ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 23 ቀን 2013 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቍጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልአተ ጉባኤው የመክፈቻው ሥርዐተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከጥቅምት 11 ቀን 2013ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ጥቅምት 23 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ የተለመደውን ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ ሲያካሂድ ሰንብቶ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሚበጁ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ውሳኔዎችን አሳልፎአል፡፡
በዚሁ መሠረት፡-
1. ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የቀረበው የጉባኤ መክፈቻ ንግግር የበጀት ዓመቱ የሥራ መመሪያ ሆኖ እንዲያገለግል ምልአተ ጉባኤው ተቀብሎታል፡፡
2. ለምልአተ ጉባኤው ቀርቦ ውይይት የተካሄደበት የ39ኛው አጠቃላይ የሰበካ ጉባኤ የጋራ መግለጫ ጉባኤው ተቀብሎ ያጸደቀው በመሆኑ ለሚመለከታቸው ሁሉ ተላልፎ በሥራ እንዲተረጐም ተወስኗል፡፡
3. የቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ችግር አስመልክቶ በጉባኤው ሰፊ ውይይት የተደረገበት ሲሆን ባለፈው አንድ ዓመት በሀገራችን በኢትዮጵያ በቤተ ክርስቲያናችንና በክርስቲያን ወገኖቻችን ላይ የደረሰው ግፍና መከራ እንዲቆም በየምክንያቱ በክርስቲያንነታቸው ምክንያት የታሰሩ ካህናትና ምእመናን ጉዳያቸው እየታየ ከታሰሩበት እንዲፈቱ፣ የመንግሥት የበታች ባለሥልጣናትም ለጥፋተኞች ከሚያደርጉት ድጋፍ እጃቸውን እንዲሰበስቡ ጉባኤው አጥብቆ አሳስቧል፡፡ ከዚሁ ጋር በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያን ወገኖቻችን ላይ ባለፈው ለደረሰው ጥፋትና ለወደፊትም የሕግ ክትትል በማድረግ ችግሩን የሚከላከሉ የሕግ ባለሙያዎች ኮሚቴ ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አህጉረ ስብከት ድረስ እንዲቋቋም ተወስኗል፡፡
4. ወቅታዊ ሀገራዊ ሰላምን በተመለከተ ጉባኤው በሰፊው ተነጋግራል፡፡ በሀገራችን ያለው ወቅታዊ የሰላም ዕጦት እየታየ ያለው አለመግባባት ለዜጎች ተረጋግቶ አለመኖርና ለሁከት አልፎ ተርፎ ለሰዎች ሕይወት መጥፋት ምክንያት እየሆነ በመሆኑ በቀጣይም አላስፈላጊ ሁከት ውስጥ እንዳይገባ ከወዲሁ ዕርቅና ሰላም ማምጣት አስፈላጊ መሆኑን ጉባኤው አምኖበታል፡፡ በመሆኑም የዕርቅና የሰላም ሂደቱን የሚያስፈጽሙ ብፁዓን አባቶችን በአስታራቂነት ሰይሟል፡፡
5. በሀገራችን ኢትዮጵያ የሕዝባችን የዘመናት ድህነትና የኑሮ ጒስቍልና አስወግዶ ለሀገራችንም ብልጽግና ሆነ ለሕዝባችን እድገት ከፍተኛ ተስፋ የተጣለበት የታላቁ ሕዳሴ ግድብ አስመልክቶ ጥቅምት 13 ቀን 2013ዓ.ም. የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አካባቢያዊ ጦርነት እንዲነሣ ያስተላለፉት መልእክት ሀገራችን ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት ወይም በሞግዚትነት ለማስተዳደር የተደረገ ሙከራ በመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት ተቃውሞታል፡፡ የዓለምም መንግሥታትና ሕዝቦች እንዲህ ዓይነቱን ትንኮሳ እና የቅኝ ግዛት ፍላጎት እንዲቃወሙ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
6. በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 50 የሚገኘው በአሁኑ ጊዜ ባለው የሀገረ ስብከቱ አሠራር ላይ አመቺ ሆኖ ስለአልተገኘ ከሕገ ቤተ ክርስቲያኑ እንዲወጣ እና የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እንደማንኛውም ሀገረ ስብከት ራሱን ችሎ ሊቀጳጳስ ተመድቦለት እንዲመራ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ ከዚህም ጋር አሁን እየተሠራበት ያለው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ከወቅቱ ጋር ተገናዝቦ መሻሻል እንዳለበት ስለታመነ ይኸው እየተሠራበት ያለው ሕገ ቤተ ክርስቲያን መርምረውና አጥንተው መሻሻል የሚገባቸውን ነጥቦች አሻሽለው ወደፊት በቋሚ ሲኖዶስ ከሚመረጡ ሕግ ባለሙያዎች ጋር ሕጉን አሻሽለው ለግንቦቱ ርክበ ካህናት እንዲያቀርቡ ሦስት ብፁዓን አባቶችን ጉባኤው መድቧል፡፡
7. የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አፈጻጸም አስመልክቶ ቀደም ሲል በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እየተወሰኑ የተፈጸሙና ያልተፈጸሙትን በመለየት ሊፈጸሙ ያልቻሉበት ምክንያት ተገልጾ ለፊታችን ግንቦት ርክበ ካህናት ውጤቱ እንዲቀርብ ጉባኤው መመሪያ ሰጥቷል፡፡
8. የብፁዓን አባቶች የሥራ ምደባና ዝውውር በማስፈለጉ ቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን ሁኔታ ከመረመረ በኋላ በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ ዝውውርና አዲስ የሥራ ምደባም ተካሂዷል፡፡
9. በምሥራቅ ጐጃም ሀገረ ስብከት በቆጋ ኪዳነ ምሕረት ገዳም ተከሥቶ የነበረውን የዶግማና የቀኖና ጥሰት አስመልክቶ ችግሩ በአጣሪ ልኡካን እንዲጣራ ተደርጎ በቀረበ ሪፖርት ላይ ጉባኤው ተነጋግሮ ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ በመንፈስ ቅዱስ ጵጵስና ተሹመናል ያሉት መነኮሳት የፈጸሙት ድርጊት አግባብነት የሌለው ከሕገ ቤተ ክርስቲያን ውጭ ሆኖ ስለተገኘ መነኮሳቱ በራሳቸው የለበሱት ልብሰ ጵጵስናና የጵጵስና ቆብ አውልቀው ንስሓ ተሰጥቷቸው በምንኵስናቸው ብቻ ተወስነው በገዳሙ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን እንዲኖሩ ተወስኗል፡፡ ከዚሁ ጋር ተፈጸመ የተባለው ዳግም ጥምቀትና ክህነት ከቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ውጭ የሆነና ቤተ ክርስቲያናችን የማትቀበለው በመሆኑ ይህን ድርጊት የፈጸሙ ሁሉ ከድርጊታቸው እንዲቈጠቡ ጉባኤው አሳስቧል፡፡
10. የኦሮምያ ቤተ ክህነት አደራጅ ኮሚቴ ነን ከሚሉ አባላት ጋር በተደረገ ውይይት መግባባት ደረጃ ላይ በመደረሱ ክህነታቸው የተያዘ ካህናት ክህነታቸው ተለቆ በቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር ውስጥ የሥራ መደብ ተሰጥቷቸው እንዲያገለግሉ ተወስኗል፡፡
11. የቤተ ክርስቲያኒቱ የ2013ዓ.ም. አጠቃላይ በጀት ላይ የተነጋገረው ምልአተ ጉባኤ ከበጀትና ሂሣብ መምሪያ በቀረበው የበጀት ድልድል ላይ ተነጋግሮ ማስተካከያዎችን በማድረግ በሥራ ላይ እንዲውል አጽድቋል፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ከላይ በተጠቀሱ ነጥቦች እና እንዲሁም በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳይ ላይ በስፋት ተነጋግሯል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች የደረሰው ጐርፍ መጥለቅለቅና የአንበጣ መንጋ በበርካታ ወገኖቻችን ላይ ያደረሰው ችግር ከፍተኛ መሆኑን ጉባኤው ተገንዝቧል፡፡ በመሆኑም ኅብረተሰቡ ለተቸገሩ ወገኖቻችን የተለመደ ድጋፉን ከማድረግ ወደኋላ እንዳይል ምልአተ ጉባኤው ጥሪውን አቅርቧል፡፡ በሀገራችን በኢትዮጵያ በዓለማችንም ጭምር እየታየ ያለው አለመግባባት፣ የጐርፍ መጥለቅለቅ፣ የበሽታ ወረርሽኝ የመሳሰሉት ሁሉ እግዚአብሔር አምላክ በምሕረቱ ተመልክቶ ሰላሙንና አንድነቱን ለዓለማችንና ለሕዝባችን ይሰጥልን ዘንድ ከኅዳር 1-7 2013 ዓ.ም. ድረስ በመላ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትና አድባራት ጸሎተ ምሕላ እንዲደረግ ተወስኗል፡፡
በመጨረሻም፡ ሀገራዊ ሰላምና አንድነት አስመልክቶ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በወሰነው መሠረት የዕርቅ ሂደቱን የሚቀጥልበት ሆኖ ከዚሁ ጋር የፌዴራል መንግሥቱ የየክልል መሪዎች እንዲሁም መላው ኢትዮጵያዊ ሁሉ ለሀገራችን አንድነትና ሰላም ለልማቱና ለሕዝባዊ አንድነቱ በጋራ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን እያቀረበ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ከጥቅምት 11 እስከ 23 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ ለ13 ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን ጉባኤ በጸሎት አጠናቅቋል፡፡
ሰላመ እግዚአብሔር ከሁላችን ጋር ይሁን
እግዚአብሔር ሀገራችንን ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይጠብቅ፡፡