ነሐሴ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. በዓለ ደብረ ታቦርን በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

 

የመጀመሪያው የቴሌቪዥን ትምህርት ነበር

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

‹‹መነ ይብልዎ ሰብእ ለወልደ ዕጓለ እመሕያው
ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?››
(ማቴ. 16፥13)

በሀገራችን በኢትዮጵያና በተለያዩ ክፍላተ ዓለም ሆናችሁ ይህን የቅዱስ ወንጌል ቃል በመስማት ላይ የምትገኙ ውሉደ እግዚአብሔር ሁሉ፣ እግዚአብሔር አምላካችን በረከቱን፣ ጸጋውንና መልካም ስጦታውን ሁሉ እንዲያበዛላችሁ እየጸለይን፣ እንኳን ለበዓለ ደብረ ታቦር በሰላም አደረሳችሁ እንላለን ፡፡

የደብረ ታቦር በዓል ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መለኮታዊ ባሕርዩንና ምሥጢረ መንግሥቱን የገለጸበት ቀን በመሆኑ፣ በክርስትናው ዓለም ዐቢይ ስፍራ የሚሰጠው ታላቅ በዓል ነው ፡፡

የታቦር ተራራ ቀደም ሲል ከክርስቶስ ልደት በፊት ዲቦራ የተባለች ነቢይት በዚህ ተራራ ላይ ቆማ ወደ እግዚአብሔር በመጸለይና የጦር አመራርን በመስጠት፣ ሕዝበ እስራኤልን ለመውጋትና ለመውረር በእብሪት ተነሣሥቶ የመጣውን ሲሣራን፣ በባርቅ አዝማችነት ድል ያደረገችበት የድል ተራራ እንደሆነ በቅዱስ መጽሐፍ ተጽፎአል (መሳ. 4፥4-24)፡፡ ይህ ድል በዘመነ ሥጋዌ የሚነሡትን የኑፋቄ ትምህርቶች ሁሉ በደብረ ታቦር በሚገለጸው መለኮታዊ ትምህርት ድል የሚደረጉ መሆናቸውን የሚያመለክት ነበር፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊትም “ታቦርና አርሞንኤም በስምህ ደስ ይላቸዋል፤ ስምህንም ያመሰግናሉ፤ ክንድህ ከኀይል ጋር በዚያ ይገለጻል” በማለት እግዚአብሔር ወልድ በዚህ ተራራ ላይ ኀይለ መለኮቱን ሲገልጽ፣ ተራራው በብርሃነ መለኮቱ ደምቆ የደስታ ተራራ እንደሚሆን ከክርስቶስ ልደት በፊት በአንድ ሺሕ ዓመት ገደማ በትንቢት ተናግሮለታል (መዝ. 88፥12)፡፡

የክርስትና ሃይማኖት ከጥንተ ፍጥረት ጀምሮ በልዩ ልዩ ኅብረ ትንቢት፣ በልዩ ልዩ ኅብረ አምሳል፣ በልዩ ልዩ ኅብረ ቃል እንደ ሰንሰለት ተያይዞ የመጣውን ተስፋ-ድኅነት መሠረት አድርጎ የቀጠለ ሃይማኖት እንጂ፣ በሆነ ፈላስፋ ወይም የፈጠራ ክሥተት የመጣ አይደለምና፣ እንደ ሌላው ትምህርተ ክርስትና ሁሉ፣ የታቦር ተራራ መለኮታዊ ክሥተትም በድንገት የተገለጸ ሳይሆን፣ ከክርስቶስ ልደት በፊት ለአንድ ሺሕ ዓመታት ያህል እየተነገረ የመጣና በተስፋ ሲጠበቅ የነበረ ድንቅ የእግዚአብሔር መለኮታዊ ክሥተት እንደሆነ ከቅዱስ መጽሐፍ ትምህርት እንገነዘባለን፡፡ የትንቢትና የምሳሌ ሁሉ መዳረሻ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነውና፣ መድኀኒታችን በሥጋ በዚህ ዓለም ተገልጾ ወንጌለ መንግሥተ ሰማያትን ሲያስተምር፣ በተነገረው ትንቢት መሠረት መለኮታዊ ባሕርዩንና ድል አድራጊው ምሥጢረ መንግሥቱን በደብረ ታቦር ላይ ገለጸ፤ የነገሩንም አፈጻጸም ቅዱስ መጽሐፍ እንደ ሚከተለው ያስተምረናል፡- ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሕዝቡ መካከል ተገኝቶ ከሚያስተምረው ጥልቅ ትምህርትና ከሚሠራው ድንቅ ተኣምር የተነሣ ሕዝቡ ስለማንነቱ ብዙ ያወራና ይናገር ነበር ፡፡

ጌታችንም በሕዝቡ ዘንድ ያለውን የተለያየ አባባል ተቀባይነት አግኝቶ ወደ ተሳሳተ አቅጣጫ እንዳይሄድ ለማረም በፈለገ ጊዜ ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?›› በማለት ደቀ መዛሙርቱን ጠየቀ፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ሕዝቡ የሚለውን በመጥቀስ አንዳንዶቹ ኤልያስ ነው ይሉሃል፤ አንዳንዶቹም ኤርምያስ ነው ይሉሃል፣ አንዳንዶቹ ደግሞ መጥምቁ ዮሐንስ ነው ይሉሃል፣ ሌሎቹ ደግሞ ከቀደምት ነቢያት አንዱ ሳይሆን አይቀርም ይሉሃል ብለው መለሱ፡፡ ጌታችንም እናንተሳ ማን ትሉኛላችሁ? አላቸው፤ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ መለሰ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ትክክለኛውንና እውነተኛውን መልስ ስለመለሰ ጌታችን ‹‹የዮና ልጅ ስምዖን ጴጥሮስ ሆይ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋዊና ደማዊ አእምሮ ይህንን አልገለጸልህምና ብፁዕ ነህ›› ብሎ መልሱን ከምስጋና ጋር ተቀብሎአል፤ (ማቴ. 16፡13-19)፡፡

ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ጌታችን ነቢይ ወይም ከነቢያት አንዱ ሳይሆን ‹‹የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ›› መሆኑን ለደቀ መዛሙርቱ አረጋገጠላቸው፡፡ ከዚህ ቀደምም ጌታችን የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ቅዱስ ገብርኤል ቅድስት ድንግል ማርያምን ባበሠረ ጊዜ ‹‹ካንቺ የሚወለደው ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል፤ ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ›› ሲል ስሙንና ማንነቱን በግልጽ አሳውቆ ነበር (ሉቃ. 1፡30-35)፡፡ እግዚአብሔር አብም ጌታችን በዮርዳኖስ በተጠመቀ ጊዜ ‹‹የምወደው ልጄ ይህ ነው›› በማለት ገልጾ ነበር (ማቴ. 3፡17)፡፡

በጣም የሚገርመው ደግሞ አጋንንት ሳይቀሩ ‹‹አንተ ማን እንደሆንህ ዐውቀናል፤ አንተ የእግዚአብሔር ቅዱስ ነህ፤ አንተ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ›› እያሉና እየሰገዱ በተደጋጋሚ መመስከራቸው ነው (ሉቃ. 4፥31-41)፡፡ ይሁን እንጂ ጌታችን የእግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ እንደሆነ በፈጣሪም ሆነ በፍጡራን ዘንድ ብዙ ጊዜ ቢነገርም ሰዎች ይህን መገንዘብና ማወቅ አቅቶአቸው ወዲያና ወዲህ ሲባዝኑ በመገኘታቸው፣ ጌታችን በስማቸው እየተጠቀሰ ያሉትን ነቢያት በተገኙበት፣ በታቦር ተራራ ላይ ማንነቱንና የመንግሥቱን ምንነት ለመግለጽ ብሎ፣ ቅዱስ ጴጥሮስ በቂሳርያ ምስክርነቱን በሰጠ በስድስተኛው ቀን፣ ሦስቱ ደቀ መዛሙርቱን ይዞ ወደ ታቦር ተራራ ወጣ፡፡ በዚያም ፊቱ ተለውጦ እንደ ፀሓይ ብርሃን ሆነ፤ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ሆነ፤ ሙሴና ኤልያስም ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩ፤ ብሩህ ደመናም መጥቶ ጋረዳቸው፤ ከደመናውም ‹‹የምወደው ልጄ ይህ ነውና እርሱን ስሙት›› የሚል ድምፅ መጣ፤ ሦስቱ ደቀ መዛሙርት ማለትም ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ዮሐንስና ቅዱስ ያዕቆብም ከግርማ መለኮቱ የተነሣ ፈርተው በምድር ላይ ወደቁ፤ በመጨረሻም ጌታችን ዳሰሳቸውና እንዲነሡ አደረጋቸው (ማቴ. 17፥1-8)፡፡

እንግዲህ ይህ ሁሉ የሆነው ዓለም በጌታችን ማንነትና በሚያወርሳት መንግሥቱ ምንነት መንታ መንገድ ላይ ቆማ በጥርጥርና በክሕደት እንዳትጎዳ እውነተኛው ትምህርትና እምነት የትኛው እንደሆነ ለይታ እንድታውቅ ለማድረግ ነው፡፡ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታችንን ካበሠረበት ቀን ጀምሮ እስከ በዓለ ደብረ ታቦር ድረስ ስለጌታችን ማንነት የተነገሩ ሁሉ ፣ጌታችን ‹‹የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ መሆኑን የሚያስረግጡ ናቸው፤ ይህም ማለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእግዚአብሔር የተወለደ እግዚአብሔር መሆኑን አረጋግጠዋል ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር አንድያ ልጅ መባሉ ሰዎች ከእግዚአብሔር በባሕርይ ሳይወለዱ፣ በጸጋ ወይም በስጦታ የእግዚአብሔር ልጅ የመሆን መብት ተሰጥቶአቸው ውሉደ እግዚአብሔር እንደሚባሉት ዐይነት ሳይሆን፣ የእግዚአብሔር ብቸኛ የባሕርይ ልጅ ነው ለማለት ነው ፡፡

በሌላ አባባል በባሕርያዊ ልደት ክዋኔ ከሰው የተወለደ ሰው፣ ከእንስሳም የተወለደ እንስሳ እንጂ ሌላ ሊሆን እንደማይችል ሁሉ፣ ከእግዚአብሔር በባሕርይ የተወለደም እግዚአብሔር ከመሆን በቀር ሌላ ሊሆን አይችልምና ጌታችን የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ በመሆኑ እግዚአብሔር ነው ማለት ነው፡፡ ፍጡራን በሙሉ በባሕርይም፣ በመልክም ራሳቸውን የሚመስል ልጅ እንደሚያስገኙና ባሕርያዊ ውርስንም በዘር እንደሚያስተላልፉ ሁሉ፣ ጌታችንም የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ ስለሆነ በባሕርዩም፣ በመልኩም እንደአባቱ ነው፤ እንደዚሁም ለአባቱ ያለው ሁሉ ገንዘቡ በመሆኑ እንደ አባቱ እግዚአብሔር ነው፤ በዚህ የባሕርይ ልጅነት ዐይነት ከእግዚአብሔር የተወለደ ሌላ ልጅ የለምና ቅዱስ መጽሐፍ ጌታችንን ‹‹አንድያ የእግዚአብሔር ልጅ ወይም ወልድ ዋሕድ›› ይለዋል ፡፡ ይህ አገላለጽ የጌታችን ወልደ እግዚአብሔርነት በጸጋ ወይም በችሮታ ከእግዚአብሔር ከተወለድነው ከክርስቲያኖች ልጅነት ጋር በእጅጉ የተለየ መሆኑን ያስረዳል፣ (ዮሐ. 1፡ 12-18፣ ዮሐ. 3፡16)፡፡

ጌታችንም ይህንን ሲያመለክት ነው ‹‹እኔና አብ አንድ ነን፤ እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ እንዳለ እመኑኝ፤ ለአብ ያለው ሁሉ የእኔ ነው፤ የእኔም የሆነ ሁሉ የአንተ ነው፤ የአንተም የእኔ ነው›› ያለው (ዮሐ. 10፡30፣ 14፡11፤ 16፡15፤ 17፡10)፡፡ ወንጌላዊው ዮሐንስም ‹‹በመጀመሪያው ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ፤ … ያ ቃል ሥጋ ሆነ›› በማለት የጌታችንን እግዚአብሔርነት በማያሻማ መልኩ በግልጽ ጽፎልናል፤ (ዮሐ. 1፡1-14)፡፡ ከዚህ ላይ ማስተዋል ያለብን ዐቢይ ነገር ጌታችን የእግዚአብሔር አብ ልጅ ቢሆንም፣ በአባቱና በእርሱ መካከል መቀዳደምና መበላለጥ የሌለ መሆኑን ነው፤ ምክንያቱም ባሕርየ እግዚአብሔር አንድ ከመሆኑም ሌላ በሦስቱ አካላት መካከል የባሕርይና የህልውና ልዩነት የለምና ነው፡፡ ቃል የሚለው የጌታችን ስምም ይህንን በሚገባ ይገልጸዋል፤ ምክንያቱም፡- የቃል ህላዌ ከልብና ከእስትንፋስ እንደማይቀድም ወይም እንደማይዘገይ ሁሉ ወልደ እግዚአብሔር ክርስቶስም በህላዌው ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ የማይቀድም ወይም የማይዘገይ መሆኑን በግልጽ ያስረዳልና ነው፡፡ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት ከጥንት ዘመን ጀምሮ ማለትም ከዘመነ ብሉይ አንሥቶ በግልጽና በማያሻማ መልኩ የተገለጸ ቢሆንም፣ ጥንትም ሆነ ዛሬ ሰዎች በዚህ ጉዳይ ላይ የተለያዩ አባባሎችን በመፍጠር መለያየታቸው አልቀረም፡፡ ሆኖም ከሰዎች ደካማ ዕውቀትና አናሳ ግንዛቤ የተነሣ ችግሩ መከሠቱ ባይቀርም፣ ቅዱሳት መጻሕፍት ግን ጌታችን ‹‹የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ›› እንደሆነ በማያሻማ መልኩ ነግረውናል፤ እግዚአብሔር አብም በፈለገ ዮርዳኖስና በደብረ ታቦር ይህንን አረጋግጦልናል፤ ቅዱስ ገብርኤልም በናዝሬት ከተማ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ባበሠረ ጊዜ፣ ቅዱስ ጴጥሮስም በቂሳርያ እግዚአብሔር ገልጾለት በመሰከረ ጊዜ፣ አጋንንትም በቅፍርናሆም ጌታችንን ባዩ ጊዜ፣ እርሱ ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን መስክረዋል፡፡

የእግዚአብሔር ልጅ ማለትም እግዚአብሔር ማለት እንደሆነ ተቃዋሚዎቹ አይሁድ ሳይቀሩ ያወቁትና የተረዱት ሐቅ ነበረ፡፡ አይሁድ ይህን ግንዛቤ ሊይዙ የቻሉት፣ የሰው ልጅ ሰው ከመሆን በቀር ሌላ እንስሳ ሊሆን እንደማይችል ሁሉ፣ የእግዚአብሔር ልጅም እግዚአብሔር ከመሆን በቀር ሌላ ሊሆን እንደማይችል በመገንዘባቸው ነው፤ አይሁድ ቁም ነገሩን አምነው ባይቀበሉትም አባባሉን ግን ምን ማለት እንደሆነ በትክክል ተገንዝበውታል፡፡ ነገሩም እንዲህ ተገልጾአል፡- ‹‹ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር አስተካክሎ እግዚአብሔር አባቴ ነው ስላለ አይሁድ ሊገድሉት ፈለጉ›› ይላል ቅዱስ መጽሐፍ፤ ይህ የአይሁድ ቍጣ፣ እግዚአብሔር አባቴ ነው ማለቱ፣ እግዚአብሔር ነኝ ማለቱ ነው፤ ከሚል የተነሣ እንደሆነ ጥቅሱ ያመለክታል (ዮሐ. 5፡18)፡፡

ይሁንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎች የነቢያትን ስም እየጠቀሱ ስለማንነቱ ይናገሩት የነበረውን አባባል ፍጹም ስሕተት መሆኑን ለማሳየት፣ በቅዱስ ጴጥሮስ የተነገረውን ምስክርነት፣ እንደገና በዓበይተ ነቢያት በሙሴና በኤልያስ፣ ከሁሉ በላይ ደግሞ በባሕርይ አባቱ በእግዚአብሔር አብ፣ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ መሆኑን በታቦር ተራራ ላይ አረጋገጠ፤ ይህም ከሆነ ዓለም ስለጌታችን ማንነት መቀበል ያለባት እውነት ይህና ይህ ብቻ ነው፤ ከዚህ ውጭ የሆነ ሁሉ ስሕተትም፣ ቅዠትም፣ ውሸትም ከመሆን በቀር ምንም ዐይነት እውነትነት የለውም ፡፡

እኛም ከዚህ ተነሥተን ስለጌታችን ማንነት አምነን ስንመሰክር፡- ‹‹በአንድ የእግዚአብሔር ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን፤ ከብርሃን የተገኘ ብርሃን፣ ከእውነተኛ አምላክ የተገኘ አምላክ፣ የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ፣ በባሕርዩ ከአብ ጋር አንድ የሆነ፤ ሁሉ በእርሱ የሆነ፣ ያለእርሱ ግን ምንም ምን የሆነ የሌለ›› እያልን እናምናለን፤ እንመሰክራለንም ፡፡ ከዚህም ጋር ‹‹ጌታችን ሰውም፣ አምላክም ነውና በወልደ እግዚአብሔርነቱ እግዚአብሔር እንደሆነ ሁሉ፣ በክርስቶስነቱ ደግሞ የእግዚአብሔር ልጅም የሰው ልጅም መሆኑን አንዘነጋም፤ ስለሆነም ወልደ እግዚአብሔርና ወልደ ማርያም የሆነው ክርስቶስ ከሁለት አካላት አንድ አካል፣ ከሁለት ባሕርያት አንድ ባሕርይ ሆኖ በተዋሐደ ህላዌ በታቦር ተራራ ላይ ቆሞ ሳለ፣ አብ ‹‹ይህ የምወደው ልጄ ነው፤ እርሱ የሚላችሁን ስሙ›› በማለቱ፣ ጌታችን በተዋሕዶ ‹‹የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ›› መሆኑን ዐውቀናል፤ አምነናልም፤ ከዚህ አኳያ ስለክርስቶስ ማንነት የሚጠይቀን ካለ መልሳችንም፤ እምነታችንም ምሥጢረ ተዋሕዶ የተገለጸበት ይኸው የደብረ ታቦር ትምህርት ብቻ ነው ፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በታቦር ተራራ ላይ የገለጸው የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅነቱን ብቻ ሳይሆን ምሥጢረ መንግሥቱንም ጭምር ነው፡፡ ነቢያትም፣ ጌታችንም፣ ሐዋርያትም፣ ብዙ የተናገሩላት፣ የእግዚአብሔር ልጆች የሆንን ምእመናንም በተስፋ የምንጠባበቃት የእግዚአብሔር መንግሥት፣ በመጨረሻ ጊዜ ተገልጻ ሁሉንም በቍጥጥሯ ሥር እንደምታደርግ ይታወቃል፤ (ራእ. 21፥1-4)፡፡ ስለሆነም የዚህ መንግሥት ገዥ ማን ነው? በዚህ መንግሥት ውስጥ የሚኖሩስ እነማን ናቸው? ይህ መንግሥት ሲገለጥ የሚሆነው ክሥተትስ ምንድን ነው? የሚለውን ጥያቄ የደብረ ታቦር ክሥተት በሚገባ ገልጾታል፡፡ የታቦር ተራራ ውብና አስደሳች ከመሆኑም ሌላ በጣም ከፍ ያለ ተራራ ነው፤ ቅዱስ ያሬድ የዚህን ተራራ ውበት ሲገልጽ ‹‹ሰላም ለከ ኦ ደብረ ታቦር ዘከለሎ ብርሃን ይሤኒ ላሕዩ እምኵሉ አድባር፤ ከተራሮች ሁሉ ይልቅ ውበትህ ያማረ፣ ብርሃነ መለኮት የጋረደህ ደብረ ታቦር ሆይ ሰላምታ ላንተ ይገባል›› ብሎአል፡፡

በመሆኑም ይህ ውብ፣ ብርሃናዊና ከፍ ያለ ተራራ የመንግሥተ ሰማያት አምሳያ ነው፤ ወልደ እግዚአብሔር ክርስቶስ በግርማ መለኮት፣ በክበበ ትስብእት በዚህ ተራራ እንደተገለጸ ሁሉ፣ በመጨረሻ ጊዜ በምትገለጸዋ የእግዚአብሔር መንግሥትም ጌታችን በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት ተገልጾ ብርሃንዋና መሪዋ፣ ገዢዋም ሆኖ በመካከልዋ እንደሚኖር ምሥጢሩ ያሳያል፡፡ በታቦር ተራራ ላይ ከነቢያት፣ ሙሴና ኤልያስ፣ ከሐዋርያት፣ ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ዮሐንስና ቅዱስ ያዕቆብ፣ ከሕያዋን ኤልያስ፣ ከሙታን ሙሴ፣ ከደናግል ኤልያስ፣ ከሕጋውያን ሙሴ ተገኝተዋል።

ይህም ከክርስቶስ በፊትና በኋላ የተነሡ ቅዱሳን፣ ሙታንና ሕያዋን፣ ደናግልና ሕጋውያን በአንድነትና በእኩልነት በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ በፍጹም ደስታ እንደሚኖሩ ምሥጢሩ ያመለክታል (1ቆሮ. 15፥52፣ 1ተሰ. 4፥15፡17)፡፡ በመሆኑም ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ምንነት የሚጠይቀን ካለ የእግዚአብሔር መንግሥት ከሁሉም በላይ ከፍ ያለችና ውብ የሆነች፣ ዕጹብ ድንቅ በሆነ መለኮታዊ ብርሃን አሸብርቃ የምትኖር፤ ክርስቶስ በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት በቅዱሳኑ ላይ ነግሦባት የሚኖር፣ በዘመነ ብሉይም ሆነ በዘመነ ሐዲስ የተነሡ ቅዱሳን ሁሉ የሚገኙባት፣ ሙታንም ሆኑ ሕያዋን፣ ሕጋውያንም ሆኑ ደናግል፣ በአንድነትና በእኩልነት ከብረውና ደስ ተሰኝተው የሚኖሩባት፣ ዘለዓለማዊት መንግሥት እንደሆነች ከደብረ ታቦር በተማርነው ትምህርት መሠረት እንመልስለታለን፤ በዚህም አምነን እንኖራለን፡፡

የእግዚአብሔር መንግሥት ለወደፊቱ በግልጽ የምትመጣበት ጊዜ እንዳለ ብናውቅም፣ ዛሬም ቢሆን በዓለሙ ሁሉ በገዥነት አለች፤ ይልቁኑም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ዛሬም የእግዚአብሔርን ሕዝብ በመምራት ትገኛለች፤ የእግዚአብሔር ሕዝብ በዋናነት የሚተዳደረውና የሚመራው በእግዚአብሔር ሕገ መንግሥት ነው፤ የኢትዮጵያ ሕዝብም የእግዚአብሔር ሕዝብ ስለመሆኑ ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም፤ ከሆነ ጊዜ ጀምሮ ኢትዮጵያና እግዚአብሔር የተለያዩበት ጊዜ ፈጽሞ የለም፤ ዛሬ ለዓለም ሕዝብ ምሥጢር ሆኖ የሚገኘው የሕዝባችን አንድነትና ነፃነት የእግዚአብሔር ሕዝብ ከመሆናችን የተገኘ እንጂ ሌላ እንዳይደለ አንዘንጋ፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነት ከደብረ ታቦር አስተምህሮ የተወረሰ ነው፤ ደብረ ታቦር የብሉዩንና የሐዲሱን፤ ሕጋዊውንና ድንግሉን፣ ፈጣሪንና ፍጡራንን፣ ሕያዉንና ምዉቱን በአንድነት በእግዚአብሔር መንግሥት ክልል ውስጥ ያገናኘ የእግዚአብሔር መንግሥት አምሳያ ነው፤ ኢትዮጵያ ሀገራችን ይህንን ትምህርት ተቀብላና እንደ ደብረ ታቦር የእግዚአብሔር መንግሥት ተምሳሌት ሆና፣ የተለያየ ቋንቋና ባህል ያላቸውን ልጆቿን ሁሉ በፍቅር፣ በአንድነት፣ በክብር፣ በስምምነትና በወንድማማችነት አስማምታና አቅፋ ለዝንተ ዓለም የነበረች ቅድስት ሀገር ናት፤ ይህ ለማንም ሆነ ለማን ያልተሰጠ ልዩ ጸጋና በረከት ለኢትዮጵያውያን በምልአት የተሰጠ በመሆኑ ልናከብረውና ልንጠብቀው ይገባል፤ በዚህም እጅግ ደስ ሊለንና ለዚህ የመረጠንን እግዚአብሔርን ዘወትር ልናመሰግን ይገባል፡፡

ዛሬም እንደ ትናንቱ በወንድማማችነት፣ በፍቅር፣ በስምምነት፣ በእኩልነት በመዋደድ፣ በመከባበር፣ በመተማመን የተመሠረተ አንድነትን፣ ነፃነትንና ሃይማኖትን ጠብቆ መኖር ለኢትዮጵያውን ከማንኛውም በላይ የሆነ ክብርና ጸጋ ነው፤ የቀደሙት ኢትዮጵያውን አበው ለዝንተ ዓለም የገነቡት ይህ ጠንካራና ጽኑ ግንብ በተራ ምክንያት እንዳይፈርስ በሚገባ መጠበቅ አለብን ፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነት፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነትና የኢትዮጵያ ሕዝብ ሃይማኖት ለድርድር የሚቀርቡ አይደሉም፤ ባሉበት ብቻ ተጠብቀው መኖር አለባቸው፤ ሕዝቡም ይህንን መጠበቅ አለበት፤ የደብረ ታቦር አስተምህሮ ይኸው ነውና ፡፡ ‹‹ጸጋ ዘአብ ሂሩት ዘወልድ ሱታፌ ዘመንፈስ ቅዱስ የሀሉ ምስሌየ ወምስለ ኵልክሙ›› ‹የአብ ጸጋ፣ የወልድ ቸርነት፣ የመንፈስ ቅዱስ አንድነት፤ ይህን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቴሌቪዥን ትምህርተ ወንጌል ከምትከታተሉ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ ካላችሁ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ሁለ ጋር ለዘለዓለም ጸንቶ ይኑር፡፡

እግዚአብሔር ይባርካችሁ ይቀድሳችሁ፤ ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን!

ነሐሴ 1 ቀን 2008 ዓ/ም የጾመ ፍልሰታ መግቢያ ቃለ ቡራኬና ምዕዳን

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገር ውስጥም ሆነ በተለያዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ወምእመናት፣

እንኳን ለሁለት ሺሕ ስምንት ዓመተ ምሕረት የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ።

‹‹ቃለ እግዚአብሔር ንጹሕ ወየሐዩ ለዓለም
የእግዚአብሔር ቃል ንጹሕ ነው፤ ለዘለዓለሙም ያድናል።››
(መዝ.18፡9)፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት ስለ ቃለ እግዚአብሔር አስመልክቶ በዘመረው መዝሙር ሲናገር ‹‹የእግዚአብሔር ቃል ንጹሕ ነው›› ይላል፤ በእርግጥም የእግዚአብሔር ቃል የተለያዩ ፍጡራን ከሚናገሩዋቸው ቃላት ልዩ፣ ንጹሕ፣ ቅዱስና ክቡር ነው፡፡ የፍጡራን ቃል ከሐሰት፣ ከወላዋይነት፣ ካላዋቂነት፣ ከጥርጣሬ፣ ከአስመሳይነት፣ ከአታላይነትና ከዐቅም ውሱንነት ጋር ተቀላቅሎ ስለሚነገር ንጹሕ ነው ብሎ መናገር አይቻልም፤ የእግዚአብሔር ቃል ግን ከዚህ ሁሉ የተለየ በመሆኑ ፍጹም ንጹሕ ነው፤ እውነትም ነው፤ የእግዚአብሔር ቃል ንጹሕ ብቻ ሳይሆን ኀያልም ነውና በተናገረው መሠረት ከሚፈጸም በቀር ፍጹም የማይቀለበስ ነው፡፡

‹‹የእግዚአብሔር ቃል ከሚወድቅ፣ ሰማይና ምድር ቢያልፍ ይቀላል›› የሚለው የጌታችን የአምላካችንና የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ኀይለ ትምህርት፣ የእግዚአብሔር ቃል ከሁሉም በላይ የሆነ ክብር፣ ኀይልና ጽናት ያለው መሆኑን ያስገነዝበናል፡፡ በመሆኑም ንጹሕና እውነት የሆነውን የእግዚአብሔር ቃል በማጣመም፣ ወይም በመሸራረፍ፣ ወይም በመቀናነስ ወይም ለራስ ፍላጎት በሚያመች ሁኔታ እያዛቡ መናገርና ማስተማር በእግዚአብሔር መንግሥት ከሁሉ ይልቅ ታናሽ የሚያደርግ መሆኑን በቅዱስ ወንጌል ተጽፎአል፤ (ማቴ. 5፡19)፤ የእግዚአብሔር ቃል እውነተኛና ንጹሕ የመሆኑን ያህል ሕያውና ዘለዓለማዊ ነው፤ በሁለት ወገን ስለት ካለው ሰይፍም ይልቅ የሚቈርጥና የሚለይ ኀይል አለው (ዕብ.4፡12)፡፡ ይህም ማለት የእግዚአብሔርን ቃል እንዳለ ተቀብለው የሚጠብቁትንና የሚታዘዙለትን ለዘለዓለሙ ሕያዋን የማድረጉን ያህል፣ የሚሸራርፉትንና የሚያጣምሙትን ደግሞ የመቅጣት ሥልጣን ያለው መሆኑን ያሳየናል፡፡ በመሆኑም የሰው ልጅ ድኅነት፣ ቃሉን በመጠበቅና ባለመጠበቅ ሚዛን ላይ ተቀምጦ እንዳለ መገንዘብ አለብን፡፡

ንጹሕና ሕያው የሆነው፣ ሰዎችንም ለዘለዓለሙ በሕይወት እንዲኖሩ የሚያደርገው የእግዚአብሔር ቃል፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በተመለከተ የተናገረው እውነት አለ፤ በቀጣዮቹ ሁለት ሱባዔያት የቅድስት ድንግል ማርያምን ነገረ ፍልሰት ምክንያት በማድረግ የምንፈጽመው አምልኮተ እግዚአብሔር፣ የእግዚአብሔር ቃል ስለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተናገረውን በማስታወስና ለቃሉ ተገዥ በመሆን ነው፤ የእግዚአብሔር ቃል ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ብዙ ተናግሮአል፤ ከተናገራቸውም መካከል፡ (1) ጸጋን የተሞላሽ ሆይ ደስ ይበልሽ፤ (2) እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ነው፤ (3) ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ፤ (4) በእግዚአብሔር ፊት ጸጋን አግኝተሻል፤ (5) መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፣ የልዑልም ኀይል ይጸልልሻል፤ (6) የጌታዬ እናት ወደኔ ትመጣ ዘንድ እኔ ማን ነኝ? (7) ብፅዕት ነሽ፤ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል፤ (8) እነሆ ልጅሽ እነኋት እናትህ፤ የሚሉ ይገኙባቸዋል፡፡ ስለሆነም እግዚአብሔር ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም የተናገረውን ቃል ጠቅለል አድርገን ስንመለከት በዋናነት የሚያሳየው ቅድስት ድንግል ማርያምን የጌታ እናት መሆኗን አምነው በመቀበል ‹‹ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ነሽ›› እያሉ እንዲያከብሯት በእግዚአብሔር መታዘዙ ነው፤ ምክንያቱም የድንግል ማርያም ክብር፣ ከእግዚአብሔር ክብር ጋር የተያያዘ ባሕርይ አለውና ነው፤ ቅድስት ድንግል ማርያም ምልእተ ጸጋ፣ ሙኃዘ ፍሥሐ፣ ምልእተ በረከት፣ የእግዚአብሔር ባለሟል፣ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ፣ ከእግዚአብሔር ጋር ያለች፣ ብፅዕት ባትሆን ኖሮ ጌታን ለመውለድ የሚያስችል ንጽሕናና ቅድስና አይኖራትም ነበር፤ እግዚአብሔር ንጹሐ ባሕርይ እንደ መሆኑ መጠን በንጹሐንና በቅዱሳን አድሮ ይኖራልና፡፡

ቅድስት ድንግል ማርያም ጸጋን፣ በረከትን፣ ባለሟልነትን፣ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ መሆንን፣ በድንግልና መፅነስን በእግዚአብሔር ኀይል መከለልን ገንዘብ አድርጋ መገኘቷ፣ ከእርስዋ የተወለደው ማን እንደሆነ በትክክል እንድናውቅ ያስችለናል፡፡ ቅዱስት ድንግል ማርያምን ወላዲተ አምላክ ሳንል፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አምላክ ወሰብእ ብለን ማመንና መዳን አንችልም፤ ቅድስት ድንግል ማርያምን ምልእተ ጸጋ፣ ምልእተ በረከት፣ ሙኃዘ ፍሥሐ፣ ብፅዕት፣ ንጽሕት፣ ቅድስት ስንል ነው ከእርስዋ የተወለደውን ጌታ የባሕርይ አምላክ ነው ማለት የምንችለው፣ ምክንያቱም የቅድስት ድንግል ማርያም ልዩ ጸጋና ቅድስና ለጌታችንና ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት አስረጅ በመሆኑ ‹‹ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ነሽ›› እያልን እመቤታችንን እንድናከብር የእግዚአብሔር ቃል አዞናልና፤ (ሉቃ. 1፥45-48)፡፡

ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእርሱና በቅድስት ድንግል ማርያም መካከል ያለው ግንኙነት የእናትነትና የልጅነት እንደሆነ ሁሉ፣ በምእመናንና በድንግል ማርያም መካከል ያለው ግንኙነትም በእናትነትና በልጅነት ደረጃ እንዲሆን አዞአል፤ (ዮሐ19፡26-27)፡፡ በሁሉም ዘንድ እንደ ሚታወቀው አንድን ልጅ አቅፋ፣ አዝላ፣ አጥብታ፣ መግባ፣ ንጽሕናውን ጠብቃ፣ በእንክብካቤ የምታሳድግ እናት ታስፈልገዋለች፤ እናትም የሚያከብራትና የሚያስከብራት ልጅ ያስፈልጋታል፤ እንደዚሁም ሁሉ ጌታችን እመቤታችንን የምእመናን እናት እንድትሆን ሲያደርግ፣ በሥጋዊም ሆነ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ተጐሳቁለን እንዳንጎዳ በጸሎቷ፣ በልመናዋ፣ በአማላጅነቷ እያገዘችና እየደገፈች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ልታደርሰን ብሎ እንደሆነ ልብ ብሎ ማስተዋሉ ተገቢ ነው፡፡ ምእመናንም የእመቤታችን ልጆች እንድንሆን ማድረጉ፣ በዚህ ዓለም ስንኖር እርስዋን አክብረንና አስከብረን በስሟ እየተማፀን የበረከቷና የጸጋዋ ተካፋይ እንድንሆን ብሎ እንደሆነ በውል መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹እነኋት እናትህ›› ከተባለበት ሰዓት ጀምሮ እመቤታችንን ወስዶ በቤቱ አኑሮአታል፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እመቤታችን በእያንዳንዱ አማኝ ልጇ ቤት በመንፈስ እየገባች ትኖራለች፡፡ በዚህ የጌታችን ቃል፣ የሐዋርያት ትምህርትና ትውፊት መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ቤት፣ የእመቤታችን ቤት ሆኖ ይገኛል፤ ምክንያቱም በቤቱ የድንግል ማርያምን ሥዕል አስገብቶ እምዬ እናቴ፣ ብፅዕት ነሽ እያለ የማይጸልይና የማይማፀን የለምና፣ በዚህም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመን የሆነ ሁሉ፣ የእግዚአብሔርን ቃል ሳይሸራርፍ፣ ሳይቀናንስና ሳያጣምም እንዳለ ተቀብሎ እየፈጸመ ይገኛል፤ ቃሉን በምልአት በመጠበቁና በመፈጸሙም እንደ ቃሉ ተስፋ ለዘለዓለም ሕያው ሆኖ ይኖራል፡፡

እግዚአብሔር በቅድስት ድንግል ማርያም በኩል የሰጠን ትልቁ ስጦታ ፍጹም ፍቅር ነው፤ ይኸውም በእናትና በልጅ መካከል ያለውን ፍቅር ነው፤ ያ ፍቅር ነው እስካሁን እመቤታችንንና እኛን አስተሳስሮ የሚገኘው፤ ከዚህ ፍቅር ሊለዩን የሚሞክሩትን ሁሉ በእግዚአብሔር ቃል፣ በኦርቶዶክሳዊና በኢትዮጵያዊ መንፈስ ልንቋቋማቸው ይገባል፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምን ብፁዕት ነሽ እያለ የሚያመሰግን ሁሉ፣ እንደ ኤልሳቤጥ በመንፈስ ቅዱስ የተሞላና የእግዚአብሔርን ቃል በምልአት የያዘ መሆኑን እርግጠኛ ይሁን ፡፡ በእኛና በቅድስት ድንግል ማርያም ያለው ፍቅር ዐቢይና ጥልቅ እንደመሆኑ መጠን፣ ስመ ማርያምን ጠርቶ ቁራሽ እንጀራ የሚለምን ሁሉ፣ ስለእርስዋ ፍቅር ብለን ለድሆች ስንዘክር፣ የነበረውን ሃይማኖታዊ ተግባራችን ዛሬም ሳይቀዘቅዝ ሊቀጥል ይገባል፡፡

በዚህ በጾመ ማርያም ወቅት የተራቡትን በማጒረስ የታረዙትን በማልበስ፣ የታመሙትን በመጠየቅ፣ የታሠሩትን እግዚአብሔር ያስፈታችሁ በማለት፣ በማኅበረ ሰቡ መካከል መቻቻልን፣ መተማመንን፣ ወንድማማችነትን፣ ስምምነትን፣ ፍቅርንና ሰላምን በማስፈን ሱባዔውን ልንፈጽም ይገባል፤ ከዚህም ጋር በአሁኑ ጊዜ በስፋት እያጋጠመ ያለውን የትራፊክ አደጋ መቀነስ ይቻል ዘንድ፣ ምእመናን ሁሉ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲመላለሱም ሆነ በሌላ ቦታ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ ጥንቃቄ ባልተለየው ሁኔታ እንዲሆን፣ ሹፌሮችም ሲያሽከረክሩ ኀላፊነት፣ ጥንቃቄና ማስተዋል ባልተለየው ሁኔታ እንዲሠሩ መንፈሳዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፤ በየቤተ ክርስቲያኑ የሚገኙ መምህራንና ሰባክያንም የጉዳዩን አሳሳቢነት በማስገንዘብ ሕዝቡ ከትራፊክ አደጋ ጥንቃቄ ያደርግ ዘንድ በዚሁ ሱባኤ ሰፊ ትምህርትና ምክር እንዲሰጡ አደራ ጭምር መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ ይቀድስ፤ስብሐት እግዚአብሔር አሜን፡፡