• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

ሚያዝያ 23 ቀን 2008 ዓ.ም. የትንሣኤ በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

ሞትንና መቃብርን ድል አድርጎ የተነሣው፣ የሕይወት ራስና የሁሉ ፈጣሪ የሆነው፣ ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለሁለት ሺሕ ስምንት ዓመተ ምሕረት በዓለ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ!!

‹‹ዓይቴ እንከ ቀኖትከ ሞት፤ ወዓይቴ እንከ መዊዖትከ ሲኦል
ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ? ሲኦል ሆይ ድል መንሣትህ የት አለ?››
(1ቆሮ. 15፥55)

ሞትና መቃብር የኀጢአትና የበደል ውጤቶች እንጂ የተፈጥሮ ዕድል ፈንታ ሆነው ለሰው የተሰጡ አይደሉም ፡፡ ሰው በራሱ ምርጫ ካልሆነ በቀር የሚሞት ሆኖ እንዳልተፈጠረ ቅዱስ መጽሐፍ ሲገልጽ “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን እንዲህ ብሎ አዘዘው ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህ” ይላል፤ (ዘፍ. 2፥16-17)፡፡ ሔዋንም የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መሠረት አድርጋ ስትናገር፣ ‹‹እግዚአብሔር እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ፣ አትንኩትም›› ብሎናል ብላ አረጋግጣለች፤ (ዘፍ. 3፥3)፡፡

ከዚህ አምላካዊ ቃል መረዳት እንደሚቻለው አዳም አትብላ የተባለውን ዛፍ ባይበላ ኖሮ አይሞትም ነበር ማለት ነው፤ ከዚህ አንጻር የሞትና የመቃብር ምንጩ ሕገ ተፈጥሮ ሳይሆን ግብረ ኀጢአት ሆኖ እናገኘዋለን ፡፡ በመሠረቱ ግብረ ኀጢአት የሚመነጨው ለእግዚአብሔር ካለመታዘዝ እንደሆነ ከዚህ መረዳት እንችላለን፤ ምክንያቱም አዳምና ሔዋን ሁለት ምርጫዎች ቀርበውላቸዋል፤ ማለትም በአንድ በኩል ‹‹መልካምና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብሉ፤ ከበላችሁ ግን ትሞታላችሁ›› የሚል የእግዚአብሔር ትእዛዝ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ‹‹ብትበሉ ሞትን አትሞቱም፤ ነገር ግን ከዛፉ በበላችሁ ቀን ዐይኖቻችሁ ይከፈታሉ፤ እንደ እግዚአብሔርም መልካምንና ክፉን የምታውቁ ትሆናላችሁ›› የሚል የእባብ ወይም የሰይጣን ምክር ቀርቦላቸዋል ፡፡ በዚህ ጊዜ አዳምና ሔዋን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ገሸሽ በማድረግ የእባቡን ምክር ተቀብለው ዛፉን በሉ፤ በዚህም ከባድ በደልን ፈጸሙ፡፡ አዳምና ሔዋን በዚህ ድርጊታቸው የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ተላልፈዋል፤ ምክንያቱም የእርሱን ትእዛዝ ትተው የእባቡን ምክር መቀበል እግዚአብሔርን ትእዛዝ ማቃለል እንደሆነ ግልጽ ነውና ፡፡ ኀጢአትን ወልዶ፣ ለልጅ ልጅ የሚተርፍ ከባድ የሞትና የመቃብር ቅጣትን ያስፈረደ በደል፣ ይህ ለእግዚአብሔር ያለመታዘዝና የተሳሳተ ምርጫ ነው፤ የሞት ቅጣቱ ድሮውም ከዛፉ በበላህ ቀን ትሞታለህ ተብሎ በግልጽ የተነገረ ስለነበረ አዳም ዛፉን በበላ ቀን ቅጣቱ ወዲያውኑ ተግባራዊ ሆኖአል፤ ማለትም አዳም ‹‹ዛፉን እንደበላ ወዲያውኑ ራቁቱን ወጥቶአል›› በመራቆቱም ከእውነተኛው ልብስ ከእግዚአብሔርና ከጸጋዎቹ መለየቱ በዚህ ተረጋግጦአል፤ ሞት ማለት መለየት ማለት ነውና፡፡

በአዳም ላይ የተፈረደው ሞት ብቻ ሳይሆን ‹‹አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ›› ተብሎም በሞት ላይ ርደተ መቃብርን ተፈርዶበታል (ዘፍ. 3፥19)፤ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ሰው ከእግዚአብሔር በመለየቱ ሞትና መቃብር ተረክበውታል ፡፡ በይቀጥላልም ሰው ለእግዚአብሔር ያለመታዘዝ ልምዱን አጠናክሮ ሲቀጥልበት፣ ዲያብሎስም በኀጢአት ጦር ሰውን እየወጋ ሲገድል፣ መቃብርም ሙታንን እየተቀበለ ሲማግድ አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመታት አለፉ፡፡ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር ከመዓቱ አንጻር ምሕረቱን አያርቅምና በዲያብሎስ ምክር ድል ሆኖ የተሸነፈውን ሰው የሚታደግና ዲያብሎስን ድል የሚያደርግ ብርቱና ኀያል ዘር ከጊዜ በኋላ ከሴት እንደሚወለድ በመግለጽ ወዲያውኑ ተስፋ ድኅነትን ሰጥቶአል (ዘፍ. 3፥15)፤ ይህ ዘር የጠላት ዲያብሎስን ደጅ በድል አድራጊነት እንደሚወርስ “ዘርህ የጠላትን ደጅ ይወርሳል” ተብሎ፣ የምድር አሕዛብ ሁሉ በዚህ ዘር እንደሚባረኩና እንደሚድኑ ‹‹በዘርህ የምድር አሕዛብ ሁሉ ይባረካሉ›› ተብሎ በትንቢት እየተብራራ፣ እየተገለጸና እየተነገረ ቆይቶአል፤ (ዘፍ. 22፡17)፡፡ ይህ ድል አድራጊ ዘር እንደ ትንቢቱ ቃል ከሴት ማለትም ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ በዚህ ዓለም ተገለጸ፤ ቅዱስ ወንጌልን እያስተማረ በዚህ ዓለም በተመላለሰ ጊዜም፡- ሕሙማን በመፈወስ፣ ዕዉራንን በማብራት፣ ለምጻሞችን በማንጻት፣ ሓንካሳንን በማቅናት አዳኝነቱን አስረዳ፡፡

በፈጣሪ ሥልጣን ካልሆነ በቀር በፍጡር ሊደረጉ የማይችሉና ከአእምሮ በላይ የሆኑትን ዐበይት ተኣምራት በማድረግ ሁሉን የሚችል አምላክ መሆኑን አሳየ፡፡ ዲያብሎስ በጾሙ ወቅት ያቀረበበትን ፈተና በመበጣጠስ፣ እንደዚሁም አንተ ሰይጣን፣ ከእርሱ ውጣ!! እያለ ከሰዎች በማስወጣት፣ ኀጢአትህ ተሰርዮልሃል እያለ ኀጢአትን በማስወገድ ሥልጣነ መለኮቱን ገሐድ አደረገ፤ ‹‹አልዓዛር አልዓዛር ና ውጣ ከመቃብር›› እያለ ሙታንን በማስነሣት በሞትና በመቃብር ላይ ሥልጣን ያለው መንሥኤ ሙታን መሆኑንም በተግባር አረጋገጠ፤ በአጠቃላይ በኀጢአት፣ በዲያብሎስ፣ በሞትና በመቃብር ላይ ሙሉ ሥልጣን ያለው ድል አድራጊ ዘር መሆኑን በተጨባጭ አሳየ፡፡ የማስተማር ጊዜውን ካጠናቀቀ በኋላ፣ በሰው ፈንታ ተሰቅሎ፣ ሞቶና ተቀብሮ ስለ ሰው ኀጢአት መሥዋዕት በመክፈል አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዘመን ሙሉ በሲኦል የነበሩትን ነፍሳት ወደጥንተ ቦታቸው ወደ ገነት መልሶ አስገባ (1ኛ ጴጥ. 3፥18-19፣ ሉቃ. 23፡43)፡፡ እርሱም በተቀበረ በሦስተኛው ቀን መቃብር ክፈቱልኝ፣ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል በራሱ መለኮታዊ ሥልጣን ተነሣ፤ በዚህ ጊዜ የሰው መውጊያ የሆነው ሞት ተሻረ፤ ተሸነፈ፤ ኀጢአት ጠፋ፣ መቃብርም ድል ሆኖ ባዶውን ቀረ፡፡ በጌታችን ትንሣኤ የተበሠረው የሞት መሸነፍና የመቃብር ድል መሆን፣ በዳግም ምጽአተ ክርስቶስ ለሰው ዘር ሁሉ እውን ይሆናል፤ ያን ጊዜ ሞትና መቃብር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ህልውናቸውን አጥተው ያከትማሉ፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ ለሰው ሁሉ ትንሣኤ በኵር ሆኖ ተፈጽሞአል፤ በመሆኑም የትንሣኤን በዓል ስናከብር ‹‹ክርስቶስ ተነሣ›› ብለን የምሥራች በመናገር ብቻ ሳይሆን እኛም እርሱ በተነሣው አኳኋን እንነሣለን እያልን ተስፋ ትንሣኤያችንን በማብሠርና በማስተጋባት ጭምር ሊሆን ይገባል፤ የእኛ ትንሣኤ በክርስቶስ ተጀምሮ አሁን በሂደት ላይ ያለ ሲሆን፣ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግመኛ ተመልሶ ሲመጣ የሁላችን ትንሣኤ እውን ይሆናል፤ የሰው የመጨረሻ ዕድሉ ሞት ሳይሆን ትንሣኤ መሆኑንም በዚያን ጊዜ ይረጋገጣል ፡፡ በዚህም ሰው በእግዚአብሔር መልክና አምሳል የተፈጠረ ታላቅ ፍጡር እንደመሆኑ መጠን ለዘለቄታው ተሸናፊ ሳይሆን በአምላኩ ቸርነት በመጨረሻ አሸናፊ እንደሆነ መገንዘብ እንችላለን፡፡

ዛሬም ቢሆን የሰው አሸናፊነት በመንፈሳዊም ሆነ በሥጋዊ ሕይወቱ በግልጽ የሚታይ ነው ይኸውም፡-
በሥጋዊ ሕይወቱ በኩል ከጥንት ጀምሮ በተፈጥሮ ሀብት ላይ በሚያደርገው የምርምርና የተግባር ጥረት ከጊዜ ወደጊዜ እያደገና ድል በድል እየተጓዘ ዛሬ ለደረሰበት የቴክኖሎጂ ብልጽግና በቅቶአል፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወቱ በኩልም ከአምልኮ ጣዖት ተላቆ በአንድ እውነተኛ አምላክ በማመንና ከእርሱ ጋር ግንኙነት በማድረግ በሞራል፣ በሥነ ምግባርና በሃይማኖት የበለጸገ ማኅበረ ሰብ በዓለም እንዲኖር አስችሎአል፡፡
ስለሆነም ዲያብሎስን፣ ኀጢአትን፣ ሞትንና መቃብርን የሚያሸንፉ መስተጋድላንና መዋእያን ቅዱሳን በብዛት እንዲገኙ አድርጎአል፤ አሁንም በዓለም ዙሪያ ሁሉ ስፍር ቊጥር የሌላቸው መንፈሳውያን አርበኞችና ድል አድራጊዎች አሉ፤ ባለፈው ዓመት በሊቢያ የተሠዉ ልጆቻችን በዚህ መንፈሳዊ አርበኝነት የቅድስና ድልን የተጎናጸፉ ተጠቃሽ ሰማዕታት ናቸው፡፡ የምንኖርባት ዓለም የትግል ሜዳ ናት፤ የዕለት ተዕለት ኑሮአችን ሁሉ በትግል የተሞላ በመሆኑ በሥጋዊም ሆነ በመንፈሳዊ ኑሮአችን ከትግሉ ማምለጥ አንችልም፤ እውነቱ ይህ ከሆነ የሚያዋጣው ከትግሉ መሸሽ ሳይሆን ታግሎ ማሸነፍ ነው፡፡ የጌታችን ነገረ መስቀልም የሚያስተምረን “ዘይፈቅድ ይፀመደኒ ያጥብዕ ወይንሣእ መስቀለ ሞቱ ወይትልወኒ፤ ወዘኢጾረ መስቀለ ሞትየ ኢይክል ይፀመደኒ ወኢይደሉ ሊተ፤ ሊከተለኝ የሚወድ መስቀለ ሞቱን ይዞ በቈራጥነት ይከተለኝ፤ መስቀለ ሞቴን ተሸክሞ የማይከተለኝ ሊያገለግለኝም የኔ ሊሆንም አይችልም” እያለ ነው (ማቴ. 10፥38)፡፡ በዚህ ክርስቶሳዊ የተጋድሎ ጥሪ ቅዱሳን ሐዋርያትና ቅዱሳን ሰማዕታት በአጠቃላይም ክርስቲያኖች ሁሉ ወደትግሉ ሜዳ ተቀላቅለውና በድል አድራጊነት ግዳጃቸውን ተወጥተው ለቅዱሳን አንድ ጊዜ የተሰጠች ሃይማኖትን አስረክበውናል፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀሉ፣ ዲያብሎስንና ኀጢአትን፣ በትንሣኤው ሞትንና መቃብርን ድል አድርጎ እንደተነሣ፣ የእርሱ ተከታዮች የሆኑ ቅዱሳን ክርስቲያኖችም በዚያው ፍኖተ መስቀል እየተጓዙና ድልን እየተቀዳጁ ከኛ ዘንድ ያደረሱትን ሃይማኖታዊ ተልእኮ በተለመደው መንፈሳዊ ትግል በመጠበቅ፣ ለቀጣዩ ትውልድ ማስረከብ የእኛ ፈንታ ነው፡፡ የሃይማኖት ትግል በየወቅቱ የሚለዋወጥ ከሚሆን በቀር የሚቆም አይደለም፤ የዘመናችን ትልቁ የሃይማኖት ተግዳሮት ቴረሪዝም፣ ሴኩላሪዝምና ግሎባላይዜሽን በማንነትና በሃይማኖት ህልውና ላይ እየፈጠሩት ያለ ከባድ ጫና ነው፤ ሕዝበ ክርስቲያኑ፣ በአጠቃላይም በሀልዎተ እግዚአብሔር የሚያምኑ ሁሉ ሃይማኖትና ዕሴቶቹ የፈጠሯቸው የማንነት ጸጋዎችን አጽንተው በመያዝ ካልመከቱ በቀር የሴኩላሪዝምና የግሎባላይዜሽን ፈተና ቀላል አይሆንም፡፡ ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያኑ በዚህ ረገድ ማለትም ሃይማኖቱንና ከሃይማኖት የተወረሱ ዕሴቶቹን፣ እንደዚሁም የተቀደሰ ባህሉን እየጠበቀ ለሃይማኖቱና ለማንነቱ እንዲቆም ቤተ ክርስቲያን አጥብቃ ትመክራለች፣ ታስተምራለችም፡፡ እኛ ክርስቲያኖች በሱባዔው ወቅት በጾም፣ በጸሎት፣ በምጽዋት፣ በንስሓ፣ በቅዱስ ቊርባን ፍቅርንና ሰላምን ገንዘብ በማድረግ ዲያብሎስንና ኀጢአትን ስንታገላቸው እንደቆየን ሁሉ፣ አሁንም በበዓለ ፋሲካው ቀን ጧሪ የሌላቸውን አረጋውያን፣ አሳዳጊ የሌላቸውን ሕፃናት፣ በድርቅ የተጎዱትን ወገኖች በተለይም በአሁኑ ወቅት የግድያና የአፈና ሰቆቃ ደርሶባቸው በኀዘንና በችግር ላይ የሚገኙት የጋምቤላ ብሔረ ሰብ ልጆቻችንና ወገኖቻችን በሁሉም ነገር ከጎናቸው ሆነን በማገዝ፣ በመመገብ፣ በማጠጣትና በማልበስ፣ በሽተኞችን በመጠየቅና በመርዳት ፍጹም የደስታና የድል ቀን አድርገን ማክበር ይገባናል፤ በዚህ መልካም ሥራችንም የትንሣኤ ልጆች መሆናችንን ማስመስከር ይኖርብናል ፡፡

በመጨረሻም፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ በዓለ ትንሣኤን ሲያከብር ማስታወስ ያለበት የክርስቶስን አሸናፊነት ነው፤ በአንጻሩ ደግሞ የክርስቶስ ተከታዮች የሆኑ ሁሉ አሸናፊዎች መሆን ይጠበቅባቸዋል፤ አሸናፊነታቸውም በሃይማኖትና በልማት ላይ የተመሠረተ መሆን ይኖርበታል፡፡ በመሆኑም የሀገራችን ሕዝቦች በአጠቃላይ በድህነት ላይ የጀመሩትን ትግል በድል ማጠናቀቅ ይችሉ ዘንድ ሰላማቸውንና አንድነታቸውን በመጠበቅ የሀገራችንን ሕዳሴ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪያችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን ፡፡

መልካም የትንሣኤ በዓል ያድርግልን እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፣ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡አሜን!

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32016-05-01 13:02:582025-01-28 13:04:03ሚያዝያ 23 ቀን 2008 ዓ.ም. የትንሣኤ በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ሚያዝያ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. በጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ውስጥ በንጹሓን ወገኖቻችን ላይ የደረሰው አሠቃቂ ግፍ Link to: ሚያዝያ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. በጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ውስጥ በንጹሓን ወገኖቻችን ላይ የደረሰው አሠቃቂ ግፍ ሚያዝያ 12 ቀን 2008 ዓ.ም. በጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ... Link to: ግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top