ መብራት እንድናበራላት ታዘናል፤ ይህ የእኛ የክርስቲያኖች ቀዋሚና መደበኛ ሥራችን ነው፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታሪዎች፤ በአሁኑ ጊዜ በቤተ ክርስቲያናችን ላይ እየደረሰ ካለው መከራ አንጻር ከምንም ጊዜ በላይ ታጥቀን ለቤተ ክርስቲያን ህልውና መቀጠልና ለሕዝበ ክርስቲያኑ የሕይወት ዋስትና መረጋገጥ በአንድነት የምንቆምበት ጊዜ ነው፤ለሦስት ሺሕ ዘመናት ሀገርን የገነባችና የጠበቀች ሁሉንም በእኩልነት ያስተናገደች በማንም ላይ ግፍን ያልፈጸመች ቤተ ክርስቲያናችን ዛሬ ከገጸ ምድር እናጥፋሽ የሚሉ በምሥራቅም በምዕራብም እየተበራከቱ መጥተዋል፡፡ ከዛሬ ነገ ይሻል ይሆናል፤ ፍትሕም ይገኝ ይሆናል እያልን በተስፋ ብንጠባበቅም ሲሆን አናይም፤ ይልቁንም ከጊዜ ወደ ጊዜ ነገሩ እየተባበሰ፣ ክርስቲያን ልጆቻችንም ለተደጋጋሚ ጥቃት እየተዳረጉ በክርስቲያንነታቸው ብቻ የግፍ ግፍ እየተፈጸመባቸው ይገኛሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በተለያዩ ጊዜያት ባደረገችው ጥሪ ከልዩ ልዩ በጎ አድራጊዎችና ከሕዝበ ክርስቲያኑ ለተጐዱ ምእመናን የተወሰነ ድጋፍ ለማድረግ ቢሞከርም ከችግሩ ስፋት የተነሣ የሚያረካ አልሆነም ፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፤አበው ሲናገሩ ‹‹ከራስ በላይ ነፋስ›› እንደሚሉት ቤተ ክርስቲያናችን እየገጠማት ያለውን ችግር ለመቋቋም ልጆችዋን አስተባብራና አደራጅታ ራስዋን በራስዋ ወደመጠበቅ አማራጭ ካልተሸጋገረች ዕጣ ፈንታዋ እጅግ አስጊ እየሆነ መጥቶአል፤ ክርስቲያን ልጆቻችን ተሸማቅቀው፣ ነጻነታቸው ተገፎ፣ በሀገራቸውና በወገናቸው መካከል የመኖርና ሃይማኖታቸውን የመከተል መብት አጥተው ባሉበት ሁኔታ ቤተ ክርስቲያንን እየጠበቅን ነው ማለት አይቻልም፡፡ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያንን የመጠበቅና የማጽናናት ኀላፊነት ከሁሉ በፊት በቅዱስ ሲኖዶስ ጫንቃ ላይ ያረፈ እንደመሆኑ መጠን በኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የሚዘንበውን መከራ ለመግታት ቅዱስ ሲኖዶስ በዚህ ጉባኤ ተገቢውን መፍትሔ ማስቀመጥ ይጠበቅበታል፤

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው አባላት፤“በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” እንደሚባለው ሁከት፣ ለዘመናት ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ የአንበጣ መንጋና ልዩ ልዩ መቅሠፍት በበዛበት በአሁኑ ጊዜ አንድ ላይ ሆነን በመቆም ሕዝበ ክርስቲያኑን በመጠበቅ ፈንታ ሌላ ተቀጥላና የቤተ ክርስቲያንን ዐቅም በመከፋፈል ለማዳከም በውስጣችን የሚደረጉ ሤራዎችም ለቤተ ክርስቲያን አንድነትና ጥንካሬ ከባድ ዕንቅፋቶች እየሆኑ መምጣታቸው ሌላ የጥፋት ገጽታ ሆኖ እየታየ ነው ፡፡እንደ እውነቱ ከሆነ እንደዚህ ያለው ድርጊት ለዘመናት ቤተ ክርስቲያናችንን ሲፈታተኑ የነበሩ የውጭ ኀይሎች በረቀቀ ስልትና በእጅ አዙር ቤተ ክርስቲያናችንን ሊያፈራርሱ የጠነሰሱት ተልእኮ እንጂ ላይ ላዩ አጥባቂ የኦርቶዶክስ ተከታይ መሳይ ውስጡ ግን ኦርቶዶክስን በመከፋፈል ማዳከምና ማፍረስ የሆነ ድርጊት የንጹሓን ኦርቶዶክሳውያን ተግባር ይሆናል ብለን አናምንም፤ ይህንን ደባ ሁላችንም ልናጤነው ይገባል ፡፡ለዚህ ማሳያ የሚሆነው በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት የተፈጸመው ሕገ ወጥና ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ የሆነ የኤጲስ ቆጶሳት ሢመት ይገኝበታል፤ እንደዚህ ያለ ድርጊት የሁለት ሺሕ ዘመን ሐዋርያዊ ቀኖና እና ሥርዐት ባላት ቤተ ክርስቲያናችን ቀርቶ በየትኛውም ቦታና ጊዜ ተደርጎ የማያውቅ ድፍረትና ስሕተት ነው፡፡ በመሆኑም ለዚህ ድርጊት መነሻ የሆኑ ምክንያቶችና የምክንያቱ ሰለባ የሆኑ፣ እንደዚሁም ሳይላኩና ሥልጣኑ ሳይኖራቸው ዳግም ጥምቀትን ዳግም ክህነትን በማወጅ ለዚህ አደጋ መከሠት ምክንያት የሆኑ ሁሉ በማያዳግም ሁኔታ ይህ ጉባኤ የማስቆሚያ መፍትሔ እንዲያበጅላቸው በዚህ አጋጣሚ አጥብቀን እናሳስባለን፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፤የቤተ ክርስቲያናችን ልጆች ዛሬ በብዙ መልኩ እንግልት ላይ ወድቀው ማየት የተለመደ ሆኗል፤ ብዙ ወጣት ልጆቻችን ለእንጀራ ፍለጋ ሲሉ ሃይማኖታቸው ወደማይወደድበት ሰብኣዊ መብታቸው ወደማይከበርበት፣ የንብረትም ሆነ የሕይወት ዋስትና ወደሌለበት ሀገር በመሰደድ የምድር ሲኦል እየለበለባቸው እንደሆነ እያየን ነው፤ ይህንን እየተመለከትን ተኝተን የምናድር ኢትዮጵያውያን ካለን ክርስቲያንነቱንም ሰብኣዊነቱንም ዘንግተነዋል የሚያሰኝ ነው፤ ስለሆነም ልጆቻችን በባዕድ ሀገር ራቁታቸው እንደቅጠል እየረገፉ ከማየት የበለጠ (የከፋ) አንገትን የሚያስደፋ ውርደት ስለሌለ ሀገር ዐቀፍና ዓለም ዐቀፍ የሰብኣዊ መብት ተቅዋማት፣ የኢፌዲሪ መንግሥትና መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚገባውን ሁሉ በማድረግ ልጆቻችን ወደሀገራቸውና ወደቤተሰቦቻቸው በአስቸኳይ እንዲመለሱ ያደርጉ ዘንድ ቤተ ክርስቲያን ድምፅዋን ከፍ አድርጋ ማሰማት አለባት የበኩሏን ድጋፍ ለማድረግም መዘጋጀት አለባት፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፤የሰው ልጅ በተፈጥሮው ምግብና መጠጥ ልብስና መጠለያ እንደሚሻ ሁሉ ከዚህ ባልተናነሰ ሁኔታ የእኩልነት፣ የመብትና የፍትሕ ፍላጎቱም የላቀ ነው፤ እነዚህ ፍለጎቶቹን ባጣ ጊዜ ያላስፈላጊ ሁከትና ግጭት ይፈጠራሉ፤ በዓለማችንም ሆነ በሀገራችን የሚታዩ አለመግባባቶች ይብዛም ይነስ ከዚህ የሚመነጩ ከመሆን አያልፉም፤ እነዚህ ነገሮች በተቻለ መጠን ካልተከበሩ ውጤቱ ጥሩ እንደማይሆን እያየን ነው፤ በመሆኑም በሀገራችን ያለው ያልተረጋጋ ሁኔታ ያልሆነ መልክ እንዳይዝ መንግሥታችንና የሀገራችን ተፎካካሪ ፓርቲዎች ወንድማማቾች እንደመሆናቸው መጠን ምንም ልዩነት ሳይኖር በክብ ጠረጴዛ ሆነው በመመካከር ችግሮችን ሁሉ እንዲፈቱ እንጂ ወደ አላስፈላጊ ሁኔታ እንዳይገቡ ቤተ ክርስቲያናችን በገለልተኝነትና በእናትነት መንፈስ ማገዝ አለባት፤ ማስታረቅም ማስተማርም አለባት፤ ሁሉም ነገር በሰላምና በውይይት ብቻ እንጂ ከዚህ ባፈነገጠ መልኩ የሚደረግ አማራጭ ከጒዳት በቀር ውጤት አናገኝበትም፤ ከዚህ ጎን ለጎንም ፍትሕና ርትዕ እንዲሰፍን፣ ፍትሕ የተነፈጋቸው ወገኖች ካሉ ፍትሕ እንዲያገኙ ቤተ ክርስቲያን በማእከል ሆና የመምከር ሥራ መሥራት አለባት፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፤ከዚህ በላይ የጠቃቀስናቸው ችግሮች በሀገራችን ሥር እየሰደዱ የመጡበት ምክንያት በርከት ያለ ቢሆንም የድህነት ጉዳይ የአንበሳውን ድርሻ እንደሚወስድ አያጠራጥርም፤ ወጣት ልጆቻችን ሥራና ዳቦ ባጡ ቊጥር ሌላውን አማራጭ በመከተል ሲታክቱ እነሆ በጣም በርካታ የሆኑ ዓመታት ተቈጠሩ፤ ስያሜውና አቀራረቡ ቢለያይም ከሕገ ንጉሣዊ ሥርዐት ማክተም ማግሥት ጀምሮ የተደረጉ እንቅስቃሴዎች ሁሉ ፀረ ድህነት የሚል አንድምታ ይዘው የተደረጉ ናቸው፣ ሆኖም ይቀረፋል የተባለው ድህነት ባለመቀረፉ፣ በዚያም ላይ ሌሎች ነገሮች በመካከሉ እየተሰነቀሩ ጒዞአችንን የኋልዮሽ አድርገውታል፡፡ ስለሆነም ድህነትን በእዕድገት በመቀየር ረገድ ቤተ ክርስቲያን በልማቱ፣ በድህነት ማጥፋቱና በሰላም ማረጋገጡ ዙሪያ በርትታ መሥራት ይጠበቅባታል፤ ሰበካ ጉባኤ የተቋቋመውም ሕዝቡ በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያኑ በአንድ ወጥ አደረጃጀት ተሰባስቦ አረጋውያንን በመጦር፣ ሕፃናትን በማስተማርና በመንከባከብ፣ የራስ አገዝ ልማትን በማስፋፋት፣ ለወጣቱ ትውልድ ሥራ በመፍጠርና የተሟላ መንፈሳዊ አገልግሎት ለመስጠት እንደሆነ ይታወቃል፤ ከዚህ አንጻር ሰበካ ጉባኤ ከተቋቋመበት ዘመን አንሥቶ የተገኘው እድገት የማይናቅ ቢሆንም መጓዝ የሚገባውን ያህል እንዳልተጓዘ፣ ያለውም ሀብት በአግባቡ እንዳልተያዘ የአደባባይ ምሥጢር ነው፤ ከዚህም ሌላ ሌሎች ደባል ቡድኖች በየአካባቢው ሲፈጠሩ ለቤተ ክርስቲያን አንድነትና ለምጣኔ ሀብት መባከን ያለው አደጋ ሳይጤን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ፈቃድ እየሰጠን በየፊናው ያሰማራናቸው ሁሉ በስመ ቤተ ክርስቲያን እየተሰበሰቡና ገንዘብ እየሰበሰቡ በርከት ያለ የምእመናን ሀብት እንደሚባክን መረጃዎች አሉ፤ ይህም የሚከናወነው በሀገር ውስጥና በውጭ ጭምር ነው፤ ቅዱስ ሲኖዶስና ሕዝበ ክርስቲያኑ ይህንን ድርጊት አርሞና አስተካክሎ መልክ ካላስያዘ በቀር ጒዳቱ የቤተ ክርስቲያንን ምጣኔ ሀብት ብቻ ሳይሆን አንድነትዋንና ህልውናዋንም ጭምር ከባድ አደጋ ላይ የሚጥል ይሆናል፤ በታሪክም ተወቃሽነትን ያስከትላል ስለዚህ እኛ የምንለው አሁንም መፍትሔ እናበጅለት ነው፡፡

በመጨረሻም፤ ይህ ዓመታዊና ዓለም አቀፋዊ የጠቅላላ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፣ የቀረቡትን ዐበይት ጒዳዮች በጥልቀትና በማስተዋል ተመልክቶ ለወሳኙ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ግብአት የሚሆን የውሳኔ ሐሳብ እንዲያስተላልፍ በማሳሰብ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን ፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ጉባኤያችንን ይባርክልን፤ ይቀድስልን፤
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ፤ይቀድስ፤
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡