ከግንቦት 6-19 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ንኡስ አንቀጽ 164 በተደነገገው መሠረት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የዘንድሮውን መደበኛ የርክበ ካህናት ስብሰባ ከግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ ሲያካሒድ ሰንብቷል፡፡ በዚሁ መሠረት የመክፈቻው ሥርዐተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከበዓሉ ዋዜማ ከግንቦት 5 ቀን 2006 ዓ.ም.ጀምሮ እስከ ግንቦት 19 ቀን 2006 ዓ.ም. ለ16 ቀናት ባደረገው ጉባኤ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለኅብረተሰቡ የሚጠቅመውን፤ ለሀገርና ለዓለም ሰላም የሚበጀውን አጀንዳ በማመቻቸት በስፋትና በጥልቀት ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡ ከተላለፉት ውሳኔዎች መካከል ዋናዋናዎቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡
1. ባለፉት ወራት 2006 ዓ.ም. ስለተከናወኑት መንፈሳውያንና ማኅበራውያን ተግባራት በቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ አማካይነት ቀርቦ ምልአተ ጉባኤው ያለውን ሁኔታ ከመረመረ በኋላ የተዘረጋው የልማት ዕቅድ ተፋጥኖ በተግባር እንዲረጋገጥ፣ ለውጤት የበቃውም ተጠናክሮ እንዲቀጥል መመሪያን ሰጥቷል፡፡
2. በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ መሪነት በሀገር ውስጥና በውጭው ዓለም ባሉ አህጉረ ስብከት የሚደረገው ሐዋርያዊ ጒዞ ለቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊውም ሆነ ማኅበራዊ አገልግሎት በእጅጉ ጠቃሚ ሆኖ በመገኘቱ ለዚሁ ሐዋርያዊ ጒዞ የሚያስፈልገውን ዓመታዊ በጀት፣ ጥናትና ማሻሻያ ተደርጎ ለቀጣዩ በጀት ዓመት እንዲቀርብ ተወስኗል፡፡
3. በቤተ ክርስቲያኒቱ በቅዱስ ሲኖዶስ በማእከል የሚደረገው የሜሮን አወጣጥ ዝግጅት ቀጣይነት እንዲኖረው ለማድረግ ሥራውን የሚከታተሉ ሦስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የተመደቡ ሲሆን ለሥራው የሚሆን በጀትም እንዲያዝ ተወስኗል፡፡
4. በመንበረ ፓትርያርክ ቅጥረ ግቢ የሚገኙ ብፁዓን አበው ወደ ሕክምና ቦታ ማመላለሻ፣ በውጭ አህጉረ ስብከት የሚኖሩ ብፁዓን አበው ከውጭ ሲመጡና ሲመለሱ መቀበያና መሸኛ የሚሆን መኪና በማስፈለጉ ለቀጣዩ በጀት ዓመት በጀት እንዲያዝ፤ እንዲሁም ከበጎ አድራጊዎች ርዳታ እንዲፈለግ ተወስኗል፡፡
5. የተዘጋጀውን ረቂቅ፣ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ምልአተ ጉባኤው በንባብ አዳምጦ በአብዛኛው ነጥቦች ላይ ማሻሻያ በማድረግና በማረም ለተጨማሪ እርማት ብፁዓን አባቶች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የሕግ ባለሙያዎች ያሉበት ኮሚቴ ቅዱስ ሲኖዶስ የሠየመ ሲሆን ረቂቅ ሕጉን ተመልክተው የበኩላቸውን እርምትና ማስተካከያ አድርገው ለጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እንዲያቀርቡ ተወስኗል፡፡
6. በሀገራችን በኅብረተሰቡ አንድነት እየተገነባ ያለው የዐባይ ሕዳሴ ግድብን በተመለከተ ቤተ ክርስቲያናችን ቀደም ሲል ካደረገችው የገንዘብ አስተዋፅኦ በተጨማሪ፤ ብፁዓን አበው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ የየወረዳውና የየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት፣ መንፈሳዊ ኮሌጆች፣ ገዳማትና መንፈሳውያን ት/ቤቶች፣ ሠራተኞች በበጎ ፈቃደኛነት የአንድ ወር ወርኃዊ ደመወዛቸውን ለቦንድ ግዢ እንዲያውሉ ተወስኗል፡፡
7. በስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አማካኝነት ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ ቀደም ሲል በምልአተ ጉባኤ ተወስኖ የነበረው የብዙኃን መገናኛ ሥርጭት ጥናት በባለሙያዎች ተጠንቶ በቀረበው መሠረት ምልአተ ጉባኤው ተነጋግሮ ለሚዲያዎቹ ስርጭት የተዘጋጀውን ደንብ አጽድቋል፡፡ የመገናኛ ብዙኃን ቦርድም በደንቡ መሠረት በቋሚ ሲኖዶስ እንዲቋቋምና ሥራውን እንዲቀጥል ውሳኔን አሳልፏል፡፡
8. ቤተ ክርስቲያናችን ሥራዋን በመሪ ዕቅድ ማከናወን እንድትችል ዕቅዱ ዳብሮ ለአሁኑ ጉባኤ እንዲቀርብ በጥቅምቱ ስብሰባ በተወሰነው መሠረት በባለሙያዎቹ ዳብሮ የተዘጋጀው መሪ ዕቅድ ዘገባ ለጉባኤው በስፋት የተገለጸ ሲሆን፤ የወደፊት መሪ ዕቅዱ ከዚህም በበለጠ ተዘጋጅቶ ወደ ሥራ ሊተረጐም በሚችልበት ሁኔታ ዳብሮ የመጨረሻው መሪ እቅድ በጥራዝ ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ ለማስቻል ጥናቱ በቋሚ ሲኖዶስ ታይቶ አስፈላጊው እንዲፈጸም ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
9. ቤተ ክርስቲያናችን ባሏት ክፍት ቦታዎችና በከተማው የመልሶ ማልማት ፕሮግራም መሠረት ወደፊት ሊገነቡ የታሰቡ ሕንጻዎችን አስመልክቶ በቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደርና ልማት ድርጅት ቦርድ አማካኝነት በቀረበው ሪፖርት ላይ ጉባኤው ተነጋግሮ የግንባታው ሥራ በአስቸኳይ የሚጀመርበት ሁኔታ ተጠናክሮ እንዲቀጥል መመሪያ ተሰጥቷል፡፡
10. የቤተ ክርስቲያኒቱ ቋሚ ንብረቶች ሁነው በመንበረ ፓትርያርክ አካባቢ የሚገኙ እስከ አሁን ድረስ ያልተመለሱ 4 ሕንጻዎችን በተመለከተ ለቤተክርስቲያኒቱ ባለመመለሳቸው ምክንያት ምልአተ ጉባኤው ሰፊ ውይይት ያደረገ ሲሆን ወደፊት ሕንጻዎቹ በሚመለሱበት ሁኔታ አስፈላጊው ክትትል ሁሉ እንዲደረግ ከስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡
11. ገዳማትን መልሶ ማቋቋምና ማጠናከር እንዲቻል የገቢ ምንጭ ለመፍጠር ሲባል ሰፋ ያለ ጥናት ተጠንቶ እንዲቀርብ በጥቅምቱ ምልአተ ጉባኤ ብፁዓን አበው ያሉበት አንድ ኮሚቴ በሰየመው መሠረት ተዘጋጅቶ በቀረበው ጥናት ላይ ጉባኤው ተነጋግሮ በ40 ገዳማት ላይ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን ለማከናወን የቀረበውን ጥናት ጉባኤው አጽድቆ ሥራ ላይ እንዲውል ወስኗል፡፡
12. የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የቦርድ ደንብን በተመለከተ በደንቡ ላይ አንዳንድ መሻሻል የሚገባቸው ነጥቦች በመኖራቸው ይህንኑ ደንብ ተመልክተውና መሻሻል የሚገባውን አሻሽለው ለጥቅምት 2007 ዓ.ም. ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የሚያቀርቡ ከሊቃነ ጳጳሳትና ከሕግ ባለሙያዎች ኮሚቴ እንዲቋቋም ተደርጓል፡፡
13. የማኅበረ ቅዱሳንን መተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ በተመለከተ በ1994 ዓ.ም. ወጥቶ የነበረው ደንብ እንዲሻሻል ቀደም ሲል ተቋቁሞ የነበረው ኮሚቴ ያሻሻለው ደንብ ረቂቅ 34 ገጽ ለጉባኤው ቀርቦ ምልአተ ጉባኤው ከተመለከተ በኋላ በስፋት ውይይት ተደርጎበታል፡፡
14. በሦስት አህጉረ ስብከት የብፁዓን አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ዝውውር ማድረግ በማስፈለጉ (ሀ) ብፁዕ አቡነ አብርሃም የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ወደ ምዕራብ ጐጃም ፍኖተ ሰላም ሀገረ ስብከት እንዲዛወሩ፤ (ለ) ብፁዕ አቡነ ሰላማ ሊቀ ጳጳስ የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያንና የታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም የበላይ ጠባቂ ወደ ምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት እንዲዛወሩ ተወስኗል፤ (ሐ) ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ረዳትነታቸው ተነሥተው በሀገረ ስብከታቸው በጅማ እንዲኖሩ ተወስኗል፤
15. በደብረ ሊባኖስ ገዳም የአበው ማረፊያ ቤት ለመገንባት እንዲቻል ቀደም ሲል ተይዞ የነበረው በጀት ብር 2,500,000 (ሁለት ሚሊዮን አምስት መቶ ሺህ ብር) ለሌላ ሥራ በመዋሉና ግንባታውም ሳይከናወን የቀረ መሆኑን ጉባኤው ተገንዝቦ ከተወያየ በኋላ ይኸው በጀት ለ2007 ዓ.ም. ተይዞ እንዲቀርብና ግንባታው እንዲቀጥል መመሪያ ተሰጥቷል፡፡
16. ወደፊት ስለሚመረጡ ቆሞሳት እንዲዘጋጅ ተደርጎ የነበረውን መመዘኛ (ክራይቴሪያ) ጉባኤው በንባብ ካዳመጠ በኋላ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ከተረቀቀው መመዘኛ ጋር ተገናዝቦ ለወደፊቱ እንዲቀርብ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡
17. በመንበረ ፓትርያርክ ቅጥር ግቢ ላለው ብፁዓን አባቶች ማረፊያና ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ሕንጻዎች የሚያገለግል የመብራት ጀነሬተር በአስቸኳይ እንዲገዛ ጉባኤው ወስኗል፡፡
18. በእንግሊዝ ሀገር ለሚኖሩ የቤተክርስቲያናችን ተከታዮች ለሆኑ አማንያን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት ያቀረቡትን ብድር የገንዘብ ጥያቄ ጉባኤው ተነጋግሮ ከጠየቁት ብር 4,800,000 (አራት ሚሊዮን ስምንት መቶ ሺህ ብር) ውስጥ ብር 2,400,000 (ሁለት ሚሊዮን አራት መቶ ሺህ ብር) በስጦታ እንዲሰጣቸው ሆኖ የገንዘብ አሰባሰቡም በቋሚ ሲኖዶስ ታይቶ ውሳኔን እንዲያገኝ ምልአተ ጉባኤው መመሪያን ሰጥቷል፡፡