ሐምሌ 28 ቀን 2010 ዓ.ም. አራተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ በሲኖዶሳዊ ዕርቅ፣ በሰላምና በአንድነት ወደ ሀገራቸው መግባታቸውን አስመልክቶ መንግሥት በሚሊኒየም አዳራሽ ከፍተኛ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡

ሐምሌ 28 ቀን 2010 ዓ.ም. አራተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ በሲኖዶሳዊ ዕርቅ፣ በሰላምና በአንድነት ወደ ሀገራቸው መግባታቸውን አስመልክቶ መንግሥት በሚሊኒየም አዳራሽ ከፍተኛ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡ መርሐ ግብሩን አስምልከተው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃ ይማኖት የሚከተለውን አባታዊ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

“እምይእዜሰ ይኩን ሰላም — ከዛሬ ጀምሮ ሰላም ይሁን፤» ሰላም ይስፈን በመላዪቱ ሀገራችን፤ ሰላምና ፍቅር አንድነት ይስፋፋ”

ክቡር የኢፌድሪ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ፣
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ 4ኛ የኢትዮጵያ ፓትርያርክ፣
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣
ክቡራን ሚኒስትሮችና አምባሳደሮች፣
ክቡራን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ካህናት፥
ክቡራን የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፣ በአጠቃላይ በዚህ የአንድነትና የዕርቅ ማብሠሪያ መርሐ ግብር ላይ የተገኛችሁ ሁላችሁ፤

«እምይእዜሰ ይኩን ሰላም — ከዛሬ ጀምሮ ሰላም ይሁን፤» ሰላም ይስፈን ተብሎ የተነገረው ቃል ለሁለት ተከፍለን በነበርነው አባቶች መካከል ዕርቅ ወርዶ እውን ሆኖ፥ ሥምረት አግኝቶ ለዚህ የአንድነታችንና የደስታችን ዕለት ማብሠሪያ ቀን በመድረሳችን ከሁሉም በላይ የሰላም የአንድነት እና የፍቅር አምላክ እግዚአብሔር ይመስገን፡፡

እንዲሁም ያለፈው የመለያየት ጊዜ አብቅቶ ሰላም ተገኝቶ ብፁዕ ወቅዱስነትዎ እና ብፁዓን አባቶች ወደምትወዷትና ስትናፍቋት ወደነበረችው ቅድስት ሀገራችሁ በመምጣት በዚህ ሁኔታ አንድ ሁነን በመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ፊት ለመቆም ያስቻለንን እግዚአብሔርን ደግመን እናመሰግነዋለን፡፡

በዚሁ ሳምንት ሐምሌ 25 ቀን 2010 ዓ.ም ረቡዕ ዕለት ቅዱስነታቸውን ከቦሌ ኤርፖርት ተቀብለን በቀጥታ ወደ መንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሄደን ሰፊ የሆነ የአቀባበል ሥነ ሥርዐት እንደተፈጸመ የሚታወስ ነው፡፡

ዛሬ ደግሞ በክቡር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ጋባዥነት ተመሳሳይ የአቀባበል በዓል ለማክበር በዚህ በሚሊንየም አዳራሽ ተሰብስበናልና አምላካችን እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን፡፡

በሀገር ውስጥም ሆነ በመላው ዓለም የምትገኙና እንዲሁ በዚህ ዐቢይ ጉባኤ የተገኛችሁ ሁላችሁ ሐዋርያዊት ጥንታዊትና ታሪካዊት የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በረጅሙ የታሪክ ጒዞዋ በሃይማኖት መሪዎቿ መንፈሳዊ ብርታት፣ በሊቃውንቶቿ ትምህርት፣ በካህናቶቿ አገልግሎትና በምእመናን ተከታዮቿ ጽንዐ-ሃይማኖት ህልውናዋና አንድነቷ ተጠብቆ መኖሩ ሁሉም የሚያውቀው ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ታሪኳንና ባህሏን ጠብቃ ለረዥም ዘመን ልትዘልቅ የቻለችበት ዐቢይ ምሥጢር፣ የቤተ ክርስቲያን አባቶች በነበራቸው የማይበገር የአንድነት ጽናት አንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ይሁንና ላለፉት ሁለት ዐሥርተ ዓመታት በተለያዩ ምክንያቶች አለመግባባት በመፈጠሩ የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ አመራር ለሁለት ተከፍሎ ቆይቶ ነበር፡፡

እንደሚታወቀው የሰላምና የአንድነት መሪና አስተማሪ ሆና ለዘመናት ሕዝቧን ስትመራ የኖረችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በዘመናችን ሰላምንና አንድነትን ማጣቷ መላውን የቤተ ክርስቲያን ልጆች በእጅጉ ያሳዘነና ያሳሰብ ዐቢይ ጉዳይ ሆኖ እንደቆየ እንገነዘባለን፡፡

የተወደዳችሁ የቤተ ክርስቲያናችን ተከታዮች ምእመናንና ምእመናት የቤተ ክርስቲያን አባቶችን አንድነት ለማየት ዘወትር ትናፍቁ እንደነበር ቅዱስ ሲኖዶስ ይገነዘባል፡፡ ሆኖም “ጊዜ ገቢር ለእግዚብሔር” እንደተባለው ከሁለት ዐሥርተ ዓመታት በላይ የአገር ቤትና የውጭ ሲኖዶስ በሚል በመካከላችን የጥል ግርግዳ ሆኖ ቆይቶ የነበረው ግንብ በመፍረሱና በዚህ እናንተ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ፊት በአንድነት ስንቆም የሚሰማን ልባዊ ደስታ ዕጥፍ ድርብ ነው፡፡

በእኛ በአባቶቻችሁ መለያየት ምክንያት እናንተ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ግራ ገብቷችሁ በኀዘን ለኖራችሁባቸው ዓመታት ካሳ እግዚአብሔር አምላካችን ፊቱን መልሶልን፣ በዐይነ ምሕረቱም ተመልክቶን ዕርቀ ሰላም ወርዶ በአንድነት ስንጸልይ አይታችሁ ኀዘናችሁ ወደ ደስታ እንደተለወጠ እርግጠኞች ነን፡፡

እንደሚታወቀው “ሰላም” የሚለው ቃል መልካም ነገር ሁሉ ተሟልቶና ተስተካክሎ መገኘቱን የሚያመለክት ቃል ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን የሰላምና የይቅርታ አምላክ መሆኑን ከዚህ ተጨባጭ ሁኔታ መገንዘብ እንችላለን፡፡ ሐዋርያዊት፣ ጥንታዊትና ተሪካዊት የሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በረጅሙ የታሪክ ጒዞዋ በሃይማኖት መሪዎቿ ብርታት፣ በሊቃውቶቿ ትምህርት፣ በካህናቶቿ አገልግሎትና በምእመናን ተከታዮቿ ጽንዐ -ሃይማኖት ህልውናዋና አንድነቷ ተጠብቆ መኖሩን ሁሉም የሚያውቀው ነው፡፡

በቀጣይም ከእኛ የቤተ ክርስቲያን አባቶችና ከእናንተ ከመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን የሚጠበቀው ይኸው የትናንት አባቶቻችንን ፈለግ በመከተል ለአገርና ለወገን የሚጠቅመውን ሥራ መሥራት ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ሁላችንም እንደምንረዳውና እንደምንገነዘበው አገራችን ኢትዮጵያን ወደ ጥንተ ታሪኳ ለመመለስ እና ዜጐች ሁሉ ከአላዋቂነት መንፈስ ተላቅቀው ለሰው ልጆች ሁሉ የሚያስፈልገው መሠረታዊ ጉዳይ ተሟልቶላቸው በአገራቸው ሠርተው ፍሬ በረከት በዝቶላቸው፣ አገር ለቅቆ ከመሰደድ፣ ከርስ በርስ አላስፈላጊ ግጭት ራሳቸውን ጠብቀው በአገራቸው አምረው ደምቀው በሰላም በአንድነት እንዲኖሩ ለማድረግ በሕዝባችንም ሆነ በመንግሥታችን በኩል እየተደረገ ያለውን ጥረት ግቡን እንዲመታ ቤተ ክርስቲያናችን በብርቱ ትጸልያለች፤ የበኩሏን የሚጠበቅባትንም ሆነ የሚፈለግባትን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ ናት፡፡

በተለይም በአሁኑ ጊዜ በሁላችንም የዘወትር ጸሎትና ጥረት በፈቃደ እግዚአብሔር በቤተ ክርስቲያናችን የተገኘው አንድነትና ሰላም ቤተ ክርስቲያናችን በአገር ውስጥም ሆነ በውጭው ዓለም ለምታበረክተው መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ምቹ ሁኔታ የፈጠረላት መሆኑ ተስፋችንና ራእያችንን ሰፊ ያደርገዋል፡፡ በአጠቃላይ ለዚህ የዕርቀ ሰላም ድርድር አሁን ላለንበት የሠመረ ውጤት እንድንበቃ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ መላው ካህናትና ምእመናን ልጆቻችን እንዲሁም ችግራችሁ የእኛም ችግር ነው በማለት ከጐናችን በመቆም በጸሎት ስትረዱን ለነበራችሁ፣ ከዚህ እስከ ሰሜን አሜሪካ በመጓዝ ለሰላሙ ጥረት ላደረጋችሁ የሰላምና አንድነት ጉባኤ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም እናመሰግናለን፡፡

እንዲሁም ዕርቀ ሰላሙን በአጭር ጊዜ ውስጥ አከናውነው ለመጡት በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ የሚኖሩት ሊቃነ ጳጳሳትን በእጅጉ እናመሰግናቸዋለን፡፡ በተለይም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ቅድስት አገራችንን ለመምራት ከተሰየሙበት ጊዜ አንሥቶ በአገራችን እያሳዩት ያለው የሰላምና የአንድነት ጥሪና ተልእኮ ውጤት ጋር የቤተ ክርስቲያናችንን ጉዳይ አንዱ አገራዊ ችግር አድርገው በመመልከት መለያየቱ ተወግዶ አንድነት እንዲመጣ በምክር በማግባባትና በዕርቀ ሰላሙ ጉባኤ ላይ በመገኘት እንዲሁም ይህን የዕርቅና የአንድነት ማብሠሪያ መርሐ ግብር እንዲዘጋጅ በመፍቀድና መመሪያ በመስጠት ጭምር ያደረጉት አስተዋጽኦ ምንጊዜም ታሪክ የማይረሳው ሆኖ የሚኖር ተግባር በመሆኑ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድን በቅድስት ቤተ ክርስቲያንና በእናንተ በመላው ማኅበረ ካህናትና ማኅበረ ምእመናን ስም ከልብ በመነጨ ስሜት እናመሰግናቸዋለን፡፡

በመጨረሻም ቤተ ክርስቲያናችንን ለዚህ የዕርቀ ሰላምና አንድነት ማብሠሪያ ቀን አድርሶ በእንዲህ ዐይነቱ ታላቅ ጉባኤ እንድንገናኝ ያደረገ ሁሉን ቻይ የቤተ ክርስቲያናችን መሠረትና ራስ የሆነውን እግዚአብሔርን እናመሰግናቸዋለን፡፡

እግዚአብሔር አገራችን ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፣ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!