ከግንቦት 6-19 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ንኡስ አንቀጽ 164 በተደነገገው መሠረት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የዘንድሮውን መደበኛ የርክበ ካህናት ስብሰባ ከግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ ሲያካሒድ ሰንብቷል፡፡ በዚሁ መሠረት የመክፈቻው ሥርዐተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከበዓሉ ዋዜማ ከግንቦት 5 ቀን 2006 ዓ.ም.ጀምሮ እስከ ግንቦት 19 ቀን 2006 ዓ.ም. ለ16 ቀናት ባደረገው ጉባኤ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለኅብረተሰቡ የሚጠቅመውን፤ ለሀገርና ለዓለም ሰላም የሚበጀውን አጀንዳ በማመቻቸት በስፋትና በጥልቀት ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡ ከተላለፉት ውሳኔዎች መካከል ዋናዋናዎቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡

1. ባለፉት ወራት 2006 ዓ.ም. ስለተከናወኑት መንፈሳውያንና ማኅበራውያን ተግባራት በቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ አማካይነት ቀርቦ ምልአተ ጉባኤው ያለውን ሁኔታ ከመረመረ በኋላ የተዘረጋው የልማት ዕቅድ ተፋጥኖ በተግባር እንዲረጋገጥ፣ ለውጤት የበቃውም ተጠናክሮ እንዲቀጥል መመሪያን ሰጥቷል፡፡

2. በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ መሪነት በሀገር ውስጥና በውጭው ዓለም ባሉ አህጉረ ስብከት የሚደረገው ሐዋርያዊ ጒዞ ለቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊውም ሆነ ማኅበራዊ አገልግሎት በእጅጉ ጠቃሚ ሆኖ በመገኘቱ ለዚሁ ሐዋርያዊ ጒዞ የሚያስፈልገውን ዓመታዊ በጀት፣ ጥናትና ማሻሻያ ተደርጎ ለቀጣዩ በጀት ዓመት እንዲቀርብ ተወስኗል፡፡

3. በቤተ ክርስቲያኒቱ በቅዱስ ሲኖዶስ በማእከል የሚደረገው የሜሮን አወጣጥ ዝግጅት ቀጣይነት እንዲኖረው ለማድረግ ሥራውን የሚከታተሉ ሦስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የተመደቡ ሲሆን ለሥራው የሚሆን በጀትም እንዲያዝ ተወስኗል፡፡

4. በመንበረ ፓትርያርክ ቅጥረ ግቢ የሚገኙ ብፁዓን አበው ወደ ሕክምና ቦታ ማመላለሻ፣ በውጭ አህጉረ ስብከት የሚኖሩ ብፁዓን አበው ከውጭ ሲመጡና ሲመለሱ መቀበያና መሸኛ የሚሆን መኪና በማስፈለጉ ለቀጣዩ በጀት ዓመት በጀት እንዲያዝ፤ እንዲሁም ከበጎ አድራጊዎች ርዳታ እንዲፈለግ ተወስኗል፡፡

5. የተዘጋጀውን ረቂቅ፣ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ምልአተ ጉባኤው በንባብ አዳምጦ በአብዛኛው ነጥቦች ላይ ማሻሻያ በማድረግና በማረም ለተጨማሪ እርማት ብፁዓን አባቶች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የሕግ ባለሙያዎች ያሉበት ኮሚቴ ቅዱስ ሲኖዶስ የሠየመ ሲሆን ረቂቅ ሕጉን ተመልክተው የበኩላቸውን እርምትና ማስተካከያ አድርገው ለጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እንዲያቀርቡ ተወስኗል፡፡

6. በሀገራችን በኅብረተሰቡ አንድነት እየተገነባ ያለው የዐባይ ሕዳሴ ግድብን በተመለከተ ቤተ ክርስቲያናችን ቀደም ሲል ካደረገችው የገንዘብ አስተዋፅኦ በተጨማሪ፤ ብፁዓን አበው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ የየወረዳውና የየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት፣ መንፈሳዊ ኮሌጆች፣ ገዳማትና መንፈሳውያን ት/ቤቶች፣ ሠራተኞች በበጎ ፈቃደኛነት የአንድ ወር ወርኃዊ ደመወዛቸውን ለቦንድ ግዢ እንዲያውሉ ተወስኗል፡፡

7. በስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አማካኝነት ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ ቀደም ሲል በምልአተ ጉባኤ ተወስኖ የነበረው የብዙኃን መገናኛ ሥርጭት ጥናት በባለሙያዎች ተጠንቶ በቀረበው መሠረት ምልአተ ጉባኤው ተነጋግሮ ለሚዲያዎቹ ስርጭት የተዘጋጀውን ደንብ አጽድቋል፡፡ የመገናኛ ብዙኃን ቦርድም በደንቡ መሠረት በቋሚ ሲኖዶስ እንዲቋቋምና ሥራውን እንዲቀጥል ውሳኔን አሳልፏል፡፡

8. ቤተ ክርስቲያናችን ሥራዋን በመሪ ዕቅድ ማከናወን እንድትችል ዕቅዱ ዳብሮ ለአሁኑ ጉባኤ እንዲቀርብ በጥቅምቱ ስብሰባ በተወሰነው መሠረት በባለሙያዎቹ ዳብሮ የተዘጋጀው መሪ ዕቅድ ዘገባ ለጉባኤው በስፋት የተገለጸ ሲሆን፤ የወደፊት መሪ ዕቅዱ ከዚህም በበለጠ ተዘጋጅቶ ወደ ሥራ ሊተረጐም በሚችልበት ሁኔታ ዳብሮ የመጨረሻው መሪ እቅድ በጥራዝ ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ ለማስቻል ጥናቱ በቋሚ ሲኖዶስ ታይቶ አስፈላጊው እንዲፈጸም ጉባኤው ተስማምቷል፡፡

9. ቤተ ክርስቲያናችን ባሏት ክፍት ቦታዎችና በከተማው የመልሶ ማልማት ፕሮግራም መሠረት ወደፊት ሊገነቡ የታሰቡ ሕንጻዎችን አስመልክቶ በቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደርና ልማት ድርጅት ቦርድ አማካኝነት በቀረበው ሪፖርት ላይ ጉባኤው ተነጋግሮ የግንባታው ሥራ በአስቸኳይ የሚጀመርበት ሁኔታ ተጠናክሮ እንዲቀጥል መመሪያ ተሰጥቷል፡፡

10. የቤተ ክርስቲያኒቱ ቋሚ ንብረቶች ሁነው በመንበረ ፓትርያርክ አካባቢ የሚገኙ እስከ አሁን ድረስ ያልተመለሱ 4 ሕንጻዎችን በተመለከተ ለቤተክርስቲያኒቱ ባለመመለሳቸው ምክንያት ምልአተ ጉባኤው ሰፊ ውይይት ያደረገ ሲሆን ወደፊት ሕንጻዎቹ በሚመለሱበት ሁኔታ አስፈላጊው ክትትል ሁሉ እንዲደረግ ከስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡

11. ገዳማትን መልሶ ማቋቋምና ማጠናከር እንዲቻል የገቢ ምንጭ ለመፍጠር ሲባል ሰፋ ያለ ጥናት ተጠንቶ እንዲቀርብ በጥቅምቱ ምልአተ ጉባኤ ብፁዓን አበው ያሉበት አንድ ኮሚቴ በሰየመው መሠረት ተዘጋጅቶ በቀረበው ጥናት ላይ ጉባኤው ተነጋግሮ በ40 ገዳማት ላይ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን ለማከናወን የቀረበውን ጥናት ጉባኤው አጽድቆ ሥራ ላይ እንዲውል ወስኗል፡፡

12. የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የቦርድ ደንብን በተመለከተ በደንቡ ላይ አንዳንድ መሻሻል የሚገባቸው ነጥቦች በመኖራቸው ይህንኑ ደንብ ተመልክተውና መሻሻል የሚገባውን አሻሽለው ለጥቅምት 2007 ዓ.ም. ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የሚያቀርቡ ከሊቃነ ጳጳሳትና ከሕግ ባለሙያዎች ኮሚቴ እንዲቋቋም ተደርጓል፡፡

13. የማኅበረ ቅዱሳንን መተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ በተመለከተ በ1994 ዓ.ም. ወጥቶ የነበረው ደንብ እንዲሻሻል ቀደም ሲል ተቋቁሞ የነበረው ኮሚቴ ያሻሻለው ደንብ ረቂቅ 34 ገጽ ለጉባኤው ቀርቦ ምልአተ ጉባኤው ከተመለከተ በኋላ በስፋት ውይይት ተደርጎበታል፡፡

14. በሦስት አህጉረ ስብከት የብፁዓን አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ዝውውር ማድረግ በማስፈለጉ (ሀ) ብፁዕ አቡነ አብርሃም የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ወደ ምዕራብ ጐጃም ፍኖተ ሰላም ሀገረ ስብከት እንዲዛወሩ፤ (ለ) ብፁዕ አቡነ ሰላማ ሊቀ ጳጳስ የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያንና የታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም የበላይ ጠባቂ ወደ ምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት እንዲዛወሩ ተወስኗል፤ (ሐ) ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ረዳትነታቸው ተነሥተው በሀገረ ስብከታቸው በጅማ እንዲኖሩ ተወስኗል፤

15. በደብረ ሊባኖስ ገዳም የአበው ማረፊያ ቤት ለመገንባት እንዲቻል ቀደም ሲል ተይዞ የነበረው በጀት ብር 2,500,000 (ሁለት ሚሊዮን አምስት መቶ ሺህ ብር) ለሌላ ሥራ በመዋሉና ግንባታውም ሳይከናወን የቀረ መሆኑን ጉባኤው ተገንዝቦ ከተወያየ በኋላ ይኸው በጀት ለ2007 ዓ.ም. ተይዞ እንዲቀርብና ግንባታው እንዲቀጥል መመሪያ ተሰጥቷል፡፡

16. ወደፊት ስለሚመረጡ ቆሞሳት እንዲዘጋጅ ተደርጎ የነበረውን መመዘኛ (ክራይቴሪያ) ጉባኤው በንባብ ካዳመጠ በኋላ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ከተረቀቀው መመዘኛ ጋር ተገናዝቦ ለወደፊቱ እንዲቀርብ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡

17. በመንበረ ፓትርያርክ ቅጥር ግቢ ላለው ብፁዓን አባቶች ማረፊያና ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ሕንጻዎች የሚያገለግል የመብራት ጀነሬተር በአስቸኳይ እንዲገዛ ጉባኤው ወስኗል፡፡

18. በእንግሊዝ ሀገር ለሚኖሩ የቤተክርስቲያናችን ተከታዮች ለሆኑ አማንያን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት ያቀረቡትን ብድር የገንዘብ ጥያቄ ጉባኤው ተነጋግሮ ከጠየቁት ብር 4,800,000 (አራት ሚሊዮን ስምንት መቶ ሺህ ብር) ውስጥ ብር 2,400,000 (ሁለት ሚሊዮን አራት መቶ ሺህ ብር) በስጦታ እንዲሰጣቸው ሆኖ የገንዘብ አሰባሰቡም በቋሚ ሲኖዶስ ታይቶ ውሳኔን እንዲያገኝ ምልአተ ጉባኤው መመሪያን ሰጥቷል፡፡

ግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ሞትን በሞቱ ድል አድርጎ፣ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ፣ በኀይለ መለኮቱ ከሙታን ተለይቶ የተነሣው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁላችንንም በልዩ አጠራሩ ጠርቶ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በሚካሄደው በዚህ ክርስቶሳዊና ሐዋርያዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ዐቢይ ጉባኤ ስለሰበሰበን ክብርና ምስጋና ለእርሱ ይሁን፡፡

“ወንሩጽ በትዕግሥት ኀበ ዘጽኑሕ ለነ ተስፋነ ዘሃይማኖት ተጠብቆልን ወዳለ ተስፋ ሃይማኖት ለመድረስ በትዕግሥት እንሩጥ” (ዕብ. 12፥1)

ርክበ ካህናት ተብሎ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን በሚታወቀው፣ ከጌታችን በዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን፣ ማለትም በመንፈቀ በዓለ ኃምሣ በየዓመቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንዲደረግ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስትደነግግ ትልቅ ዐላማ አላት፤ የጉባኤው ዐላማ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከመንፈስ ቅዱስ በተሰጣቸው ሐዋርያዊ ተልእኮ መሠረት በየተመደቡበት ሀገረ ስብከት ሲሠሩ በመንፈሳዊም ሆነ በአስተዳደራዊ ሥራቸው ያጋጠመ እክል ካለ በጋራ ተሰብስበው ችግሩን መፍታት የሚያስችል ጥበብ እንዲፈልጉለት ለማድረግ ነው፡፡

ከዚህም ጋር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቃለ ቅዱስ ወንጌልን ለሰው ሁሉ ማዳረስ የምትችልበትን ብልኀት በመንደፍ ሰውን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመጥራት ዝግጅት የምታደርግበት ዐቢይ ጉባኤ ነው፡፡
የቤተ ክርስቲያን ቀዳሚ ተልእኮ “ሑሩ ወስብኩ ወንጌለ ለኲሉ ፍጥረት፤ ሂዱ፣ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ” የሚለው አምላካዊ ትእዛዝ ነው። (ማር. 16፥15)

የቤተ ክርስቲያን ሥራ በርከት ያለ ቢሆንም ተጠቃልሎ ሲታይ ለሰብከተ ወንጌል ድጋፍ ሰጪ እንጂ ቤተ ክርስቲያን ከስብከተ ወንጌል ውጭ ሌላ ተግባር የላትም፡፡ እኛ የሐዋርያት ተከታዮች የሆንን ሊቃነ ጳጳሳትና ከዚያም በየደረጃው የተሰየሙ ካህናት በሙሉ እንድንሄድ የታዘዝነው ወደ አንድ ሀገረ ስብከት ብቻ ሳይሆን ወደ ዓለም ሁሉ ነው፣ የላከን አምላክ ድንበርና ወሰን የሌለው እንደሆነ ሁሉ መንግሥቱም እንደዚሁ ድንበር የለሽ ነው፤ እኛም የእርሱን ሥልጣን ስለተቀበልን ተልእኮአችን ድንበርና ወሰን የለውም፡፡

ይህም ሲባል ቅዱስ ሲኖዶስ በቤተ ክርስቲያን ላይ ያለው ሥልጣን በድንበር የተገደበ አይደለም ለማለት እንጂ የሥራ መደብ የለም ማለት አይደለም፤ ስለሆነም ቅዱስ ሲኖዶስ ማየት ያለበት በአንድ ሀገር ውስጥ ያለውን ብቻ ሳይሆን ከዚያም በላይ በዓለም ሁሉ ወንጌልን እንዴት ማዳረስ እንዳለበት በሚቃኝ መልኩ ነው፡፡

ከዚህ አኳያ ወንጌልን ለዓለም የማድረስ ተልእኮ የኛ የሊቃነ ጳጳሳቱ እስከሆነ ከሁሉም ዘንድ ለመድረስ ጠንክሮ መሮጥ የኛ ግዴታ ነው፣ ሆኖም ሩጫው ዕንቅፋት አጋጥሞት ለጉዳት እንዳይዳርገን ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን ትዕግሥትና ማስተዋል ያልተለየው ሊሆን ይገባል፡፡ ትዕግሥትና ማስተዋልን ገንዘብ አድርጎ ሥራን መሥራት ትልቅ ጥበብ እንጂ ቸልተኝነት አይደለም፤ ሃይማኖት የሚጠበቀው፣ ድኅነትም የሚገኘው፣ በትዕግሥት እንደሆነ ራሱ ባለቤቱ “ወበትዕግሥትክሙ ታጠርይዋ ለነፍስክሙ” በማለት አስተምሮናል፡፡

ታላቁ የቤተ ክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድም አርምሞ ተዐግሦ ተዐቅብ ሃይማኖተ ማለትም ነገሮችን ታግሦ በማስተዋል ማለፍ ሃይማኖትን ትጠብቃለች ብሎ አስተምሮናል፡፡ መልእክቱ በዋናነት መሮጥንና ትዕግሥትን አጣጥሞና አገናዝቦ መሥራት አስፈላጊ እንደሆነ ያሳያል፤ ይህ ለሥራችን መቃናት በጣም ጠቃሚ ነው፣ «መዘናጋት እንዳይኖር እንሩጥ፣ ስሕተትም እንዳይበዛ በትዕግሥት ይሁን፣» የሚለውን መርሕ መከተል ለሁላችንም ይበጃል፡፡

ባለፈው ዓመት የርክበ ካህናት ጉባኤያችን በቤተ ክርስቲያናችን መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን፣ ብልሹ አሠራር እንዲታረም፣ ቤተ ክርስቲያናችን ልዕልናዋና ክብሯ፣ ንጽሕናዋና ቅድስናዋ፣ አንድነትዋና ሥርዐቷ፣ እንደነበረው ተጠናክሮ እንዲቀጥል የሚያስችሉ ውሳኔዎችን መወሰናችን ይታወቃል፡፡ በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ የወሰናቸው ውሳኔዎች በጥናት ተመሥርተው ደረጃ በደረጃ በተግባር ይተረጎሙ ዘንድ ልዩ ልዩ ኮሚቴዎች ተቋቁመዋል፤ ኮሚቴዎቹም የመጀመሪያ ዙር ጥናታቸውን በጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አቅርበው እንዲታይ አድርገዋል፡፡

ከዚያም በኋላ ጥናቶቹ በሊቃውንትና በባለሙያዎች እየታገዙ የቀጠሉ ቢሆኑም በሥራው ሂደት በመጠኑም ቢሆን አንዳንድ መሰናክሎች አልነበሩም ማለት አይቻልም፤ ይሁን እንጂ ቀዋሚ ሲኖዶስ በየጊዜው በሚያደርገው ክትትልና በሚሰጠው አመራር መልክ እየያዙና መሠረተ ደልደላ እየሆኑ ሥራቸውን ቀጥለዋል፡፡ በተለይም በማእከል የተቋቋመው ኮሚቴና ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ደንብ አጥኚ ተብሎ በድጋሚ የተሰየመው ኮሚቴ በአንድነት ሆነው ሥራውን ለመሥራት ያሳዩት ቅን ተነሳሽነት ለሥራው ጥራትና ቅልጥፍና ተስፋ የሚሰጥ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር ላይ የሚታየው ክፍተት የቆየና ሥር የሰደደ ከመሆኑ አንጻር በአጭር ጊዜ ይስተካከላል የሚል እምነት ብዙ ላይኖረን ይችላል፤ ይሁንና በጀመርነው መሥመር ከቀጠልን ሩቅ በማይባል ጊዜ ውስጥ ለውጦችን ማየት እንደምንችል ጥርጥር የለንም፡፡ ሆኖም መልካም አስተዳደር በፍጥነት እንዲሰፍን ወሳኝ የሆኑ መሣሪያዎች እንደሚያስፈልጉን በዚህ አጋጣሚ ሳንጠቅስ አናልፍም፤ እነዚህም፤

1. በየአቅጣጫው ለሚነፍሱ የውጭ ነፋሳት የማይበገር አንድነት፤

2. ሕገ ቤተ ክርስቲያንና ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን ብቻ ማእከል አድርጎ መሥራት፤

3. በእናውቅላችኋለን ባዮች ግራ ሳይጋቡ በራስ በመተማመን መወሰን፤

4. የቅዱስ ሲኖዶስ ሉዓላዊ ሥልጣን በማንም ይሁን በማን እንዳይገሠስ ጥብቅና መቆም የመሳሰሉ ባሕርያት ለዚህ ጉባኤ አስፈላጊ መሣሪያዎች ናቸው፡፡

ሌላው ከዚህ ጋር አያይዘን ማንሣት የምንፈልገው ዐቢይ ጉዳይ ቤተ ክርስቲያናችን ያላትን የሰው ኀይል በአግባቡ አልምቶ ለተሻለ ውጤት የማብቃቱ ጉዳይ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ያለው የሰው ኀይል እንደሌላው ዓለም አጠቃቀም ብንጠቀምበት ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ለዓለም ሁሉ በአጠቃላይ ይበቃ እንደነበር ጥርጥር የለውም፡፡

ሁላችንም እንደምንገነዘበው በዓለም ውስጥ የሚገኘው ካህን በአጠቃላይ ቢበዛ ከሁለት ሚሊዮን የሚበልጥ ላይሆን ይችላል፣ ይሁንና የኛ ቤተ ክርስቲያን ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሚሆን የካህን ብዛት እያላት ለምን ብዙ የሥራ ክፍተቶች በየጊዜው ይከሠታሉ? የሚለውን ጥያቄ ይህ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በውል ሊያጤነው ይገባል፡፡

እየተፈጠረ ያለው ክፍተት ባጭሩ ለመጠቆም ያህል ያለንን የሰው ኀይል በዕውቀት አልምተን ክፍተቱን ከመሙላት ይልቅ “በምንስ የደነቈረ ምን ሲል ይኖራል” እንደሚባለው ከመቶ ዓመት በፊት የነበሩት አስገዳጅ ሁኔታዎች ያመጡብንን የዘመናት ልምዶች እንደመልካም ባህል ይዘን በዚያው በመቀጠላችን ክፍተቱ ተፈጥሮአል የሚል ጽኑ እምነት አለን፤ ለቤተ ክርስቲያን አይደለም ለራሱ እንኳ በአግባቡ መቆም ያልቻለ የሰው ኀይል ይዘን የትም መድረስ አንችልም፤ ሆኖም ይህን ችግር ለማስተካከል ያለውን በማፍለስ ሌላ አዲስ ተክልን መትከል ሳይሆን ያለውን የሰው ኀይል በማልማትና በሥሩ የሠለጠነ የሰው ኀይልን በማስከተል ማስተካከል እንዳለብን ሊሠመርበት ይገባል፡፡ ስለሆነም ያለንን የሰው ኀይል በዕውቀት በማልማት ክፍተቱን መሙላት ጊዜ የማይሰጥ ስለሆነ ይህ ዐቢይ ጉባኤ ሊያስብበት ይገባል እንላለን፡፡

ያለንበት ጊዜ እጅግ በጣም ከፍተኛ ውድድር የሚታይበት ጊዜ ነው፤ ሀገራችን ኢትዮጵያም በዚህ ውድድር ባደረገችው ርብርቦሽ ዓለም በአድናቆት የተናገረለት የልማትና የእድገት ጎዳና ላይ ትገኛለች፡፡ ከዚህ ከአዲስ አበባ ጀምሮ እስከ ገጠሩ ድረስ በተንቀሳቀስን ቊጥር የምናየው ነገር ሁሉ ልማትና ግንባታ ነው፣ ትምህርት ቤቱ፣ የጤና ኬላው፣ የመስኖ እርሻው፣ የትራንስፖርት ግንባታው፣ የመሠረተ ልማት ዝርጋታው ሁሉ ሲጣደፍ ይታያል፤ ይህ ከእግዚአብሔር ለኢትዮጵያ የተሰጠ ታላቅ በረከት ነው፡፡

በመሆኑም ቤተ ክርስቲያናችን የልማት በረከቱ ባለበት ብቻ እንዲቀጥል ሳይሆን ካለበት በበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ሕዝቡን በማስተማር ለልማቱና ለእድገቱ በሰፊው መንቀሳቀስ አለባት፣ የተለመደውን ሀገራዊ ኀላፊነቷም መወጣት አለባት፣ ቤተ ክርስቲያናችን ለዚህች ሀገር አንድነት መጠበቅና ለህልውናዋ ቀጣይነት ለሦስት ሺሕ ዘመናት ያህል የሠራችው ጒልህና ደማቅ ሥራ አሁንም መድገም አለባት፣ ቤተ ክርስቲያናችን ዛሬም እንደቀድሞው ሃይማኖታዊና ልማታዊ ሥራን በመሥራት የመሪነት ሚናዋን የምታጠናክርበት አቅጣጫ ይህ ጉባኤ መቀየስ አለበት፡፡

ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ተልእኮዋን በብቃት ከመወጣት ባሻገር በትምህርት ዘርፍ፣ በጤና ዘርፍ፣ በራስ አገዝ ልማት ዘርፍ፣ ወዘተ … በመሳሰሉት ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሥራዎች ሕዝቡን አስተባብራ በየቅጽረ ቤተ ክርስቲያኑ መገንባት አለባት፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚሰበሰብበት ዋና ዐላማ እነዚህና እነዚህን የመሳሰሉ ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ዐበይት ጉዳዮችን በማጥናት፣ በመገምገምና በመወሰን የተጣለበትን ኀላፊነት ለመወጣት ነው፡፡ ስለሆነም መልካም አስተዳደር በማስፈን ለተሻለ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት መሠረት የሚሆኑ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ጉባኤው የተጣለበትን ኀላፊነት በተገቢው ይወጣ ዘንድ አሳስባለሁ፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ጉባኤያችንን ይባርክ ይቀድስ አሜን