ጥቅምት 12 ቀን 2015 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
ብፁዕ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤
ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ እና በሰሜን አሜሪካ የኒዮርክ እና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤
በአጠቃላይ በዚህ መንፈስ ቅዱሳዊና ሐዋርያዊ ጉባኤ የተገኛችሁ በሙሉ፤
የቤተ ክርስቲያን ራስ የሆነው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አካሉ ስለሆነች ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለመምከርና ለመወያየት ስለ ሰበሰበን ቅዱስ አምላካችን እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፡፡
“ወሑሩ ባሕቱ ኀበ አባግዕ ዘተኀጒላ እምቤተ እስራኤል
ነገር ግን ከቤተ እስራኤል ወገን ወደ ጠቦት በጎች ሂዱ”
ማቴ. 0፥6፡፡
ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በሥጋ ሰብእ እንዲገለጥ ያደረገው ዐቢይ ምክንያት፣ የጠትን በጎች ለመፈለግ እንደሆነ ከሚያስረዱ ትምህርቶች አንዱ ይህ የጌታችን አስተምህሮ ነው፡፡
የጌታችን አገላለጽ ለጊዜው ቤተ እስራኤልን ብቻ የሚመለከት ቢመስልም በዚያ ብቻ ተወስኖ የሚቀር ግን አልነበረም፤ ይህም “ወብየ ካልኣትኒ አባግዕ እለ ኢኮና እምዝንቱ ዐጸድ& ወኪያሆንሂ ሀለወኒ ኣምጽኦን ዝየ& ወይሰምዓኒ ቃልየ& ወይከውና አሐደ መርዔተ ለአሐዱ ኖላዊ፡- ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ& እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል& ድምፄንም ይሰማሉ& አንድም መንጋ ይሆናሉ& እረኛውም አንድ” ብሎ ባስተማረው ትምህርት ይታወቃል፡፡
ከዚህ አንጻር ቤተ ክርስቲያን የቆመች በዚህ ዓለም ለሚገኙ በጎች ሁሉ እንደሆነ እንገነዘባለን& ግልገሎቼን ጠብቅ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ፣ በጎቼን ጠብቅ በማለት በቅዱስ ጴጥሮስ በኩል የነገረንም ይህንን የሚያስረግጥ ነው& እኛም በየጊዜው የምናካሂደው ሐዋርያዊ ሲኖዶስ ይህንን አደራ ለመወጣት ነው፡፡
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!!
ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በረጅሙ ታሪኳ ለሕዝባችንና ለሀገራችን ብዙ መልካም ነገርን አውርሳለች& በአንጻሩ ደግሞ ብዙ የተጋድሎ መከራን ተጋፍጣለች፡፡ በዘመኑ ሁሉ የቤተ ክርስቲያናችን ዙርያ መለስ አካሏ በተቃራኒ ነገር የተከበበ ቢሆንም፣ እጅግ በሚያስገርምና በሚያስደንቅ ሁኔታ ራሷን በመከላከል እስካሁን ዘልቃለች& ይህንን ዓለም ያስደነቀ ታሪኳን የማስጠበቅና የማስቀጠል ኀላፊነት አሁንም በቅዱስ ሲኖዶስና በምእመናኗ ጫንቃ ላይ ያረፈ መሆኑን ልብ ሊባል ይገባል፡፡
ከዚህ አንጻር በአሁኑ ጊዜ በቤተ ክርስቲያናችን ዙሪያ ያሉ አሉታዊ ገጽታዎችን በንቃት ማየት፣ መከታተልና መፍትሔን እያስቀመጡ መሥራት የዚህ ዐቢይ ጉባኤ ኀላፊነት መሆኑ ላፍታም ቢሆን መዘንጋት የለበትም፡ጌታችን “አንሥኡ አዕይንቲክሙ ወነጽሩ በሓውርቲክሙ” ብሎ እንዳስተማረን በውስጥም፣ በውጭም በዙርያ ጥምጥም ሁሉ እየሆነና እየተቃጣ ያለው ፈተና በአጠቃላይ፣ ቤተ ክርስቲያናችንን ሥጋት ላይ እንዳይጥል በጋራም ሆነ በተናጠል በንቃት መከታተል ያስፈልጋል፡፡
ሁሉም እንደሚመሰክረው ቤተ ክርስቲያናችን በሰው ሀብትም ሆነ በምጣኔ ሀብት ባላት ዐቅም በሀገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካ ክፍለ አህጉር ብሎም በኦሪየንታሉና በምሥራቁ ኦርቶዶክስ ጭምር በግምባር ቀደም ወይም በመጀመሪያ የምትቀመጥ ናት፡ይህንንም ደማቅ ታሪክ በዓለም የታሪክ መዝገብ ለማስመዝገብ የበቃችው ቤተ ክርስቲያናችን ባላት የረጅም ጊዜ ታሪክ በምድረ አፍሪካ በተለይም በምሥራቅ አፍሪካ የክርስትና ሃይማኖትን ህላዌ ለማስከበርና ዘላቂ ለማድረግ በፈጸመችው ጠንካራና ውጤታማ ተጋድሎ የተገኘ ነው፡፡
ይህ ለሦስት ሺሕ ዘመናት ተጠብቆ የዘለቀውን የተጋድሎ ደማቅ ስኬት በዙሪያችን ሆነው በአዎንታዊም ይሁን በአሉታዊ እይታ የሚመለከቱ ብዙ ናቸው፡፡ ይህንን ልዩ ሀብታችንና ታሪካችን አደንዛዥ በሚመስል ስልተ ሂደት እንዳንነጠቅ ጠንክረን መሥራት ይገባናል& የቤተ ክርስቲያናችን ሰብኣዊና ቊሳዊ ሀብታችንን አደራጅተን& አቀናጅተንና አዘምነን ለአጠቃላይ የሃይማኖታችን ጥበቃ ማዋል ለነገ የሚባል ተግባር አይደለም፡፡
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
ቤተ ክርስቲያናችን የሃይማኖት፣ የቀኖና፣ የባህልና የሥርዐት እንከን የላትም& በአስተዳደር ስልታችን ግን ገና ብዙ እንደሚቀረን ግልጽ ነው:: በመሆኑም ይህንን እውነት ከልብ ተቀብለን፣ ከዛሬ ጀምሮ ካሁን በፊት ከነበረው ይበልጥ ዛሬ ዘመኑ በሚጠይቀው ጥበብ የሀብታችን ተጠቃሚ ለመሆን፣ የሕዝበ ክርስቲያኑን ጥያቄ ለመመለስ፣ ከሁሉ በላይ ደግሞ የቤተ ክርስቲያናችንን ህልውና በቀጣይነት ዋስትና ባለው ድልድይ ለማሸጋገር በሐቅና በሐቅ በርትተን የምንሠራበት ጊዜ መሆን አለበት፡፡
ታዲያ የምንመኘውና የምናልመው ሁሉ እውን ሊሆን የሚችለው ከላይ ጀምሮ እስከ ታች ባለው የቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር መልካም አስተዳደርን ስናሰፍን እንደሆነ መዘንጋት የለብንም& በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ መልካም አስተዳደር ካልተረጋገጠ እያኮረፈንና እየተወን ከሚሄድ በቀር ፍልሰተ ምእመናንን ማስቆምና ስንዝር የሚያህል እድገትን ማስመዝገብ አንችልም፡፡ ስለዚህ ቀጣዮቹ ዓመታት ቤተ ክርስቲያናችን በሁሉም አቅጣጫ መልካም አስተዳደርን የምታረጋግጥባቸው ዓመታት እንዲሆኑ በመወሰን የማስፈጸም ኀላፊነቱን መውሰድ አለብን፡፡
በሌላ በኩል መልካም አስተዳደር ያለ ፍትሕና ያለ ልማት የትም ሊደርስ አይችልምና ፍትሕ ይሰፍን ዘንድ የመንፈሳዊ ፍርድ ቤት በሀገር ደረጃ ዕውቅና አግኝቶ ሥራ እንዲጀምር ያላሰለሰ ጥረት ብናደርግ፣ የልማትን ጉዳይ በተመለከተም የቤተ ክርስቲያናችንን የሀብት ምንጮች አጥንቶ፣ ለይቶና የትግበራ ሂደታቸውን አመላክቶ የሚያቀርብልን ከፍተኛ ባለሙያዎች ያሉበት ግብረ ኀይል በማቋቋም ወደ ግዙፍ የልማት መርሐ ግብር ብንሸጋገር፣ የምእመናን ጥበቃና አገልግሎትም በተመሳሳይ ሁኔታ ልዩ ስልት እና ጥበብ ተቀምጦለት ምእመናንን በመንፈስ ቅዱስ ኀይል የምንጠብቅበትንና የምናበዛበትን የትኲረት አቅጣጫ ብናስቀምጥ፣ በአጠቃላይ ዳር እስከ ዳር እየተናበብን በመሥራት ፈጣን እድገት የምናስመዘግብበትን ስልት ብንቀይስ፣ እግዚአብሔርና ምእመናን ከቅዱስ ሲኖዶስ የሚሹትን ማሟላት እንችላለን፡፡ ስለሆነም ጉባኤያችን በነኝህ ዙርያ በስፋትና በጥልቀት መክሮበት ወደ ተግባር ቢሸጋገር መልካም ነው እንላለን፡፡
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
ሌላው በዚህ ዐቢይ ጉባኤ ትኲረት ሰጥተን መነጋገር ያለብን የሀገራችንን የሰላም ጉዳይ በተመለከተ ነው& መቼም ቤቱ እየተቃጠለ ዝም ብሎ የሚያይ ሰው ይኖራል ብለን አናስብም& ዛሬ የሁላችን ቤት የሆነች ሀገር በሰላም ዕጦት ከባድ ችግር ውስጥ ናት፡፡
በዚህ አስከፊ ጦርነት ሰውም፣ ንብረትም ቤተ ክርስቲያንም ክኛ እየተጐዱ ነው& እነዚህ ሁሉ የቤተ ክርስቲያናችንና የሀገራችን ምርጥ ቤቶች ናቸው& ቤቶቹ ተቃጥለው ይለቁ ወይስ ምን እናድርግ;ነው ጥያቄው& መልሱ ከቤቱ ቢሆን ምርጫችን ነው& ለማንኛውም ግን ቤተ ክርስቲያናችን ነገ የምትነቀፍበት፣ እኛም የምንገመገምበትና የምንተችበት ታሪክ አስቀምጠን እንዳናልፍ በብርቱ ልናስብበት ይገባል:: ከዚህ አኳያ የሀገራችንን ችግር የመፍትሔ አቅጣጫ በቅንነት፣ በገለልተኝነት፣ በማእከላዊነት እና በአቃፊነት መንፈስና እንደዚሁም፣ ሰላምንና አንድነትን፣ ዕርቅንና ይቅርታን ማእከል ባደረገ መንፈስ ብናየው ለቤተ ክርስቲያንም ለእኛም ይበጃል፡
በመጨረሻም፡ በሀገር ላይ እየተካሄደ ያለው ጦርነትና እሱን ተከትሎ ያንዣበበው የሥጋት ደመና ወደ ባሰ ጥፋት እንዳይወስደን የሀገራችን ችግሮች በሙሉ በሰላማዊ ውይይት ይፈቱ ዘንድ የሚመለከታቸው ሁሉ ያላሰለሰ ጥረት እንዲያደርጉ፣ በጦርነቱም ሆነ በድርቁ ምክንያት በረሀብና በበሽታ እየተጐዱ ላሉ ልጆቻችንም የምግብና የሕክምና አቅርቦት እንዲያገኙ ይደረግ ዘንድ ጥሪያችንን በእግዚአብሔር ስም እያስተላለፍንና ቤተ ክርስቲያንም በዚህ ረገድ የበኩሏን ለማድረግ ዝግጁ መሆኗን እየገለጽን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የጥቅምቱ መደበኛ ጉባኤ በዛሬው ዕለት የተከፈተ መሆኑን ለሕዝበ ክርስቲያኑ እናበሥራለን።
እግዚአብሔር የተባረከና የተቀደሰ ጉባኤ ያድርግልን፤
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ፤
ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፤