ሚያዝያ 27 ቀን 2005 ዓ.ም የበዓለ ትንሣኤ ሐዋርያዊ መልእክት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ፣ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትኖሩ፣
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
በሕመም ምክንያት በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በማረሚያ ቤት የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፣

በትንሣኤው ትንሣኤያችንን ያበሠረን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለ2005 ዓ.ም በዓለ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ፡፡

“እስመ ሐደሰ ለነ ፍኖተ ጽድቅ ወሕይወት ንቅረብ እንከ በልበ ጽድቅ
የሕይወትና የእውነት መንገድን አድሶልናልና ከእንግዲህ በቅን ልቡና ወደ እርሱ እንቅረብ።”
(ዕብ. 1ዐ፣19)

የሰው ልጅ ለማያረጅና ለማያልፍ ሕይወት የታደለ፣ በእግዚአብሔር አምሳልና አርኣያ የተፈጠረ፣ እጅግ ክቡርና ታላቅ ፍጥረት እንደነበረ ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፤ በምድር በሚገኙ ፍጥረታት ሁሉ ላይ ያለው የበላይነት ሥልጣንም ይህንን ያረጋግጣል፡፡ የሰው ልጅ በእግዚአብሔር ዘንድ ይህን ያህል ጸጋ ቢኖረውም የተሰጠውን ክብርና ልዕልና በአግባቡ ጠብቆ መዝለቅ አልቻለም፤ በእግዚአብሔር ፊት በፈጸመው ከባድ በደል ምክንያት የተሰጠውን ጸጋና ክብር ከማጣቱም በላይ በሕይወት ፈንታ ሞትን፣ በእውነት ፈንታ ሐሰትን፣ በዘለዓለማዊነት ፈንታ ጊዜያዊነትን፣ በማያረጀው ፈንታ የሚያረጀውን ሕይወት ተላብሶ ወደ ምድረ ፍዳ ተባረረ፤ ከእግዚአብሔር ልጅነት ተራቈተ፣ ከማኅበረ መላእክት ተለየ፤ ረዳት የለሽና ጎስቋላ ሕይወት ተሸክሞ መኖር ጀመረ ፡፡

ለእርሱ ያልተፈጠሩ የሞትና የመቃብር ጎዳናዎች እስከ ስቅለተ ክርስቶስ ድረስ በሰፊው ተጓዘባቸው፡፡ ከክርስቶስ በፊት የነበሩ በሺሕ የሚቀጠሩ ዓመታት ለሰው ልጅ የፍዳ፡ የመርገም፣ የከነኔ ዓመታት ነበሩ፤ ሲኦልና ገሃነም የሰው ዘርን በአጠቃላይ ለመዋጥ አፋቸውን የከፈቱበትና ሰውን ሁሉ በመራራ ሥቃይ የማገዱበት፣ ገነትና መንግሥተ ሰማያት አንድ ስንኳ ለእነርሱ የተገባ ፍጡር የሌለ እስኪመስሉ ድረስ ባዶአቸውን ተዘግተው የነበሩበት መራራ ጊዜ ነበር፡፡ እግዚአብሔር እውነተኛ ዳኛ እንደመሆኑ መጠን በሰው በደል ምክንያት ትክክለኛ ፍርዱን ቢያስተላልፍም ከፈራጅነቱ ጎን ለጎን መሓሪነቱን የማያርቅ ለፍጥረቱ እጅግ ርህሩህ ነውና በሰው ላይ የተላለፈው የሞተ ነፍስ ፍርድ በልጁ በጌታችን በአምላካችንና በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መሥዋትነት እንዲያከትም አደረገ፤ የተዘጋው የገነት በር እንዲከፈት፣ በሲኦል የተጋዙ ነፍሳት ወደ ገነት እንዲመለሱ፣ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ የሰው ጒዞ ወደ ሲኦል መሆኑ ቀርቶ ወደ ገነት እንዲሆን በማድረግ ሰውን በክርስቶስ ደም ታረቀው ፡፡

በዚህ ታላቅ መሥዋዕትነት ያረጀውን የሲኦል መንገድ ዘግቶ አዲስ የገነት መንገድን ስለከፈተልን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አዲስ የእውነትና የሕይወት መንገድ ከፍቶልናልና ከእንግዲህ ወዲህ በቅን ልቡና ወደርሱ እንቅረብ እንዳለ በፍጹም ልባችን፣ በፍጹም ሐሳባችን፣ በፍጹም ኀይላችን ወደ እርሱ ልንቀርብ ይገባል ፡፡

ያረጀው ነገር ሁሉ በክርስቶስ ደም ተቀድሶና ነጽቶ ሐዲስ ሆኖአል፤ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሠርቶ የሚያሠራ የመልካም ነገር ሁሉ አርኣያና መሪ እንደመሆኑ መጠን አዲሱን መንገድ ከፍቶ እንድንጓዝበት ሲያደርግ እኛም በሐዲስ መንፈስ በአዲስ ሕይወት ልንመላለስበት እንጂ እንደገና ወደ አደራጀውና ወደአፈጀው ሕይወት ተመልሰን ልንዘፈቅ አይደለም ፡፡ አዲስ ሕይወት ማለት እግዚአብሔር ለሰው ዘር ሁሉ መድኀኒት እንዲሆን በላከው በመድኀኒችን በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የዘለዓለም ድኅነትን ማግኘት ነው፤ ምንም ዐይነት አማራጭ የማይገኝለት ይህ የእግዚአብሔር የማዳን ጸጋን የሰው ዘር ሁሉ ተቀዳሚ ሥራው አድርጎ ሊቀበለው ይገባል፤ በዚህ በኩል ካልሆነ ቢቀር ሌላ የምንድንበት መንገድ የምናመልጥበት ዓውድ ፈጽሞ የለምና፡፡

የክርስትና ሃይማኖት በቅዱሳት መጻሕፍት በግልጽ እንደተቀመጠው በመልካም ሥነ ምግባር ገዝፎ የሚታይ ሃይማኖት እንጂ በእምነት ብቻ ተደብቆ የሚኖር ሃይማኖት አይደለም፤ በርቀት ያለችው ነፍሳችን በግዙፉ የሥጋ አካላችን ውስጥ ሆና በምትሠራው ሥራ አማካይነት በአካላችን ውስጥ አንዳለች እንደምናውቅ ሁሉ አንድ ክርስቲያንም መልካም ሥራን አብዝቶ ሲሠራ በሥራ ገላጭነት ሃይማኖቱ ገዝፎ በጒልህ ይታያል፤ በመሆኑም በክርስትና ሕይወት ሃይማኖትና ሥነ ምግባር እንደነፍስና እንደሥጋ ተዋሕደው በአንድነት ሲኖሩ ሕይወተ ነፍስን እንደሚያጎናጽፉ ልብ ብሎ ማስተዋል ይገባል፡፡ ከክርስትና ሃይማኖት አስተምህሮ በሚመነጨው መርሕ መሠረት በሥራ በመትጋትና በፍጹም ፍቅር በመኖር ሕይወታችንን ይበልጥ ልናሳድገው ይገባል፤ ከሁሉ በፊት ሰው የተፈጠረው ለሥራና ለክብር እንደሆነ ከቶ ልንዘነጋው አይገባም፤ ይህም ከሆነ ሰው ለአንዲት ደቂቃ ያህል እንኳ እጅ እግርን አጣጥፎ ያለሥራ ሊቀመጥ እግዚአብሔር አልፈቀደም አይፈቅድምም፡፡ “ወበሐፈ ገጽከ ብላዕ ኅብስተከ — ወደ ወጣህባት መሬት እስክትመለስ ድረስ ጥረህ ግረህ ላብህን አንጠፍጥፈህ ብላ” ነውና ይላል (ዘፍ. 3፥19)፡፡ በዙሪያችንም ሆነ በሌላው አካባቢ የተሻለ ኑሮና ክብር ያላቸው ሆነው የሚታዩ ሁሉ የመክበራቸው ምሥጢር ጠንክረው መሥራታቸው እንደሆነ በውል ልናጤነው ይገባል፡፡

እኛ ኢትዮጵያውያንም በታላቁ የሕዳሴ ግድባችን እንደሚታየው ሃያ አራት ሰዓት ሙሉ በትጋት ከሠራን በአጭር ጊዜ ሌሎች የበለጸጉ ሀገሮች ከደረሱበት የእድገት ደረጃ የማንደርስበት ምክንያት አይኖርም፤ ዋናው ቁም ነገር ሁላችንም ኢትዮጵያውያን በኅብረት፣ በአንድነት፣ በስምምነት፣ በመተማመን፣ በመቻቻል ለሥራና ለሥራ ብቻ መነሣቱ ላይ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ደግሞ በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን በጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የምናየው ስለሆነ ለምንጣደፍለት የእድገት ሸግግር ትልቅ መሣሪያችን መሆኑን አውቀን እንደ ዐይን ብሌን ልንጠብቀው ይገባል፤ ይህ የሆነ እንደሆነ የሕዳሴውን ግድብ ጨምሮ በሀገራችን የተጀመሩትን ታላላቅ ሥራዎች ሁሉ ያለጥርጥር ማሳካት እንችላለን፡፡ የእውነትና የሕይወት መንገድ አድሶልናል የሚለውን የፋሲካ ትምህርተ ሃይማኖት የሕዳሴውን ልማት በማፋጠንና በማሳካት ልንገልጸው ይገባል፡፡

በሌላ በኩል ታላቁን የፋሲካ በዓላችንን ስናከብር ለእኛ ብሎ፣ በእኛ ፈንታ መሥዋዕት ሆኖ የዘለዓለም ሕይወትን ካጎናጸፈን ጌታ ጋር ማክበር አለብን፤ ፋሲካን ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ማክበር የምንችለው የተራቡትን በመመገብ፣ የተጠሙትን በማጠጣት፣ የታረዙትን በማልበስ፣ የታመሙትንና የታሠሩትን በመጠየቅ፣ እንግዶችን ተቀብሎ በማስተናገድ ነው፡፡ ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያኑ ከሃይማኖቱ፣ ከተቀደሰ ሥነ ምግባሩና ባህሉ በወረሰው ሥርዐት መሠረት እንደተለመደው በዓሉን በሰላም፣ በፍቅር፣ በስምምነትና በመረዳዳት፣ ድሆችን ይዞ በመመገብ በመንፈሳዊ ደስታ እንዲያከብር መንፈሳዊ መልእክታችንንና ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡ የተቀደሰና የተባረከ የፋሲካ በዓል ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር ሀገራችንንና ሕዝባችንን ይባርክ አሜን።