መጋቢት 22 ቀን 2011 ዓ.ም በዓለ ደብረ ዘይት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ በተለያዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ልጆቻችን በሙሉ፤
ፈታሒ በጽድቅ ኰናኒ በርትዕ የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለበዐለ ደብረ ዘይት በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ።
“ወባሕቱ ጸልዩ ከመ ኢይኩን ጕያክሙ በሰንበት ወበክረምት
ሽሽታችሁ በሰንበትና በክረምት እንዳይሆን ጸልዩ።”
(ማቴ. 24፥20)
የችግሮች ሁሉ ቊልፍ መከላከያ የሆነው ይህ የጸሎት አስተምህሮ፣ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ተቀምጦ ለቅዱሳን ሐዋርያት፣ በይቀጥላልም ለእኛ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ሁሉ ያስተማረው ዐቢይ ትምህርት ነው፡፡ በግዘፍ የሚታዩት የምልአተ ዓለም (ዩኒቨርስ) ክፍለ ዓለማትና በውስጣቸው የሚገኙ ሥጋውያንና ደማውያን ፍጡራን በሙሉ፣ መጨረሻ እንዳላቸው የእግዚአብሔር እስትንፋስ ያለባቸው የብሉይ ኪዳንና የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት በእርግጠኝነት ይናገራሉ፡፡
ከሁሉ በላይ ደግሞ ዓለማትን በሙሉ የፈጠረ የእግዚአብሔር አካላዊ ቃል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ በምልአተ ዓለም የሚገኘው ግዙፍ ፍጥረት በሙሉ ሰማያትና ምድርም ጭምር መጨረሻ እንዳላቸውና በኅልፈት ታሪካቸውና ህልውናቸው እንደሚዘጋ አበክሮ ተናግሮአል፤ ለእኛም አሳውቆናል፤ ጌታችን የዓለምን ፍጻሜ የሚያስረዳይህንን ትምህርት ሲያስተምር ዘመኑን ቀኑንና ሰዓቱን ለይተን ልናውቅ እንደማንችል ከመግለጹ ባሻገር ያለን አማራጭ ዕድል ሁል ጊዜ ተዘጋጅቶ መኖር ብቻ እንደሆነ አጥብቆ አስተምሮናል፡፡
ጌታችን የዓለም ዕድሜ የሚጠናቀቅበት ዓመት እንዲሁም ቀንና ሰዓት ልናውቅ እንዳልተፈቀደ ቢያስተምርም የዓለም ፍጻሜ መቃረብን የሚጠቁሙ ግዙፍና ተጨባጭ ምልክቶች እንደሚከሠቱ ግን በግልጽ አሳውቆናል፡፡ በአጠቃላይ የዓለም ፍጻሜ እየተቃረበ ሲመጣ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ሆኖ የማያውቅ አሰቃቂና አስጨናቂ መከራ በዓለም ላይ እንደሚከሠት በሚገባ አስተምሮናል፤ ከምልክቶቹ መካከልም የሚከተሉት በዋናነት ተጠቅሰዋል፤ እነሱም፡ ቅዱስ ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፤ ብዙ ሐሰተኞችና አስመሳይ የክርስትና መምህራን ይመጣሉ፤ እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስመ ክርስቶስ የሚሰብኩ ሐሰተኞች በየአካባቢው ይነሣሉ፤ ረኃብ ቸነፈር የምድር መንቀጥቀጥና መናወጥ በተደጋጋሚ ይከሠታል፤ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ለጦርነት ይሰላለፋሉ፤ የጦርነት ድምጽ በየአቅጣጫው ይሰማል፤ ከዐመፅና ከክፋት የተነሣ ፍቅር ከሰዎች ትጠፋለች፤ ብዙ ሰዎች ሃይማኖታቸውን ይክዳሉ እርስ በርሳቸውም ይጣላሉ፤ ሃይማኖታውያን ክርስቲያኖች ስሙን በመጥራታቸው ብቻ ይጠላሉ፤ ሐሰተኞቹ መምህራን ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ነገሮችን በማሳየት ብዙ ክርስቲያንን ያስታሉ የሚሉት ናቸው፡፡ እነዚህ ምልክቶች በሚከሠቱበት ጊዜ የሰው ልጅ በሰላም ገብቶ በሰላም መውጣት አጥቶ፣ ዕለታዊ ኑሮው ተበጥብጦ፣ ህልውናው እንደሚቃወስ፣እጅግ አስቸጋሪ ሁኔታም እንደሚፈጠር ጌታችን በደብረ ዘይት ትምህርቱ ላይ በማያሻማ ሁኔታ አስተምሮናል፤ እንዳትሳሳቱ ተጠንቀቁ ብሎም አስጠንቅቆናል፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤
ጌታችን በዓለም ፍጻሜ የሚሆነውን ከባድ መከራ ብቻ ሳይሆን ልናደርገው የሚገባን ጥንቃቄንም በሚገባ ከማስተማሩም ሌላ ልናደርጋቸው ከሚገቡ ጥንቃቄዎች መካከል የሚከተሉትን ነግሮናል እነርሱም፡ (1) ሁልጊዜ ትዕግሥትን አጥብቀን በመያዝና በዚያው በመጽናት መዳን የምንችል መሆኑን እንድናውቅ፣ (2) ክርስቶስ እዚህ አለ እያሉ የሚያሳስቱ የሐሰተኞች ክርስቲያኖች ትምህርትንና የሚያደርጓቸው ታላላቅ ድንቅ ምልክቶችን ማመንና መቀበል ፈጽሞ እንደሌለብን፣ (3) የክርስቶስ ምጽአት መብረቅ ከምሥራቅ ሲወጣ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ እንደዚሁ በግልጽ ይሆናል እንጂ በእልፍኝ ወይም በሌላ ስፍራ በድብብቆሽ አለመሆኑን ዐውቀን እንድንጠነቀቅ፣ (4) የዓለም ፍጻሜና የጌታ መምጫ ቀን ለይተን ማወቅ ስለማንችል ሁልጊዜ ተዘጋጅተን እንድንኖር፣ (5) በሰንበትና በክረምት የሚሸሽ ሰው ማምለጥ እንደማይችል ሁሉ ሃይማኖትና ሥነ ምግባር የሌለው ሰውም ከመከራ አያመልጥምና በሃይማኖትና በሥነ ምግባር ጸንተን በጸሎት እንድንተጋ አስተምሮናል፡፡ ጌታችን መከራው ሊሆን ግድ ነው ካለ በኋላ፣ በመከራው ከሚመጣ ጥፋት ለመዳን ምን ምን ማድረግ እንዳለብን እነሆ በግልጽ አስተምሮናል፤ በመሆኑም “ማወቅ ለመጠንቀቅ” እንደሚባለው ጌታችን መከራውንም የመከራውንም ማምለጫ አስቀድሞ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ አስተምሮናልና ልናዳምጠው ልንሰማውና ልንጠቀምበት ይገባል፡፡ በየቀኑ የምንሰማውና የምናየው የዓለማችን ሁኔታ ጌታችን ከነገረን ምልክት ጋር በእጅጉ የተቀራረበ ሆኖ እንደሚታይ ለሁሉም ግልጽ ነው፤ በመሆኑም የጌታችን ገዢ አስተምህሮ “ሁልጊዜ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ” የሚል ከመሆኑ ጋር ምልክቶቹ በዝተውና እንደቃሉ ሆነው ስናያቸው ይበልጥ መጠንቀቅ እንዳለብን ሳናሠምርበት አናልፍም፡፡
የጌታችንን ቃል ልብ ብለን አስተውለነው ከሆነ እኛ ኢትዮጵያውያንም ከዚህ የመከራ ገፈት ውጭ የሆን አይመስልም፡፡ በሀገራችን ውስጥ፣ ታላላቅ ምልክቶችና ድንቅ ነገሮችን እናደርጋለን፣ ትንቢት እንናገራለን፣ ፈውስም እንሰጣለን የሚሉ ሐሳውያን በእጅጉ ተበራክተዋል፡፡ በሀገራችን ፍቅር እየቀዘቀዘ፣የግጭት ሁኔታ እየተበራከተ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ መቃቃርንና መጠራጠርን እያሳየ ነው፡፡ ብዙ ሐሰተኞች መምህራን ብዙ ክርስቲያኖችን እያሳሳቱ ሃይማኖታቸውን እንዲክዱ እያደረጉ ነው፡፡ ጠብ ጥላቻ መለያየትና ረኃብ እንዳለ እየተሰማ ነው፤ እየታየም ነው፤ እነዚህ ሁሉ ለዋናው መከራ የምጥ ጣር ናቸው ብሎ ጌታችን እንደ ነገረን ሁኔታዎቹ በኅሊናችን የሚጭሩት ነገር አለና በተሰጠን የመፍትሔ አማራጭ መጠቀም ግድ ይለናል፡፡
በተለይም በሃይማኖትና በሥነ ምግባር ጸንቶ፣ ለትዕግሥት ተገዝቶ ነገሮችን በፍቅር ማሸነፍ፣ በጸሎትም መትጋት አሁን በሀገራችን እየተከሠተ ላለው ችግር ቁልፍ መፍትሔዎች ናቸው፤ ከጥንት ጀምሮ የኢትዮጵያ ኀይል እግዚአብሔር እንጂ ሌላ ሰው ሠራሽና ተገለባባጭ የውጭፖለቲካዊ ፍልስፍና አልነበረም፤ሰው ሠራሽ የፍልስፍና ፖለቲካዊ አስተሳሰብ ወደ ሀገራችን ባልገባበት ወቅት ኢትዮጵያ ከሁሉ በላይ በሆነ በእግዚአብሔር ኀይል ብቻ ትጠበቅ ስለነበረች አሁን ላጋጠመን የሃይማኖትና የሥነ ኅሊና ውድቀት ሳትንበረከክ ረጅም ዘመናትን አሳልፋለች፡፡ ይህንም ስንል ጠቃሚ የሆኑ ነገሮችን ፈጽሞ መቀበል የለብንም ማለታችን አይደለም፤ የነበረንን የኛው ታላቅ ነገርን ትተን የሌላውን ብቻ ተቀብለን ለመሮጥ የምናደርገው አካሄድ ማረም አለብን ማለታችን ነው፤ በነበረን መልካም እሤት ላይ ጠቃሚ የሆነውን ዕውቀት ከእኛው ነባር ጥበብ ጋር አጣጥመንና እንደጋቢ ደርበን መጠቀም አለብን እንጂ፣ የነበረንን የሚያሳጣ ነገር ብቻ መከተሉ አያዋጣም ነው እያልን ያለነው።
ሀገራችን የነበሯት ድንቅ ዕሴቶች በሃይማኖት እግዚአብሔርን መፍራት፣ ሃይማኖትን መሠረት ያደረገ የአንድነት፣ የመቻቻልና እየተረዳዱ እየተጋገዙ በፍቅር መኖር፣ በኢትዮጵያዊ ቅዱስ ባህልና ውርስ ተሳስሮ ተከባብሮና ተፈቃቅሮ መኖር፣ ሁሉንም በይቅርታ እየተዉ መሄድ፣ ለባዕድና ለመጤ ባህል፣እንደዚሁም ለሃይማኖት ተጋፊ አለመንበርከክ፣ ችግሮችን ሁሉ በሃይማኖት መሪዎችና በሀገር ሽማግሌዎች ምክር እየፈቱ በፍቅር መርሕ ይቅር ይቅር መባባል፣ ታጋሽና አርቆ ተመልካች መሆን፣ ቂም በቀልን መጸየፍ መተኪያ የሌላቸው ውድ የሀገራችን ድንቅ ዕሤቶች ናቸው፤ አሁን የመጣብን ጣጣ እነዚህን ዕሴቶች ንቀንና ትተን ጆሮዎቻችንና ኅሊናችንን ለባሕር ማዶ ባህሎችና ፖለቲካዊ ፍልስፍናዎች ብቻ ከፍተን ስለተገኘን፣ በተገኝው ቀዳዳ ሁሉ ባዕዳን ለራሳቸው ድብቅ ዐላማ በሚያመች ሁኔታ እኛን እየከፋፈሉ፣ በውስጥ ጉዳያችንም ጣልቃ እየገቡ እርስ በርሳችን ሊያናቁሩን እየተጉ እንደሆነ ልንዘነጋው አይገባም፡፡
በአሁኑ ጊዜ ለኢትዮጵያውያን የሚበጀን ነገር ቢኖር የሚያኮሩንና አንድ የሚያደርጉን ብዙ ዕሴቶች ስላሉን እነሱን ተከትለን ችግራችንን ሁሉ በትዕግሥት፣ በይቅርታና ቂም በቀልን ፈጽሞ በመተው አንድነታችንን ማጠናከር ላይ ማተኮር ነው፤እኛ አንድ ከሆን በኋላ የሚጠቅመን የውጭ የአስተዳደር ብሂል ካለ ማስተዋል ባልተለየው የጋራ ውይይት ባለን ላይ ደርበን መጠቀም እንችላለን፡፡ የመለያየት ጎጂነቱ በማያሻማ ሁኔታ ታውቆ፣ ለብዙ ዘመናት ተለያይው የነበሩ ሀገራት በአህጉር ደረጃ ተሳስረው፣ ፓለቲካዊ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅማቸውን በጋራ ለማሳደግና በጋራ ለመጠቀም በሚተባበሩበት በአሁኑ ዘመን፣ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ አብረን የነበርን እኛ ኢትዮጵያውያን ቂም በቀልን መተው አንለምድ ብለን፣ የውጭ ጣልቃ ገቦችን ቅስቀሳ ጆሮ ዳባ ልበስ ማለት አቅቶን ችግራችንን ራሳችን በራሳችን በይቅርታና በውይይት ማስወገድ ተስኖን ታሪካችንን ጥላሸት እንዳንቀባውና ታላቋ የእግዚአብሔር ሀገር ኢትዮጵያን ፈተና ላይ እንዳንጥላት በእጅጉ መጠንቀቅ አለብን፡፡
በአሁኑ ጊዜ የተሻለችና አንድነቷ አስተማማኝ የሆነች ኢትዮጵያን ለማስቀጠል ሲባል ሁሉንም ነገር መተው ከሁሉም ኢትዮጵያውያን ይጠበቃል፤ ቂም በቀልን፣ የጥላቻና ጽንፈኛ አስተሳሰብን፣ ያለፉትን ግድፈቶች እየተረኩ ቅራኔ ማባባስን ጭራሽ ማቆም አለብን፤ ያለፈውን ትተን ወደፊት በአንድነት ለመቀጠል ምርጫችን ካላደረግን የሚገጥመን ነገር ጥሩ አይሆንም፤ በመሆኑም ሁላችንም ኢትዮጵያውያን የነበረንን ፈሪሀ እግዚአብሔር ተላብሰን፣ ቂም በቀልን በመተው፣ ይቅር ባይነት ከሁሉም የላቀ ጠቃሚያችን መሆኑን ተገንዝበን ወደዚሁ አስተሳሰብና እምነት መምጣት አለብን፡፡
በመጨረሻ፤ በበዐለ ደብረ ዘይት ዕለት ለመላ ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን የምናስተላልፈው ዐቢይ መልእክት የኢትዮጵያ አንድነትና እድገት የሚረጋገጠው ከሁሉ በፊት ቂምን፣ በቀልንና ጭፍን ጥላቻን ትታችሁ፣ ሁሉንም በይቅርታና በመተው ተቀብላችሁ ለወደፊቱ የተሻለችና አንድነትዋ የጠነከረ ኢትዮጵያን ለማየት አብዝታችሁ ስትሠሩ ብቻ እንደሆነ አትዘንጉ፤ ይህም ለዘለቄታው የተሳካ እንዲሆን የኢትዮጵያ ፍጹምና ዘላቂ ጥበብ ለሆነ ፈሪሀ እግዚአብሔር ፣ለትዕግሥትና ለወንድማዊ ፍቅር ዝግጁ በመሆን፣ በጸሎትም በመትጋት አንድነታችሁን እውን ታደርጉ ዘንድ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡
መልካም በዐለ ደብረ ዘይት ያድርግልን! እግዚአብሔር ሀገራችን ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡