• Amharic  
  • English  
  • ቀዳሚ ገጽ
  • የኢ/ኦ/ተ/ቤ
    • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
    • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • ልዩ ጽ/ቤት
    • የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት
    • የቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች
    • የሀገር ውስጥ ሐዋርያዊ አገልግሎቶች
    • የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
  • ቃለ በረከት
  • ዜና መዋእል
  • አርዕስተ ሊቃነ ጳጳሳት
  • ያግኙን
  • Menu Menu

መጋቢት 13 ቀን 2012 ዓ.ም የደብረ ዘይት በዓል መልእክት የሚከተለው ነው

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ከሚመጣው ቊጣ ማምለጥ ትችሉ ዘንድ በጾም፣ በጸሎትና ለእግዚአብሔር በመታዘዝ ቀን ከሌሊት እየተጋችሁ የምትገኙ በሀገር ውስጥና በመላው ዓለም ዙሪያ ያላችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤ በጾምና በኀይለ መንፈስ ዲያብሎስን ድል አድርጎ የድል መንገድን ያስተማረን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለበዓለ ደብረ ዘይት በሰላም አደረሰን፤ አደረሳችሁ!!

‹‹ናሁ ተዐውቀ ከመ ሀለወነ ኵልነ ንትሐተት በኀበ እግዚአብሔር፤
በእግዚአብሔር ዘንድ ሁላችንም እንደምንጠየቅ እነሆ ታወቀ።››
(ሮሜ. 14፥12)

የነገሥታት ንጉሥ፣ የመሪዎች መሪ፣ የዳኞች ሁሉ የበላይ ዳኛ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመጨረሻውን የዳኝነት ፍርድ ለመስጠት ዳግመኛ እንደሚመጣ የብሉይ ኪዳንና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ደጋግመው ይነግሩናል፤ በተለይም ደብረ ዘይት ተብሎ በሚጠራው ቅዱስ ተራራ ላይ ሆኖ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ዳግም ምጽአቱ በዝርዝርና በስፋት ማስተማሩን ክርስቲያኖች የሆን ሁላችን በውል የምናውቀው ነው፤ ጌታችን በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ሆኖ እንዳስተማረን የዳግም ምጽአቱ መቃረብ ምልክቶች ፍቅር ቀዝቅዞ ጥላቻ እንደሚስፋፋ፣ በርካታ የጦርነት ወሬዎች እንደሚሰሙ፣ ረኃብና ቸነፈር እንደሚከሠት፣ ብዙ ሐሰተኞች ክርስቲያኖች ተነሥተው እውነተኞች የሆኑ ክርስቲያኖችን እንደሚያሳስቱ፣ እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ የሚናገሩ ሐሰተኞች ነቢያት እንደሚነሡና በአጠቃላይ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ሆኖ የማያውቅ መከራ እንደሚከሠት አስተምሮናል፤ ይሁን እንጂ ትዕግሥትን አጽንቶ የያዘ ሁሉ እንደሚድን ግልጽ አድርጎአል፤ መከራው ካለፈ በኋላ መብረቅ በምሥራቅ ሲወጣ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ፣ የእርሱ አመጣጥም በዓለም ውስጥ ያሉ በሙሉ እያዩት በግልጽ እንደሚመጣ እንጂ በእልፍኝ ወይም በድብብቆሽ እንደማይመጣ በመግለጽ፣ ክርስቶስ እዚያ አለ፤ ኢየሱስ እዚህ አለ ኑ ወደኛ የሚሉትን እንዳንሰማና እንዳንከተልም አስጠንቅቆናል፤ በመሆኑም ቃሉን በምልአት በመቀበል በእምነትና በዕውቀት ላይ በተመሠረተ መንፈሳዊ አስተውሎት በመከታተል በጊዜያችን እየሆነ ያለውን ሁሉ ልንገነዘበው ይገባል፤ ከጥንቃቄ ጒድለት የተነሣ፣ ከስሕተት ከግድየለሽነትና ከክሕደት እንዳንወድቅም መጠንቀቅ ይኖርብናል ፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤

ዳግም ምጽአቱን በማመን፣ ምን ጊዜም በሥነ ምግባርና በሃይማኖት ጸንቶ መኖር የሃይማኖታችን ቀዋሚ አስተምህሮ ነው፤ ጌታችን ዳግመኛ ይመጣል ሲባል ለምን ጉዳይ እንደሚመጣ በሚገባ ማወቅና ቅድመ ዝግጅት ማድረግም ከነፍስ ወከፍ ክርስቲያን ይጠበቃል፤ ጌታችን ዳግመኛ ወደዚህ ዓለም የሚመጣበት ዋናው ምክንያት እውነተኛውንና የመጨረሻውን ፍርድ ለሰው ልጆች ለመስጠት ነው፤ የዳኝነቱ መሠረትም በዚህ ዓለም በሕይወተ ሥጋ ሳለን የሠራነው ሥራ ነው፤ ዳኛው ፊትን አይቶ የማያፍር፣ የማይፈራ፣ የማያዳላና ሚዛንን የማያዛባ ነውና በዚህ ዓለም በሕይወተ ሥጋ ሳለን የሠራናትን ያችንኑ እንደ ሥራችን ያስረክበናል፤ ይህ ዳኝነት ይግባኝ የሌለበት፣ ሙግትና ክርክር የማይካሄድበት፣ ምስክርና ማስረጃ አለኝ የማይባልበት ፍርድ ቤት ነው፤ ወደዚህ ፍርድ ቤት የማይቀርብና የማይጠየቅ ሰውም የለም አይኖርምም፤ ተሸፋፍኖ፣ ተደባብቆና ተሽለኩልኮ ማምለጥም አይቻልም፤ የሰው ልጆች የሆን ሁላችን ያለን ብቸኛ አዋጪ ስልት በዚህ ዓለም በሕይወተ ሥጋ ስንኖር በሃይማኖትና በሥነ ምግባር ጸንተን መኖር ብቻ ነው፤ የፈጸምነው ስሕተት ሲኖርም በንስሓ እንዲሠረዝ በማድረግ መንፈሳዊ ሕይወትን ጠብቀን ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነትን አጽንተን መኖር ነው፡፡

ክርስቶስ አምላካችን ወደዚህ ዓለም ዳግመኛ ሲመጣ በሠራነው ሥራ መጠን ፍዳ ወይም ዋጋ እንደሚጠብቀን ተገንዝበን ከፍዳ የምናመልጥበትንና ዋጋ የምናገኝበትን ሥራ መሥራት ከጥበብ ሁሉ የበለጠ ጥበብ ነው ፡፡ ከዚህ አኳያ በልዩ ትኵረት ልንከታተላቸው፣ እንደዐይን ብሌንም ልንጠብቃቸው የሚገቡ ነገሮች ሁለት ዐበይት ነገሮች እንዳሉ ጌታችን አስተምሮናል፡፡ እነሱም (1ኛ) አንደኛው እግዚአብሔርን በሁለመናችን መውደድ ሲሆን፤ (2ኛ) ሁለተኛው ደግሞ ባልንጀራችንን እንደነፍሳችን መውደድ ናቸው፤ እነዚህ የፍጹም ፍቅር ሕግጋትን በአግባቡ ከጠበቅን ኀጢአት መግቢያ አይኖረውም፤ ምክንያቱም እግዚአብሔርን ከልብ የምንወድ ከሆነ እንደፈቃዱ መኖር የሚከብድ አይሆንም፤ ሰውንም እንደነፍሳችን የምንወድ ከሆነ ለሰው መልካም ነገርን መሥራት የሚከብድ አይሆንም፤ በተወሰነ ደረጃ ብንሳሳት እንኳ ሥር የሰደደ የኀጢአት ልምድና ሱስ አይኖረንምና በፍጥነት ንስሓ ገብተን በፍቅረ እግዚአብሔርና በፍቅረ ቢጽ ጸንተን መቀጠል እንችላለን፡፡

ዛሬ በዓለም እየተከሠቱ ያሉ ችግሮች ሁሉ የፍቅረ እግዚአብሔርና የፍቅረ ቢጽ እጥረቶች ያስገኙአቸው መዘዞች እንደሆኑ ምንም ጥርጥር የለንም፤ የዘመናችን ትውልድ እግዚአብሔርን ከልብ የሚያምን፣ የሚፈራና ለእሱ ለመታዘዝ ዝግጁ ቢሆን ኖሮ፣ ሰውንም እንደራሱ አድርጎ የሚወድ ቢሆን ኖሮ መሳሳቡ፣ መጨካከኑ፣ ራስ ወዳድነቱ፣ ከዚያም አልፎ ለመጠፋፋት መነሣሣቱ መቼ ዕድል ያገኝ ነበር፤ ዓለማችን፣ ሀገራችንም ጭምር እየተለማመደችው ያለው ይህ የጥላቻና የራስ ወዳድነት አመለካከት፣ በምድር ላይ በእጅጉ የሚጐዳንና በመጨረሻው የፍርድ ቀንም በዕዳና በፍዳ የሚያስጠይቀን ነው፡፡ ስለዚህ ለጠብና ለመለያየት መንሥኤ ናቸው የሚባሉ ምክንያቶች በሙሉ በፍቅረ እግዚአብሔርና በፍቅረ ቢጽ ማማ ላይ ሆነን ብናያቸው ኖሮ ኢምንት ነበሩ፡፡ ሁሉም ችግሮች በውይይት ወይም በሰጥቶ መቀበል መርሕ አለያም በሕግና በሕግ ብቻ መፍታት እየተቻለ ሰው ሰውን ለመጕዳት መከጀል ትልቅ ስሕተት ነው፤ የሦስት ሺሕ ዘመናትና ከዚያም በላይ ከእግዚአብሔር ሕግ ጋር ተሳስረው የኖሩ ሀገርና ሕዝቦች አሉን ብለን በኵራት የምንተርክ ሕዝቦች የሕጎች ሁሉ የበላይ ሕግ የሆነውን ፍቅረ እግዚአብሔርንና ፍቅረ ቢጽን ማእከል አድርገን የውስጥ ችግራችንን በሰላማዊና በወንድማዊ መንፈስ መፍታት እንዴት ያቅተናል? ድንጋይ መወራወርስ ማንን ይጠቅማል? እኛ ኢትዮጵያውያን አሁን እየተከተልነው ያለው አካሄድ ለእኛ መልካም ነገርን የማይመኙልንና እድገታችንን የማይሹ እንዲሁም በአንድነታችን ከባድ ሥጋት የሚያድርባቸውን ብቻ ይጠቅም እንደሆነ እንጂ እኛን ፈጽሞ እንደማይጠቅመን በተጨባጭ እያየነው ነው፡፡

በመሆኑም አሁንም ወደልባችን እንመለስና ችግራችንን በራሳችን ፈትተን ወደፍጹም ፍቅራችንና ወደሃይማኖታችን በማምራት እድገታችንን ልናፋጥን ይገባል፤ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት መሪዎችና ምሁራንም በገለልተኝነትና በቅንነት ሆነን የመምከር፤ የማስታረቅና የማስማማት ሥራን አጠንክረን መሥራት ይገባናል፤ መንግሥትም ከፍተኛ ኀላፊነት ያለበት ነውና ነገሮችን ሁሉ በትዕግሥትና በአርቆ አስተዋይነት በመመልከት፣ ሁሉንም ለማሰባሰብና ለማቀፍ እንደዚሁም ቅሬታ ያላቸውን ወገኖች ይበልጥ በማቅረብና ሥጋታቸውን በመቅረፍ፣ አስተማማኝ ሰላምና ጠንካራ አንድነት በሀገሪቱ ሕዝቦች እንዲረጋገጥ ተግቶ እንዲሠራ እንመክራለን፤ ሕዝቡና የፖለቲካ ተፎካካሪ ወገኖቻችንም ልዩነቶችና አለመግባባቶች እየቀነሱ አንድነትና ፍቅርን፣ መተማመንና ከሥጋት ነፃ መሆንን እያጐለበቱ በከፍተኛ ኀላፊነት እንዲሠሩ በዚህ አጋጣሚ አባታዊ ምክራችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም፤ ሁሉም ነገር ከእግዚአብሔር ቍጥጥር ሥር በታች መሆኑን አምናችሁ በሀገራችን ፍጹም ሰላምና ፍቅር እንዲሰፍን ይህ አሁን በድንገት ተነሥቶ እንደ ሰደድ እሳት በመላው ዓለም ላይ የተለቀቀውን ‹‹ኮሮና ቫይረስ›› የተባለውን ወረርሽኝ በሽታ በመለኮታዊ ኀይሉ እንዲያስወግድልን በምሕላና በጸሎት እግዚአብሔርን በመማፀን ተጠምዳችሁ የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፣ አሁንም ዘላቂ ሰላምና አንድነትን ሊሰጠን ወደሚችል ወደ እግዚአብሔር በኃዘንና በለቅሶ፣ በዕርቅና በይቅርታ በፍጹም ፍቅርም ልባችሁን በመስበር ወርኀ ጾሙ እስኪጠናቀቅ ድረስ ምሕላችሁን እንድትቀጥሉ አደራ ጭምር አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡ እግዚአብሔር ወርኀ ጾሙን አስፈጽሞ ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም ያድርሰን!!

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ፤ ይቀድስ፤ ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን!!

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/a/wp-content/uploads/logo-am.svg tc32020-03-22 14:01:372025-01-28 14:02:33መጋቢት 13 ቀን 2012 ዓ.ም የደብረ ዘይት በዓል መልእክት የሚከተለው ነው
Search Search

Recent Posts

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ፤ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሸገር ከተማ ሀገረ ስብከት የለገጣፎ ኆኅተ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ምርቃት ሕንጻ ቤተክርስቲያን ተገኝተው ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ
  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ
  • መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
  • ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ወኣምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰምንቱ ዓመተ ምሕረት

Archives

  • May 2026
  • April 2026
  • March 2026
  • February 2026
  • April 2025
  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: የካቲት 16 ቀን 2012 ዓ.ም የዐቢይ ፆም መግቢያ መልእክት Link to: የካቲት 16 ቀን 2012 ዓ.ም የዐቢይ ፆም መግቢያ መልእክት የካቲት 16 ቀን 2012 ዓ.ም የዐቢይ ፆም መግቢያ መል... Link to: መጋቢት 14 ቀን 2012 ዓ.ም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ካህናትና ምእመናን ከኮሮና ቫይረስ ራሳቸውን እንዲጠብቁ መመሪያዎች አስተላልፏል፡- Link to: መጋቢት 14 ቀን 2012 ዓ.ም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ካህናትና ምእመናን ከኮሮና ቫይረስ ራሳቸውን እንዲጠብቁ መመሪያዎች አስተላልፏል፡- መጋቢት 14 ቀን 2012 ዓ.ም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top