ጥቅምት 13 ቀን 2012 ዓ.ም. በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች በልዩ ልዩ ምክንያቶች ሃይማኖትን፣ ብሔርና ቋንቋን መሠረት ያደረገ የሰው መግደልና የአብያተ ክርስቲያናት አስምልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በፍጹም የሚያወግዘው መሆኑን የተሰጠ መግለጫ በቅዱስነታቸው ተላልፏል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

«ተገሐሥ እምእኩይ ወግበር ሠናየ — ከክፉ ነገር ራቅ፤ ሰላምን ፈልጋት።»
(መዝ. 33፥12)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሥራቿና አምላኳ የሰላም አባትና አለቃ የሆነው ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደመሆኑ በጸሎቷና በአገልግሎቷ ስለ ሀገር ሰላም፣ ስለ ሕዝቦቿና ስለ መላው ዓለም ሰላም ዘወትር ወደአምላኳ ስታማፅንና ስትማልድ የኖረች ያለችና ወደፊትም የምትኖር የሀገር ባለውለታና የሁሉም እናት መሆኗ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ በሀገራችን በተለያዩ ክልሎች ልዩ ልዩ ምክንያቶች የአማራና የቅማንት፣ የሱማሌና የአፋር፣ የአማራና የትግራይ የኦሮሞና የአማራ የጉምዝና የአማራ የሲዳሞና የወላይታ በሚል ብሔርና ሃይማኖትን እንዲሁም ቋንቋን መሠረት ያደረገ በኢትዮጵያ ሀገራችን እንኳንስ ሊደረጉ ይቅርና ሊታሰቡ የማይገባቸው መጠነ ሰፊ ግጭቶች በመከሠታቸው የሰው ሕይወት ጠፍቷል፣ በርካታ ንብረት ወድሟል፣ ዜጎች ከቀያቸው አለአግባብ እየተፈናቀሉ ለከፋ እንግልትና ዕርዛት ተዳርገዋል፡፡ እስከ አሁን ድረስ በግጭቶች እየደረሱ ካሉት የሰው ሕይወት ጥፋትና የንብረት ውድመት ልንማር ባለመቻላችን በያዝነው ሳምንት ችግሩ ቀጥሎ በአዲስ አበባ፣ በኦሮምያ ክልልና በሌሎችም ክልሎች እየተከሠተ ያለው ግጭት እጅግ አሳሳቢ ከመሆኑም በላይ ጊዜ የማይሰጥና ሁሉም ኢትዮጵያውያን በአንድነትና በኅብረት ችግሩን ካልቀረፍነው መጠነ ሰፊ ጉዳትን የሚያስከትል ከመሆኑም በላይ በሀገራችን ያሉ ጅምር የልማትና የእድገት ጒዞዎችን በመግታት ሀገሪቱን ለከፍተኛ ጥፋትና ድህነት የሚዳርግ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ በመሆኑ ዓመታዊ ስብሰባውን በማካሄድ ላይ የሚገኘው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስለ ሀገር ሰላም ቅድሚያ በመስጠትና ከሌሎች የመወያያ አጀንዳዎች በማስቀደም በጉዳዩ ላይ በስፋት ከተወያየ በኋላ ተከታዩን አስቸኳይ የአቋም መግለጫና የሰላም ጥሪ አስተላልፏል፡፡

1. ማንኛውም የተለየ ሐሳብና አመለካከት ያለው ወገን ቢኖር ሐሳቡን በሠለጠነና በሰከነ መንገድ ሀገራዊ አንድነትን ማእከል ባደረገ ሁኔታ በክብ ጠረጴዛ በመወያየት ችግሮቹ እንዲፈቱና የአሠራር ግድፈቶች ካሉም እንዲታረሙ እንዲደረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፣
2. የሀገር ተረካቢ የሆናችሁ መላው የኢትዮጵያ ወጣቶች ሀገራችሁ ኢትዮጵያ ከዛሬ ይልቅ ነገ በእናንተ ተተኪነትና በምታከናውኑት የማይተካ የላቀ አስተዋፅኦ ወደ ላቀ የእድገት ደረጃ ደርሳ እናንተም ሆናችሁ መላው ወገናችሁ ተጠቃሚ የሚሆንባት የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባትና እውን ለማድረግ የሀገሪቱ ሙሉ ተስፋ በእናንተ በወጣት ልጆቻችን ትከሻ ላይ የተጣለ መሆኑ ይታወቃል፤ በመሆኑም በወቅታዊና ሚዛናዊ ባልሆነ አንዳንድ ከሕግ ማዕቀፍ የወጡ አካሄዶችን በሰከነ አእምሮ እና በትኵረት በመመልከት ሀገራችን ኢትዮጵያን ከጥፋትና ካልተገባ ግጭት ትታደጓት ዘንድ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከአደራ ጋር በአጽንዖት ለእናንተ ለልጆቿ ጥሪዋን ታስተላልፋለች፡፡
3. በሀገራችን ኢትዮጵያ የተፈጠረውን የመድበለ ፓርቲ ሥርዐት ተከትሎ ለሀገራችሁ የሚሆን ልዩ ልዩ አማራጭ ሐሳቦችን በማመንጨት ሕጋዊ ዕውቅና አግኝታችሁ በመንቀሳቀስ ላይ የምትገኙ ሁላችሁም የፖለቲካ ፓርቲዎች በሙሉ ፖሊሲ ቀርጻችሁና ያመናችሁበትን ርእዮተ ዓለም አቅዳችሁ የምትንቀሳቀሱት ሀገራችሁ ኢትዮጵያ ወደተሻለ የእድገት ደረጃ እንድትደርስ የበኩላችሁን ድርሻ ለመወጣት መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ ከዚህ አንጻር በየጊዜው ዘር፣ ብሔርና ሃይማኖትን መሠረት አድርገው እየተከሠቱ ያሉ ግጭቶችን ከጅምሩ በአንድነት ማስቆም ካልተቻለ ነገ የምትረከቧትና የምታስተዳድሯት ሀገር ልትኖር ስለማትችል በቅድሚያ የፖለቲካ አመለካከት ልዩነት ሳይገድባችሁ ለሀገር ሰላምና አንድነት በኅብረት ዘብ በመቆም የበኩላችሁን ኀላፊነት ትወጡ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
4. ለመንግሥታችሁና ለሕዝባችሁ ሙያዊ ትንታኔን መሠረት ያደረገ አማራጭ ሐሳቦችን በግብአትነት በማበርከት የሀገራችንን እድገትና የዲሞክራሲያዊ ሥርዐት ወደ ተሻለ ደረጃ እንዲደርስ የበኩላችሁን አስተዋፅኦ ለማበርከት በማሰብ ልዩ ልዩ ጽሑፎችንና ዘገባዎችን በመገናኛ ብዙኃንና በማኅበራዊ ሚዲያ የምታቀርቡና የምታስተላልፉ የፖለቲካ ተንታኞችና አክቲቪስቶች ከስሜት፣ ከብሔር፣ ከቋንቋና ከሃይማኖት ልዩነት በጸዳ ሁኔታ እናት ሀገራችሁን ማእከል በማድረግ ለተሻለ ሰላምና አንድነት የበኩላችሁን ድርሻ ከማበርከት ባለፈ ሕዝብን ከሕዝብ የሚያጋጩና አንዳንድ ያልተገቡ ትርክቶችን አላግባብ ከማሰራጨት በመቈጠብ ሀገራዊ ግዴታችሁን እንድትወጡ እናሳስባለን፤
5. የመንግሥትም ሆነ የግል የመገናኛ ብዙኃን ድርጅቶች ከተቋቋማችሁበት መሠረታዊ ተልእኮና ዓላማ አንጻር በተቻለ አቅም ዘርን፣ ቀለምን፣ ብሔርንና ሃይማኖትን መሠረት ካደረጉ የትንኮሳ ቃላቶች በመራቅና ሚዛናዊ የሆኑ መረጃዎችን ለሕዝባችን በማድረስ ለሀገራችን ኢትዮጵያ ሰላምና አንድነት የበኩላችሁን ኀላፊነት እንድትወጡ አደራ እንላለን፤
6. የማኅበራዊ ሚዲያ መሠረታዊ ዐላማው ዜጎች በእውነታ ላይ የተመሠረቱ ወቅታዊ መረጃዎችን በተሻለ ፍጥነት እንዲያገኙ ታስቦ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ግን በሀገራችን ኢትዮጵያ እየታየ ያለው እውነታ ከዚህ በተለየ መልኩ ሕዝብን ከሕዝብ፣ ብሔርን ከብሔር፣ ጎሳን ከጎሳ ሃይማኖትን ከሃይማኖት የሚያጋጩና ከእውነት የራቁ ግጭት ቀስቃሽ ሐሰተኛ መረጃዎችን በማሠራጨት ሀገራችን ኢትዮጵያ የቆየ የአብሮነትና የአንድነት ባህሏን በሚያጎድፍ መልኩ ላልተገባ ዐላማ እየዋለ መሆኑ አጠያያቂ አይደለም፤ ከዚህ አንጻር ዛሬ በሌሎች ላይ የሚደርሰው የሰው ሕይወት መጥፋትና የንብረት ውድመት ነገ በየአንዳንዱ ቤት ሲያንኳኳ ሁሉም የጉዳቱ ሰለባ እንደሚሆን በመረዳት በተቻለ ዐቅም የማኅበራዊ ሚዲያውን ለሀገራዊ ሰላምና አንድነት በመጠቀም ሁሉም የማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚው ሕዝባችን የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ እንጠይቃለን፤
7. ሀገር በዕውቀት እና በተሻለ ሐሳብ የምታድግና የምትመራ መሆኑ አጠያያቂ አይደለም፡፡ ከዚህ አንጻር የሀገራችን ምሁራን ያላቸው ድርሻ በቀላሉ ሊገመት የማይችል ሲሆን በአሁኑ ወቅት ግን አንዳንድ ምሁራን የሚያስተላልፏቸው የኢትዮጵያን ታሪክ መሠረት ያላደረጉ ትርክቶች ለሀገራችን የግጭትና ያለመግባባት መንሥኤ ሲሆኑ ይስተዋላሉ፡፡ በመሆኑም የሀገራችን ምሁራን በተቻለ አቅም ከልዩነትና ከግጭት ይልቅ ለሀገራዊ አንድነት እና ሰላም ኀላፊነታችሁን እንድትወጡ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፤
8. በየደረጃው ያላችሁ የመንግሥት የሥራ ኀላፊዎች መላው ሕዝባችን ትመሩትና ታስተዳድሩት ዘንድ የሰጣችሁን ይሁንታና ሀገራዊ ኀላፊነት ከግምት ውስጥ ባስገባና በታላቅ ሀገራዊ ኀላፊነት ስሜት በተቻለ መጠን ግጭቶችና አለመግባባቶች ከመከሠታቸው በፊት ልዩ ልዩ የውይይት መድረኮችን ለመላው ሕዝባችሁ በማዘጋጀት እና በውይይት መድረኩ የሚገኙትን ግብአት የዕቅዳችሁ አካል አድርጋችሁ በመተግበር ኀላፊነታችሁን ከቀድሞው በተሻለና በላቀ ሁኔታ በመፈጸም ለሀገራችን ሰላምና አንድነት እድገትና ብልጽግና የድርሻችሁን እንድትወጡ እንጠይቃለን፤
9. በየደረጃው ያላችሁ የፀጥታና የፍትሕ አካላት ሁሉ በተለያዩ ቦታዎች ግጭቶችና አለመግባባቶች ከመከሠታቸው በፊት ቅድመ መከላከልን መሠረት ያደረገ የፀጥታ ሥራን በመተግበር እየተከሠቱ ያሉ ግጭቶችንና የሰው ሕይወት መጥፋትን እንዲሁም የንብረት ውድመትን በመከላከል የተጣለባችሁን ኀላፊነት እንድትወጡ እናሳስባለን፤
10. መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ! እስከ አሁን ድረስ የኢትዮጵያን ሰላም በማይወዱ አካላት የሚከሠቱ ልዩ ልዩ አፍራሽና ግጭት ቀስቃሽ አጀንዳዎችን ወደጎን በመተውና በአርቆ አሳቢነትና በሀገር ባለቤትነት መጠነ ሰፊ ትዕግሥት የተሞላበት ሀገራዊ አንድነትና ኅብረት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ላበረከታችሁት የማይተካ ሚናና ታሪክ የማይረሳው ውለታ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም እያመሰገነ እንደአሁን ቀደሙ ሁሉ ለሀገራችን ሰላምና አንድነት ዘር፣ ብሔርና ሃይማኖት ሳይለያያችሁ እጅ ለእጅ በመያያዝ የበኩላችሁን የማይተካ ድርሻ እንድትወጡ የአደራ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፤
11. በሀገራችን ኢትዮጵያ የምትገኙ የሁሉም የሃይማኖት ተቋማት ሀገራችን ኢትዮጵያ በሃይማኖት ብዝኀነትና ተቻችሎና ተከባብሮ በመኖር አስደናቂ ባህሏ ሌሎች ሀገራት የሚቀኑባትና በአርኣያነትም የሚጠቅሷት ሀገር መሆኗ ይታወቃል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ይህን አኲሪና አርኣያ የሆነ ታሪኳን በሚያደበዝዝ ሁኔታ ሃይማኖትና ብሔርን መሠረት ያደረጉ ግጭቶች እየተበራከቱ በመሆናቸው ዜጎች ያለምንም መሸማቀቅና ተጽዕኖ እምነታቸውን ለማምለክና ለማስመለክ የማይችሉበት የሥጋት አደጋ እየተጋረጠ ከመሆኑ አንጻር ሁሉም ቤተ እምነቶች ለሀገራዊ አንድነትና ለእምነት ነፃነት በአንድነትና በኅብረት ለመላው ሕዝባችን የሰላም ጥሪ በማስተላለፍና ዘወትር በየአስተምህሮአችን ለሕዝባችን የሰላምን ጥሪ ተደራሽ በማድረግ ሀገራዊ ኀላፊነታችንን እንወጣ ዘንድ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡
12. በመጨረሻም ያለ ሀገር ሰላምና አንድነት እንዲሁም ፍቅርና እድገት መኖር ስለማይቻል መላው ሕዝባችን እንደየእምነቱና ሃይማኖቱ ሥርዐት ከዛሬ ጥቅምት 13 ቀን 2012ዓ.ም. ጀምሮ ለ3 ቀን ያህል በጾም፣ በጸሎትና በኀዘን ስለ ሀገር ሰላም በአንድነት ጥሪውን ለፈጣሪውና ለአምላኩ ያቀርብ ዘንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ጸሎትና ምሕላ እንዲደረግ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም ጥሪውን አስተላልፏል፡፡ መንፈሳዊ አዋጁንም አውጇል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!