• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ሞትን በሞቱ ድል አድርጎ፣ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ፣ በኀይለ መለኮቱ ከሙታን ተለይቶ የተነሣው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁላችንንም በልዩ አጠራሩ ጠርቶ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በሚካሄደው በዚህ ክርስቶሳዊና ሐዋርያዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ዐቢይ ጉባኤ ስለሰበሰበን ክብርና ምስጋና ለእርሱ ይሁን፡፡

“ወንሩጽ በትዕግሥት ኀበ ዘጽኑሕ ለነ ተስፋነ ዘሃይማኖት ተጠብቆልን ወዳለ ተስፋ ሃይማኖት ለመድረስ በትዕግሥት እንሩጥ” (ዕብ. 12፥1)

ርክበ ካህናት ተብሎ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን በሚታወቀው፣ ከጌታችን በዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን፣ ማለትም በመንፈቀ በዓለ ኃምሣ በየዓመቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንዲደረግ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስትደነግግ ትልቅ ዐላማ አላት፤ የጉባኤው ዐላማ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከመንፈስ ቅዱስ በተሰጣቸው ሐዋርያዊ ተልእኮ መሠረት በየተመደቡበት ሀገረ ስብከት ሲሠሩ በመንፈሳዊም ሆነ በአስተዳደራዊ ሥራቸው ያጋጠመ እክል ካለ በጋራ ተሰብስበው ችግሩን መፍታት የሚያስችል ጥበብ እንዲፈልጉለት ለማድረግ ነው፡፡

ከዚህም ጋር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቃለ ቅዱስ ወንጌልን ለሰው ሁሉ ማዳረስ የምትችልበትን ብልኀት በመንደፍ ሰውን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመጥራት ዝግጅት የምታደርግበት ዐቢይ ጉባኤ ነው፡፡
የቤተ ክርስቲያን ቀዳሚ ተልእኮ “ሑሩ ወስብኩ ወንጌለ ለኲሉ ፍጥረት፤ ሂዱ፣ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ” የሚለው አምላካዊ ትእዛዝ ነው። (ማር. 16፥15)

የቤተ ክርስቲያን ሥራ በርከት ያለ ቢሆንም ተጠቃልሎ ሲታይ ለሰብከተ ወንጌል ድጋፍ ሰጪ እንጂ ቤተ ክርስቲያን ከስብከተ ወንጌል ውጭ ሌላ ተግባር የላትም፡፡ እኛ የሐዋርያት ተከታዮች የሆንን ሊቃነ ጳጳሳትና ከዚያም በየደረጃው የተሰየሙ ካህናት በሙሉ እንድንሄድ የታዘዝነው ወደ አንድ ሀገረ ስብከት ብቻ ሳይሆን ወደ ዓለም ሁሉ ነው፣ የላከን አምላክ ድንበርና ወሰን የሌለው እንደሆነ ሁሉ መንግሥቱም እንደዚሁ ድንበር የለሽ ነው፤ እኛም የእርሱን ሥልጣን ስለተቀበልን ተልእኮአችን ድንበርና ወሰን የለውም፡፡

ይህም ሲባል ቅዱስ ሲኖዶስ በቤተ ክርስቲያን ላይ ያለው ሥልጣን በድንበር የተገደበ አይደለም ለማለት እንጂ የሥራ መደብ የለም ማለት አይደለም፤ ስለሆነም ቅዱስ ሲኖዶስ ማየት ያለበት በአንድ ሀገር ውስጥ ያለውን ብቻ ሳይሆን ከዚያም በላይ በዓለም ሁሉ ወንጌልን እንዴት ማዳረስ እንዳለበት በሚቃኝ መልኩ ነው፡፡

ከዚህ አኳያ ወንጌልን ለዓለም የማድረስ ተልእኮ የኛ የሊቃነ ጳጳሳቱ እስከሆነ ከሁሉም ዘንድ ለመድረስ ጠንክሮ መሮጥ የኛ ግዴታ ነው፣ ሆኖም ሩጫው ዕንቅፋት አጋጥሞት ለጉዳት እንዳይዳርገን ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን ትዕግሥትና ማስተዋል ያልተለየው ሊሆን ይገባል፡፡ ትዕግሥትና ማስተዋልን ገንዘብ አድርጎ ሥራን መሥራት ትልቅ ጥበብ እንጂ ቸልተኝነት አይደለም፤ ሃይማኖት የሚጠበቀው፣ ድኅነትም የሚገኘው፣ በትዕግሥት እንደሆነ ራሱ ባለቤቱ “ወበትዕግሥትክሙ ታጠርይዋ ለነፍስክሙ” በማለት አስተምሮናል፡፡

ታላቁ የቤተ ክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድም አርምሞ ተዐግሦ ተዐቅብ ሃይማኖተ ማለትም ነገሮችን ታግሦ በማስተዋል ማለፍ ሃይማኖትን ትጠብቃለች ብሎ አስተምሮናል፡፡ መልእክቱ በዋናነት መሮጥንና ትዕግሥትን አጣጥሞና አገናዝቦ መሥራት አስፈላጊ እንደሆነ ያሳያል፤ ይህ ለሥራችን መቃናት በጣም ጠቃሚ ነው፣ «መዘናጋት እንዳይኖር እንሩጥ፣ ስሕተትም እንዳይበዛ በትዕግሥት ይሁን፣» የሚለውን መርሕ መከተል ለሁላችንም ይበጃል፡፡

ባለፈው ዓመት የርክበ ካህናት ጉባኤያችን በቤተ ክርስቲያናችን መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን፣ ብልሹ አሠራር እንዲታረም፣ ቤተ ክርስቲያናችን ልዕልናዋና ክብሯ፣ ንጽሕናዋና ቅድስናዋ፣ አንድነትዋና ሥርዐቷ፣ እንደነበረው ተጠናክሮ እንዲቀጥል የሚያስችሉ ውሳኔዎችን መወሰናችን ይታወቃል፡፡ በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ የወሰናቸው ውሳኔዎች በጥናት ተመሥርተው ደረጃ በደረጃ በተግባር ይተረጎሙ ዘንድ ልዩ ልዩ ኮሚቴዎች ተቋቁመዋል፤ ኮሚቴዎቹም የመጀመሪያ ዙር ጥናታቸውን በጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አቅርበው እንዲታይ አድርገዋል፡፡

ከዚያም በኋላ ጥናቶቹ በሊቃውንትና በባለሙያዎች እየታገዙ የቀጠሉ ቢሆኑም በሥራው ሂደት በመጠኑም ቢሆን አንዳንድ መሰናክሎች አልነበሩም ማለት አይቻልም፤ ይሁን እንጂ ቀዋሚ ሲኖዶስ በየጊዜው በሚያደርገው ክትትልና በሚሰጠው አመራር መልክ እየያዙና መሠረተ ደልደላ እየሆኑ ሥራቸውን ቀጥለዋል፡፡ በተለይም በማእከል የተቋቋመው ኮሚቴና ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ደንብ አጥኚ ተብሎ በድጋሚ የተሰየመው ኮሚቴ በአንድነት ሆነው ሥራውን ለመሥራት ያሳዩት ቅን ተነሳሽነት ለሥራው ጥራትና ቅልጥፍና ተስፋ የሚሰጥ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር ላይ የሚታየው ክፍተት የቆየና ሥር የሰደደ ከመሆኑ አንጻር በአጭር ጊዜ ይስተካከላል የሚል እምነት ብዙ ላይኖረን ይችላል፤ ይሁንና በጀመርነው መሥመር ከቀጠልን ሩቅ በማይባል ጊዜ ውስጥ ለውጦችን ማየት እንደምንችል ጥርጥር የለንም፡፡ ሆኖም መልካም አስተዳደር በፍጥነት እንዲሰፍን ወሳኝ የሆኑ መሣሪያዎች እንደሚያስፈልጉን በዚህ አጋጣሚ ሳንጠቅስ አናልፍም፤ እነዚህም፤

1. በየአቅጣጫው ለሚነፍሱ የውጭ ነፋሳት የማይበገር አንድነት፤

2. ሕገ ቤተ ክርስቲያንና ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን ብቻ ማእከል አድርጎ መሥራት፤

3. በእናውቅላችኋለን ባዮች ግራ ሳይጋቡ በራስ በመተማመን መወሰን፤

4. የቅዱስ ሲኖዶስ ሉዓላዊ ሥልጣን በማንም ይሁን በማን እንዳይገሠስ ጥብቅና መቆም የመሳሰሉ ባሕርያት ለዚህ ጉባኤ አስፈላጊ መሣሪያዎች ናቸው፡፡

ሌላው ከዚህ ጋር አያይዘን ማንሣት የምንፈልገው ዐቢይ ጉዳይ ቤተ ክርስቲያናችን ያላትን የሰው ኀይል በአግባቡ አልምቶ ለተሻለ ውጤት የማብቃቱ ጉዳይ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ያለው የሰው ኀይል እንደሌላው ዓለም አጠቃቀም ብንጠቀምበት ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ለዓለም ሁሉ በአጠቃላይ ይበቃ እንደነበር ጥርጥር የለውም፡፡

ሁላችንም እንደምንገነዘበው በዓለም ውስጥ የሚገኘው ካህን በአጠቃላይ ቢበዛ ከሁለት ሚሊዮን የሚበልጥ ላይሆን ይችላል፣ ይሁንና የኛ ቤተ ክርስቲያን ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሚሆን የካህን ብዛት እያላት ለምን ብዙ የሥራ ክፍተቶች በየጊዜው ይከሠታሉ? የሚለውን ጥያቄ ይህ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በውል ሊያጤነው ይገባል፡፡

እየተፈጠረ ያለው ክፍተት ባጭሩ ለመጠቆም ያህል ያለንን የሰው ኀይል በዕውቀት አልምተን ክፍተቱን ከመሙላት ይልቅ “በምንስ የደነቈረ ምን ሲል ይኖራል” እንደሚባለው ከመቶ ዓመት በፊት የነበሩት አስገዳጅ ሁኔታዎች ያመጡብንን የዘመናት ልምዶች እንደመልካም ባህል ይዘን በዚያው በመቀጠላችን ክፍተቱ ተፈጥሮአል የሚል ጽኑ እምነት አለን፤ ለቤተ ክርስቲያን አይደለም ለራሱ እንኳ በአግባቡ መቆም ያልቻለ የሰው ኀይል ይዘን የትም መድረስ አንችልም፤ ሆኖም ይህን ችግር ለማስተካከል ያለውን በማፍለስ ሌላ አዲስ ተክልን መትከል ሳይሆን ያለውን የሰው ኀይል በማልማትና በሥሩ የሠለጠነ የሰው ኀይልን በማስከተል ማስተካከል እንዳለብን ሊሠመርበት ይገባል፡፡ ስለሆነም ያለንን የሰው ኀይል በዕውቀት በማልማት ክፍተቱን መሙላት ጊዜ የማይሰጥ ስለሆነ ይህ ዐቢይ ጉባኤ ሊያስብበት ይገባል እንላለን፡፡

ያለንበት ጊዜ እጅግ በጣም ከፍተኛ ውድድር የሚታይበት ጊዜ ነው፤ ሀገራችን ኢትዮጵያም በዚህ ውድድር ባደረገችው ርብርቦሽ ዓለም በአድናቆት የተናገረለት የልማትና የእድገት ጎዳና ላይ ትገኛለች፡፡ ከዚህ ከአዲስ አበባ ጀምሮ እስከ ገጠሩ ድረስ በተንቀሳቀስን ቊጥር የምናየው ነገር ሁሉ ልማትና ግንባታ ነው፣ ትምህርት ቤቱ፣ የጤና ኬላው፣ የመስኖ እርሻው፣ የትራንስፖርት ግንባታው፣ የመሠረተ ልማት ዝርጋታው ሁሉ ሲጣደፍ ይታያል፤ ይህ ከእግዚአብሔር ለኢትዮጵያ የተሰጠ ታላቅ በረከት ነው፡፡

በመሆኑም ቤተ ክርስቲያናችን የልማት በረከቱ ባለበት ብቻ እንዲቀጥል ሳይሆን ካለበት በበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ሕዝቡን በማስተማር ለልማቱና ለእድገቱ በሰፊው መንቀሳቀስ አለባት፣ የተለመደውን ሀገራዊ ኀላፊነቷም መወጣት አለባት፣ ቤተ ክርስቲያናችን ለዚህች ሀገር አንድነት መጠበቅና ለህልውናዋ ቀጣይነት ለሦስት ሺሕ ዘመናት ያህል የሠራችው ጒልህና ደማቅ ሥራ አሁንም መድገም አለባት፣ ቤተ ክርስቲያናችን ዛሬም እንደቀድሞው ሃይማኖታዊና ልማታዊ ሥራን በመሥራት የመሪነት ሚናዋን የምታጠናክርበት አቅጣጫ ይህ ጉባኤ መቀየስ አለበት፡፡

ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ተልእኮዋን በብቃት ከመወጣት ባሻገር በትምህርት ዘርፍ፣ በጤና ዘርፍ፣ በራስ አገዝ ልማት ዘርፍ፣ ወዘተ … በመሳሰሉት ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሥራዎች ሕዝቡን አስተባብራ በየቅጽረ ቤተ ክርስቲያኑ መገንባት አለባት፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚሰበሰብበት ዋና ዐላማ እነዚህና እነዚህን የመሳሰሉ ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ዐበይት ጉዳዮችን በማጥናት፣ በመገምገምና በመወሰን የተጣለበትን ኀላፊነት ለመወጣት ነው፡፡ ስለሆነም መልካም አስተዳደር በማስፈን ለተሻለ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት መሠረት የሚሆኑ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ጉባኤው የተጣለበትን ኀላፊነት በተገቢው ይወጣ ዘንድ አሳስባለሁ፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ጉባኤያችንን ይባርክ ይቀድስ አሜን

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/007-3.jpg 664 1000 tc https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc2014-05-14 20:45:072024-12-03 20:47:39ግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ሚያዝያ 12 ቀን የ2006 ዓ.ም በዓለ ትንሣኤ Link to: ሚያዝያ 12 ቀን የ2006 ዓ.ም በዓለ ትንሣኤ ሚያዝያ 12 ቀን የ2006 ዓ.ም በዓለ ትንሣኤ Link to: ከግንቦት 6-19 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች Link to: ከግንቦት 6-19 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች ከግንቦት 6-19 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top