37ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ጥቅምት 5 ቀን 2011 ዓ.ም አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
በአጠቃላይ በዚህ ዓመታዊ ዓለም ዐቀፍ አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ለመሳተፍ በዚህ ስፍራ የተገኛችሁ ክቡራንና ክቡራት፤ የቤተ ክርስርቲያን አንድነትን በቅዱስ መንፈሱ ኀይል ዘወትር የሚጠብቅ እግዚአብሔር አምላካችን አንድነታችንን መልሶ፣ ወንድማማችነታችንን፣ ፍቅራችንንና ሰላማችንን አድሶ ለዚህ ታሪካዊና ዓመታዊ ዓለም ዐቀፍ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በሰላም ስላደረሰን ክብርና ምስጋና ለእርሱ እናቀርባለን፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ጥሪ ተቀብላችሁ በዚህ ጉባኤ ለመገኘት ከቅርብም ከሩቅም፣ ከውስጥም ከውጭም ለመጣችሁና የእግዚአብሔር ሠራዊት ለሆናችሁ ለእናንተም እንኳን በደኅና መጣችሁ እንላለን፡፡
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፣
ሐዋርያዊት፣ዓለም አቀፋዊት፣ አንዲትና ቅድስት የሆነች ቤተ ክርስቲያናችን በቅዱስ ባኮስ ኅጽዋ ለሕንደኬ ንግሥተ ኢትዮጵያ አማካኝነት እንደተመሠረተች ቅዱስ መጽሐፍና የታሪክ መጻሕፍተ አበው የመሰከሩት እውነት ነው፡፡ ከዚህም በኋላ በቅዱስ ፍሬምናጦስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዘኵሎን አድያማተ ኢትዮጵያ ትጋት፣ በቅዱሳን ነገሥት አብርሀ ወአጽብሐ አደራጅነት፣ በሀገረ ስብከት ደረጃ ተቋቁማ የተሟላ ሐዋርያዊ፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ለመላው ሕዝበ ኢትዮጵያ ስታበረክት ኖራለች፡፡ቅዱሳን ነገሥት አብርሀ ወአጽብሐ የክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች ከመሆናቸውም ባሻገር የቅዱስ ፍሬምናጦስ አቡነ ሰላማ ሐዋርያዊ ተልእኮ እንዲቃና ድጋፍ ሰጭ ብቻ ሳይሆኑ ከሊቀ ጳጳሱ ጋር እንደ አንድ ሐዋርያ ሆነው ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ እየተዘዋወሩ ሕዝቡን ሁሉ አስተምረው፣አሳምነውና አጥምቀው የሥላሴ ልጅነትን እንዳጎናጸፉት፣ ትዕይንተ ደብተራ ዘአክሱም፣ ባሕረ ጣና ዘጎንደር ፣ መርጡለ ማርያም ዘጎጃም፣ ተድባበ ማርያም ዘወሎ፣ ጎሐ ጽዮን ዘሸዋ፣ በሓ ጊዮርጊስ ዘከፋ የዐይን ምስክሮች ናቸው፡፡
ቅዱስ ፍሬምናጦስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃንና ቅዱሳን ነገሥት አብርሀ ወአጽብሐ ሃይማኖተ ክርስትና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሃይማኖት እንዲሆን በአዋጅ ከማጽናታቸውም ሌላ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ለካህናት መተዳደሪያ የሚሆን መሬት በበቂ ሁኔታ እንዲሰጥ በማድረጋቸው ቤተ ክርስቲያናችን በዚህ ሥርዐተ ምግብና እስከ 1969 ዓ.ም. ስትተዳደር ኖራለች፡፡ አበው “መሰላል ሳይፈጥር ገደል አይፈጥርም” እንደሚሉት እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያናችንን ፊት ለፊት ከተጋረጠባት ፈተና ለመታደግ ሲል በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ላይ ቅዱስ መንፈስን አሳደረ፤ ቅዱስነታቸው ቤተ ክርስቲያን በመሬት ሥሪት የመተዳደር ዕድሏ ቀጣይ እንደማይሆን፣ የተደቀነው ፈተናም ለቤተ ክርስቲያን አሥጊ መሆኑን እንዲገነዘቡና መፍትሔ እንዲያበጁ እግዚአብሔር ስላመለከታቸው ቤተ ክርስቲያን እንደ ጥንቱ እንደ ዘመነ ሐዋርያት በልበ ምእመናን ተጠልላ በእደ ምእመናን እንድትመገብ የሚያስችል አሠራርን ቀየሱ፡፡
እግዚአብሔርም ሩቅና ዘላቂ ሕልማቸውን ባርኮላቸው ቤተ ክርስቲያን በልበ ምእመናን ተጠልላ በእደ ምእመናን እንድትመገብ የሚያስችል የቃለ ዐዋዲ መተዳደሪያ ደምብን በቅዱስ ሲኖዶስ አጽድቀው፣ በፍትሐ ብሔር ዕውቅና አሰጥተው ለቤተ ክርስቲያን የህልውና ማስቀጠያ ዋስትና አስረክበው በሰማዕትነት አልፈዋል፤
ካህናትን፣ ምእመናንና ወጣቶችን በአንድነት አደራጅቶ፣ በሐብለ ሃይማኖት ባስተሳሰረው በቃለ ዐዋዲ ደምብ የምትመራው ቤተ ክርስቲያናችን ይህ መሰሉን ዓለም አቀፋዊ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ስታካሄድ እነሆ ዛሬ ሠላሳ ሰባተኛው ጉባኤ ላይ ደርሳለች፡፡ በመሆኑም፣ ይህ ጉባኤ የቤተ ክርስቲያንን አጠቃላይ የሥራ ክንዋኔ የምንመዝንበት፣ ባለፈው ዓመት ያጋጠሙንን ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ፈተናዎችን የምንገመግምበት፣ በአንጻሩ ደግሞ ባለፉት ዓመታት የተከሠቱ ፈተናዎች በቤተ ክርስቲያንና በሕዝበ ክርስቲያን ላይ ዳግም እንዳይከሠቱ መብታችንንና ክብራችንን ለማስጠበቅ በቊርጠኝነት ለመሥራት የምንነሣበት፣ ክፍተት የሚታይባቸውን የመልካም አስተዳደር ዕጦት፣ የሀብት አያያዝ ብክነት፣ የምእመናን ፍልሰት፣ በውጭ የሚገኙ የአብያተ ክርስቲያናት ውሕደት፣ የሀገር ሰላምና አንድነት፣ የዜጎችን ደኅንነት አንሥቶ በስፋትና በጥልቀት ይወያይባቸዋል፤ የጋራ አቋምም ይወስድባቸዋል የሚል ጽኑ እምነት አለን፡፡ መቼም ሁላችንም እንደምንገነዘበው የጉባኤ አስፈላጊነት፣ በሥራ ሂደት የተከሠተውን ደግም ይሁን መጥፎ ገጠመኝ በጋራ ለማየትና ለመመዘን፣ ከዚያም ካለፈው ልምድና ተሞክሮ ግንዛቤ በመውሰድ ካለው ነባራዊ ሁኔታ ጋር የተገናዘበ ግምታዊ ተነብዮን አስቀምጦ ለወደፊት የተሻለ የቅድመ መከላከያና ማስተካከያ አሠራር ለመዘርጋት ነው፡፡
የሰበካ ጉባኤ የጀርባ አጥንት በሆነው የቃለ ዐዋዲ ደንብ የተገኘው የሰበካ ጉባኤ ለውጥ ቀላል ባይሆንም በደምቡ መሠረት በምልአት ቢሠራበት ኖሮ ማለትም በዘመነ የሰው ኀይል አስተዳደር፣ በሠለጠነ የሀብት አያያዝ፣ እንዲሁም በጠነከረ አሓዳዊ መዋቅር ቢታጀብ ኖሮ አሁን ካለው የበለጠ እድገት ማስመዝገብ ይቻል እንደነበር በግልጽ ይታያል፡፡ ከስድሳ ሚሊዮን ያላነሰ የምእመናን ብዛት ይዛ፣ በቢሊዮን ብር የሚገመት የመሬት ይዞታ ጨብጣ፣ ብዙ ትርፍ ሊያስገኙ የሚችሉ የንዋየ ቅድሳት ምርቶችን ተጠቃሚ ሆና፣ በቱሪዝም ክፍለ ኢኮኖሚ ልትጠቀምባቸው የሚችሉ ኁልቈ መስፈርት የሌላቸው ቅርሶችን በጉያዋ ታቅፋ የምትገኝ ቤተ ክርስቲያናችን ድሀ ናት ብለን መናገር እንዴት እንችላለን? ይህ ሁሉ ሀብት ያላት ቤተ ክርስቲያንን ምንም እንደሌላት ቈጥረን የአብነት ት/ቤቶች ሲዳከሙ፣ ገዳማት ሲዘጉ ዝም ብለን ማየትስ ኀጢአት አይደለምን?
የሠላሳ ሰባተኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤን ልዩ የሚያደርገው ቤተ ክርስቲያናችን ብዙ አስደሳችም አሳዛኝም ድርጊቶች ባስተናገደችበት ማግስት የሚካሄድ መሆኑ ነው፡፡ ከመልካም አጋጣሚዎች መካከል ለብዙ ዓመታት ተለይተውን በባዕድ ሀገር የቆዩት አራተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘአትዮጵያ ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር ወደ ሀገራቸው ገብተው የቤተ ክርስቲያን አንድነት ወደነበረበት መመለሱ ነው፤ እንደዚሁም የኢትዮጵያና የኤርትራ መንግሥታትና ሕዝብ ወደ ሰላምና ዕርቅ ተሸጋግረው፣ ወንድማማችነታቸውን አጽንተው፣ የጥል ግድግዳን አፍርሰው፣ በፍቅር ተሳስረው ለመኖር መስማማታቸው ከመልካም አጋጣዊዎች መካከል የሚጠቀሱት ናቸው፡፡
በሌላ በኩል ዓመታዊው ጉባኤያችን ካለፉት 3 ዓመታት በፊት ጀምሮ እየባሰበት የመጣ ግጭት ቤተ ክርስቲያናችን ብዙ ምእመናን ልጆችዋ ከቀያቸው የተፈናቀሉበት፣ የቆሰሉበት፣ የተጎዱበትና የሞቱበት፣ በተለይም በኢትዮጵያ ሱማሌ ክልል እና በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎችና በርካታ ዞኖች የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ከነ ሙሉ ንብረታቸው የተቃጠሉበት፣ ካህናትና ምእመናን በሚዘገንን የጭካኔ ተግባር የተገደሉበት አሳዛኝ ድርጊት በተፈጸመበት ማግስት የሚካሄድ በመሆኑ በደጉም በክፉም ገጽታው እናስታውሰዋለን፤ ይሁንና ሁሌም እንደሚባለው ላለፈው ክረምት ቤት አይሠራምና፥ እንደዚህ ዐይነቱ ድርጊት እየተለመደ እንዳይሄድ ቤተ ክርስቲያን ልዩ የግንኙነት መረብ ወይም የኮሙዩኒኬሽን ሲስተም ዘርግታ የአምልኮ ቦታዋንና የምእመናን ልጆችዋን ደኅንነት በቅርበት በመከታተል ኀላፊነትዋን መወጣት ይኖርባታል፡፡ ይህ ምልዓተ ጉባኤም በመላ ሀገራችን ጸሎት እንዲታወጅ ውሳኔ ማሳለፍ አለብን፤ ቤተ ክርስቲያናችን ከሆነ በኋላ ማልቀስና በዐሥር ሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ አውጥታ መደጎም ሳይሆን፣ በዐሥር ሚሊዮን ብር የግንኙነት መረብ ዘርግታ ችግር ከመፈጠሩ በፊት የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥራ በመሥራትና ከመንግሥት የጸጥታ ኀይል ጋር ተቀናጅታ አደጋዎችን አስቀድማ መከላከል አለባት፤ በዚህ ዙሪያ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤም ጠንካራና ትክክለኛ ውሳኔ በመወሰን አቅጣጫ ያስቀምጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ከዚህም ሌላ ባለፉት ዓመታት በነበረው የአባቶች መለያየት ምክንያት አንዱ የውጭ ሲኖዶስ፣ ሌላው የሀገር ውስጥ ሲኖዶስ፣ ሌላው ደግሞ ገለልተኛ በሚል ስያሜ ምክንያት ቤተ ክርስቲያናችን አንድነትዋን አጥታ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አስዳደርዋን በአግባቡ ለማከናወን ብዙ እክል እያጋጠማት እንደቆየ የሚዘነጋ አይደለም፤ አሁን ግን በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በመንግሥታችን ድጋፍ ፣ በሕዝበ ክርስቲያኑ ጸሎት የቤተ ክርስቲያናችን አንድነት የተረጋገጠ በመሆኑ ከቤተ ክርስቲያን ማእከላዊ አስተዳደር ውጪ ሆኖ መኖር ክርስቶስ ደሙን አፍስሶ በመሠረታት ቤተ ክርስቲያን ላይ መዘበት ነው የሚሆነው፤ ከሁሉም በላይ በመላው ዓለም ላይ የሚገኙ ካህናትና ምእመናን፣ እናቶችና አባቶች ወጣቶች በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ድንጋጌ መሠረት በፍትሕ መንፈሳዊ እንደተደነገገው ቅዱስ ሲኖዶስ በመደበው ሊቀ ጳጳስ በሚተዳደር ሀገረ ስብከት ሥር ታቅፋ የማትመራ ቤተ ክርስቲያን፣ እንደዚሁም በሊቀ ጳጳስ አስተዳደር ሥር ባለች ቤተ ክርስቲያን ያልታቀፈ ማንኛውም ካህን ይሁን ምእመን፣ ምእመናት ሴቶች ይሁኑ ወጣቶች ኦርዶክሳዊ ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን እየጣሱ እንደሆነ ሊያውቁና ሊገነዘቡ ይገባል፡፡ በመሆኑም ከዛሬ ጀምሮ ሁሉም በየአካባቢያቸው ባለው ሀገረ ስብከት እየታቀፉ በሊቀ ጳጳሱ ሥር በመሆን ሃይማኖታቸውን እንዲጠብቁ ለቤተ ክርስቲያናቸው መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎት እንዲያበረክቱ በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡
በመጨረሻም፡ ይህ ዐቢይ ጉባኤ በሐዋርያዊ ተልእኮ፣ በመልካም አስተዳደር፣ በቤተ ክርስቲያን ሀብት አጠባበቅ፣ በቤተ ክርስቲያን መዋቅራዊ ውሕደት፣ በሀራዊ ሰላምና አንድነት፣ በቤተ ክርስቲያን ቀጣይ ልማትና እድገት፣ እንደዚሁም በቤተ ክርስቲያን ሉዓላዊ ህልውና፣ በመብቷና በክብሯ መጠበቅ ላይ አጥብቆ በመወያየት ለቤተ ክርስቲያን የሚበጅ ውሳኔ እንዲያሳልፍ፣ ከዚህም ጋር ለተቃጠሉ አብያተ ክርስቲያናትና ለተጎዱ ምእመናን ድጋፍ እንዲደረግላቸው በሰፊው እንዲመክር በማሳሰብ ሠላሳ ሰባተኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በዛሬው ዕለት የተከፈተ መሆኑን በእግዚአብሔር ስም እናበሥራለን፡፡ እግዚአብሔር ጉባኤውን የተባረከና የተቀደሰ ያድርግልን
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡