• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ጥቅምት 12 ቀን 2012 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በደሙ የዋጀ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለዓመታዊው የጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ አደረሰን አደረሳችሁ፡፡

“ወይእዜኒ ረዐዩ ዘሀለዉ ኀቤክሙ መርዔቶ ለክርስቶስ፤ አሁንም በእናንተ ዘንድ ያሉትን የእግዚአብሔርን መንጋ ጠብቁ (1ኛ ጴጥ. 2፥6)፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪ፣ ጠባቂ፣ መጋቢ፣ አስተናባሪና አስተዳዳሪ ነው፤ በሰማይና በምድር ያለው የሚታየውና የማይታየው ፍጥረት በአጠቃላይ በእግዚአብሔር ጥበቃና አስተዳደር ሥር ነው፤ ፍጡራን ከእሱ በተገኘ የአእምሮ ነፃነት በሚፈጽሙት ተግባር የራሳቸው ድርሻና ኀላፊነት እንዳላቸው ቢታወቅም ያለእርሱ ዕውቅና የሚደረግ እንደሌለ ግን ከቅዱስ መጽሐፍ እንማራለን፡፡ እንግዲህ እሱ የጠባቂዎች ጠባቂ ሆኖ ሳለ ከፍጡራን ወገን ደግሞ በልዩ ምርጫው እየሾመ መንጋውን ወይም ፍጥረቱን ያስጠብቃል፤ ይህ ከጥንት ጀምሮ የነበረ የእግዚአብሔር አሠራር እንደሆነ ቅዱስ ያሬድ ሲገልጽ “ኢኀደጋ ለምድር እምቅድመ ዓለም ወእስከ ለዓለም እንበለ ካህናት ወዲያቆናት፤ ዓለም ከመፈጠሩ በፊት አንሥቶ እስከ ዘላለሙድረስ ምድርን ያለካህናት እና ያለ ዲያቆናት አልተዋትም” በማለት ያረጋግጣል፡፡

ይህ የሚያመለክተን እግዚአብሔር ዓለምን ያለ ጠባቂ የተወበት ዘመን ካለመኖሩም ሌላ ጠባቂዎቹ ካህናትና ዲያቆናት መሆናቸውን ነው፤ ካህናት የሚለው ስያሜ የወል ስም ሆኖ ከቅዱስ ፓትርያርክ ጀምሮ ያለው ውሉደ ክህነት በሙሉ እንደሚያጠቃልል ይታወቃል፡፡ ከዚህ አኳያ ኰኵሐ ሃይማኖት ቅዱስ ጴጥሮስ ከጌታችን በተሰጠው የጥበቃ ኀላፊነት መሠረት እሱም በክህነት ለወለዳቸው ልጆቹ በፈንታው “መንጋውን ጠብቁ” እያለ ምእመናንን ሲያስጠብቅ እናያለን፡፡ ትልቁ የእግዚአብሔር ትእዛዝና የቤተ ክርስቲያን ተልእኮም ይህ የጥበቃ ተግባር ነው፡፡

እግዚአብሔር እኛ ካህናትን በኀላፊነት የሾመበት ዋና ዐላማ መንጋውን እንድንጠብቅለት ነው፤ ይህ መንጋ ተብሎ የተገለጸው ወገን የተለየ ሕዝብና ጐሳ ሳይሆን ትዝምደ ሰብእን ወይም የሰው ዘርን በሙሉ ነው፡፡ በራሱ እምቢተኝነት ከሚቀርበት በስተቀር የጌታችን ጥሪ ለትዝምደ ሰብእ በሙሉ እንደሆነ “ሑሩ ወስብኩ ወንጌለ ለኵሉ ፍጥረት ሂዱ፥ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ” በማለት አሳውቆናል፡፡ እንዲህም ከሆነ ጠብቁ ተብለን የታዘዝነው ያመኑትን ወይም የተጠመቁትን ብቻ ሳይሆን ያላመኑትንም ያልተጠመቁትንም በአጠቃላይ እንደሆነ ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም፡፡

ከዚህ አንጻር መንጋችንን ስንጠብቅ ያመኑትን በነፍሳቸውም በሥጋቸውም ምንም ዐይነት ጉዳት እንዳይደርስባቸው የተሟላ ጥበቃና እንክብካቤ በማድረግ፣ ያላመኑትንም በፍቅር በማቅረብና ዘመድ ዘመድ በማለት፣ ውስጣዊና መንፈሳዊ ስሜታቸውን በመንፈስ ቅዱስ ኀይል በማነቃቃትና ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በማምጣት እንደሆነ ለሁላችን ግልጽ ነው፡፡ ሆኖም ይህን የጥበቃ ሥራ በአግባቡ ለማሳካት ትልቁ ትጥቃችን ቅዱስ ወንጌል እንደሆነ ምን ጊዜም መዘንጋት የለበትም፡፡ቃለ ቅዱስ ወንጌልን ለፍጥረት ሁሉ ለማዳረስ የተለያዩ ዘዴዎችንና አቀራረቦችን፣ ሥልጠናዎችንና አስተምህሮዎችን መጠቀምና በዚህም የባዘነውን በግ ወደ መንጋው የምንመለስበት ታሪካዊና ወቅታዊ ሥራ ከፊታችን ይጠብቀናል፡፡

በአሁኑ ጊዜ በየቀኑ የሚባክኑና በተኵላ የሚነጠቁ በጎች እጅግ እየተበራከቱ ነው፤ ዛሬ ሁሉም ነገር መልካም ነው ብለን የምንዘናጋበት ጊዜ ሳይሆን የጐደለውን ለመሙላት ቃል የምንገባበት፣ ያንኑም በተግባር ፈጽመን በጎቻችንን የምንሰበስብበት ጊዜ ነው፤ በዚህ አኳኋን በንቃትና በትጋት በኀላፊነትና በቊጭት ከሠራን ከባዘኑት በጎች መካከል ብዙዎቹን ወደ መንጋቸው መመለስ እንደምንችል፣ ያሉትም ባሉበት ጸንተው እንዲቀጥሉ ማድረግ እንደምንችል ምንም ጥርጥር የለውም፡፡

የጥበቃ ተግባራችን ከውጭ ኀይሎች ጣልቃ ገብነትና ከውስጥ ጥቅመኞች የተነሣ ተደጋጋሚ ዕንቅፋት በበዛበት በአሁኑ ጊዜ “በእንቅርት ላይ… ” እንደሚባለው በሀገራችን በተፈጠረው ያለመረጋጋት ክሥተት አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለዋል፣ ካህናትና ምእመናን ተገድለዋል፤ አሁንም ሥጋቱ እንዳለ፣ ከቀረበልን የአህጉረ ስብከት ሪፖርት ሰምተናል፤ በዐይናችንም አይተናል፤ ነባር የቤተ ክርስቲያናችን ይዞታዎች ሥልጣንን መከታ ባደረጉ ወገኖች እየተነጠቁ ነው፤ ምእመናን በሚደርስባቸው የማያባራ ተፅዕኖና አድልዎ ከቀያቸው እየተፈናቀሉና እየተሰደዱ ነው፡፡

ለመሆኑ እንዲህ ዐይነቱ ኢሰብኣዊ ድርጊት እስከ መቼ ነው የሚቀጥለው? ይህ ድርጊት እንዲቆም እስከ ሞት ድረስ መሥዋዕት መሆን ከዚህ ጉባኤ አባላት ይጠበቃል፡፡ ይህ ጉባኤ የኀያሉ የእግዚአብሔር ጉባኤ ነው፤ ይህ ጉባኤ በኢትዮጵያ ብቻ ከሰባ ሚሊዮን ያላነሰ ሠራዊት ያለው ጉባኤ እንጂ ብቻውን አይደለም፤ ይህ ጉባኤ በሙሉ ዐቅሙ ሥራውን ከሠራና ድምፁን ካነሣ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በዓለም ዙሪያ ሁሉ ሰሚው ብዙ ነው፡፡ ስለዚህ በቤተ ክርስቲያናችን ላይ በታችኛው የመንግሥት መዋቅር እየደረሰብን ያለውን የማንታገሠው ግፍ መንግሥት እንዲያስተካክልልን ደጋግመን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ እኛም በጸሎት አምላካችንን ከመማፀን ጋር ሁሌም በተጎጂው ሕዝባችን መካከል እየተገኘን በልዩ ልዩ ግፍ ልባቸው የተሰበረውን የልጆቻችን ኀዘን መቅረፍ ይኖርብናል፡፡ ችግራቸውንም መጋራት ይጠበቅብናል፤ የተቃጠሉ አብያተ ክርስቲያናትን እንደገና መገንባት አለብን፤ መንግሥትም በሕገ መንግሥቱ የተቀመጠውን የሃይማኖት ክብር ነጻነትና እኩልነትን በሚሸረሽሩ የታችኛው መዋቅር ባለሥልጣናት ላይ የማያዳግም የእርምት ማስተካከያ እንዲያደርግ ጥብቅ ክትትል ማድረግ አለብን፡፡

የመንጋ ጥበቃችን ሥራ እየተሰነካከለ የሚገኘው ከውጭ ሆነው በገንዘብ፣ በፖለቲካና በኢኮኖሚ እርስ በርሳችንን በመከፋፈል በሚተነኩሱን ኀይሎች ብቻ አይደለም፤ በውስጣችን ያለው ሕግ ያልጠበቀ አሠራርም የምእመናንን ልቡና እያቈሰለ የሚገኝ ሌላው የጥበቃችን ዕንቅፋት ነው፤በመሠረቱ ይህንን ችግር ከሥር መሠረቱ ነቅለን በማፅዳት ማስተካከል ካልቻልን ችግራችን በወሳኝ መልኩ ሊቀረፍ አይችልም፡፡

በመሆኑም ቀደም ሲል የተጠኑትን የቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ ችግር መፍትሔና የመሪ ዕቅድ ጥናቶች ይህ ዐቢይ ጉባኤ በወሰነው መሠረት ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በአስቸኳይ ይተገብር ዘንድ ጠበቅ ያለ መመሪያ ሊያስተላልፍ ይገባል፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ በብልሹ አስተዳደር አዙሪት የሚታመስ የቤተ ክርስቲያን አሠራር ሊኖር አይገባም፤ በዚህ ዓመት አሠራራችንን ሁሉ አስተካክለን ወደ መንጋ ጥበቃና ወደ ልማት ሥራችን በፍጥነት መሸጋገር አለብን፡፡

በመጨረሻም፡- የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያናችን ላይ በተደጋጋሚ እየደረሰ ያለውን ዙሪያ መለስ ጥቃት ለመመከትና ለመከላከል ብሎም ለማስቆም አንድ የጥቃት መከላከል ግብረ ኀይል እንደዚሁም በየአካባቢው የሚሰነዘሩትን ጥቃቶች፣ ወከባዎች፣ ተጽዕኖዎችና አድላዊ አሠራሮችን እየተከታተለ ትክክለኛ ኢንፎርሜሽንን የሚያቀርብ የኮሙኒኬሽን ግብረ ኀይል በአሁኑ ጉባኤያችን አቋቁመን ቤተ ክርስቲያናችንንና መንጋችንን ከመከራ እንድንታደግ የሀገራችንን ሰላምና የሕዝባችንን አንድነትም በጽኑ እንድናስጠብቅ አባታዊ መልእክታችንን እያስተላለፍን፣ የጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዕለት መከፈቱን እናበሥራለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፤ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/007-3.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32019-10-23 09:39:542025-01-27 09:42:16ጥቅምት 12 ቀን 2012 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to:  38ኛው የሰበካ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ከጥቅምት 5-8 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ Link to:  38ኛው የሰበካ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ከጥቅምት 5-8 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡  38ኛው የሰበካ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ከጥቅምት... Link to: ጥቅምት 13 ቀን 2012 ዓ.ም. በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች በልዩ ልዩ ምክንያቶች ሃይማኖትን፣ ብሔርና ቋንቋን መሠረት ያደረገ የሰው መግደልና የአብያተ ክርስቲያናት አስምልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በፍጹም የሚያወግዘው መሆኑን የተሰጠ መግለጫ በቅዱስነታቸው ተላልፏል፡፡ Link to: ጥቅምት 13 ቀን 2012 ዓ.ም. በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች በልዩ ልዩ ምክንያቶች ሃይማኖትን፣ ብሔርና ቋንቋን መሠረት ያደረገ የሰው መግደልና የአብያተ ክርስቲያናት አስምልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በፍጹም የሚያወግዘው መሆኑን የተሰጠ መግለጫ በቅዱስነታቸው ተላልፏል፡፡ ጥቅምት 13 ቀን 2012 ዓ.ም. በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top