ከግንቦት 17 ቀን እስከ ግንቦት 23 ቀን 2013 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቍጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልአተ ጉባኤው የመክፈቻው ሥርዐተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከግንቦት 17 ቀን 2013ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ግንቦት 20 ቀን 2013ዓ.ም. ድረስ የተለመደውን ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ ሲያካሂድ ሰንብቶ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሚበጁ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ውሳኔዎችን አሳልፎአል፡፡

በዚሁ መሠረት፡-

1. የ2013 ዓ.ም. ግንቦት ርክበ ካህናት የጉባኤ መክፈቻ በሀገራችን ወቅታዊ ሁኔታዎች ማለትም፡-
• ስለ ሀገር ደኅንነትና ስለ ሕዝቦች አንድነት፣
• ከቀያቸው ስለተፈናቀሉና ለስደት ስለተዳረጉ ወገኖች፣
• በተለያዩ አካባቢዎች እየታዩ ስለአሉ አለመግባባቶች የሚያመላክት እና ይህንንም በመግባባት በውይይት በይቅርታ መፍታት እንደሚገባ ከሁሉም በላይ ወደ እግዚአብሔር በመጸለይ ምሕረት መጠየቅ እንደሚያስፈልግ የሚገልጽ በመሆኑ ጉባኤው ተቀብሎ በተግባር ላይ እንዲውል ተስማምቷል፡፡

2. ሀገራዊ ሰላምን አስመልክቶ ጉባኤው በስፋት ከተነጋገረ በኋላ በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች በተፈጠሩ ግጭቶች ምክንያት የጠፋው የሰው ሕይወት የታረዱና ከቀያቸው የተፈናቀሉ ወገኖች በችግሩ ምክንያት የወደመ ንብረት በዐይነትና በቊጥር ተለይቶ በየአህጉረ ስብከቱ ተጣርቶ እንዲቀርብ ተወስኗል፡፡

3. የቤተ ክርስቲያን የአምልኮ ሥፍራ ስምና እስከዛሬ ተጠብቆ የቆየ ክብሯ እንዲሁም በካህናትና በምእመናን ላይ እየደረሰ ያለ ሞት፣ ስደት የመሳሰለው ከየአህጉረ ስብከቱ ተጣርቶ ሪፖሪት እንዲቀርብ መንግሥትም አስፈላጊውን ጥበቃ እንዲያደርግ ጉባኤው አሳስቧል፡፡

4. ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በሀገራችን የነበረውንና የቆየውን ታሪካዊ ሂደት ለመቀየር በዚህም አጋጣሚ የኖረውንና ዓለም የሚያውቀውን በዓለም ዐቀፍ ደረጃ በዩኒስኮ የተመዘገበ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመስቀል አደባባይና የባሕረ ጥምቀት ቦታዎች እንዲሁም የአምልኮ ሥፍራዎችን ምክንያት በመፍጠር አንዳንድ ወገኖች የግጭትና የትንኮሳ ተግባር እየፈጸሙ መሆኑ ጉባኤውን በእጅጉ አሳዝኗል፡፡በመሆኑም ይህ በቤተ ክርስቲያናችን ስም የቆየው የዘመናት ታሪክ ሀገራዊ ታሪክ ተደርጎ ልዩ ጥበቃና ክብካቤ ሊደረግለት ስለሚገባ አሁንም መንግሥት ለጉዳዩ ትኵረት በመስጠት የኖረው የቤተ ክርስቲያኒቱና የሀገሪቱ ታሪክ ክብሩ ከነማንነቱ ተጠብቆ እንዲኖር የበኩሉን እንዲወጣ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት አሳስቧል፡፡

5. ሀገራችን ኢትዮጵያ በዘመናት ታሪኳ እንደሚታወቀው ዳር ድንበሯን ጠብቃና አስጠብቃ ያለ ቅኝ ግዛት ያለ ማንም ጣልቃ ገብነት በሀገር ወዳድ መሪዎቿ አንድነቷን ጠብቃ የቆየች መሆኗ ዓለም የሚያውቀው ነው፡፡ ይሁን እንጂ በአሁኑ ጊዜ አንዳንድ የውጭ ሀገራት ከሩቅና ከቅርብ ግንባር በመፍጠር በሀገራችን ህልውና ላይ እያደረጉት ያለው ጣልቃ ገብነት፣

• ሀገራዊ የመልማት ፍላጎታችንን ለመግታት
• ዳር ድንበራችንን ለመድፈር እያደረጉ ያለውን ሙከራ ጐረቤት ሀገራት ጭምር በጠላትነት እንዲነሣሡብን እያደረጉ ያለው ቅስቀሳ ተዘዋዋሪ ቅኝ ግዛት በመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ተቃውሞአል ሕዝባችንም ከምንጊዜውም በተለየ መልኩ ሀገራዊ አንድነቱን በመጠበቅ ሀገሪቱን ከውጭ ወራሪ በመከላከል ሀገራዊ ልማትን በማፋጠን የበኩሉን እንዲወጣ ጉባኤው ጥሪውን አቅርቧል፡፡

6. ሀገራችን ኢትዮጵያ በልማት እንድታድግ ሌሎች ሀገራት ከደረሱበት ደረጃ ለማድረስ በዚህም ዜጎችን ከጨለማ ወደ ብርሃን ለማውጣት ታስቦ እየተገነባ ያለው ሕዳሴ ግድባችን ወደ መጨረሻው ምዕራፍ እየተቃረበ እና ለኢትዮጵያውያን ሁሉ የአንድነታችን ማሳያ እየሆነ በመምጣቱ አሁንም ለግንባታው ፍጻሜ መላው ኢትዮጵያዊ እንዲረባረብ ጉባኤው ጥሪውን አቅርቧል፡፡

7. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዘመናት ታሪኳ የአብያተ ክርስቲያናትን ዐጸድ በመትከል አረንጓዴ ልምላሜን በማስፋፋት ጠብቃ የቆየች ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ደግሞ መንግሥታችን በየዓመቱ በቢሊየን የሚቈጠር ችግኝ ተከላ መርሐ-ግብር ማዘጋጀቱ ለአየር ጥበቃና በምግብ ራስን ለመቻል እየተደረገ ያለው ሀገራዊ ጥረት የሚደገፍ በመሆኑ በዘንድሮውም የችግኝ ተከላ መርሐ-ግብር መላው ዜጋ የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ጉባኤው አሳስቧል፡፡

8. ከአንድ ዓመት በፊት በመላው ዓለም ተከሥቶ ብዙዎችን ለኅልፈተ ሕይወት የዳረገው ኮቪድ 19 ተላላፊ በሽታ በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን በመስፋፋቱ ብዙዎች ወገኖቻችንን ለሞት እየዳረገ የሚገኝ በመሆኑ መላው ሕዝባችን ከምንግዜውም በበለጠ በአሁኑ ጊዜ ከጤና ባለሙያዎች የሚሰጠውን ምክረ ሐሳብ በመቀበል ራሱን ከወረርሽኙ እንዲጠብቅ ጉባኤው አሳስቧል፣

9. በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች በተፈጠረው አለመግባባት ምክንያት ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ ያለመጠለያ የሚገኙ እና በዚሁ ተላላፊ በሽታ ምክንያት ችግር ላይ የወደቁ ወገኖቻችንን በተለመደውና በኖረው የመረዳዳትና የመተሳሰብ ባህላችን ከምንጊዜው በላይ አሁን ለችግራቸው እንድንደርስላቸው ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን አቅርቧል፡፡

10. ሀገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ በሽግግር ላይ የምትገኝ በቀጣይም ሕዝባዊ ምርጫ ለማካሄድ በከፍተኛ ዝግጅት ላይ መሆኗ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም ገዥው ፓርቲም ሆነ ተፎካካሪዎች ለሀገራችንና ለሕዝባችን የሚጠቅመውን ሰላማዊ መንገድ እንዲከተሉ መላው ሕዝባችንም ለሀገርና ለወገን ይጠቅማሉ የሚባሉትን በመምረጥ ሁሉም አካል ውጤቱን በጸጋ በመቀበል ኢትዮጵያዊ ጨዋነትን የምናስመሰክርበት ምርጫ እንዲሆን ጉባኤው የሰላም ጥሪውን አቅርቧል፡፡

11. በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት በጐንቻ ሲሶ እነሴ ወረዳ በምስካበ ቅዱሳን ቆጋ ኪዳነ ምሕረት በሕገ ወጥ መንገድ ዶግማና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን በጣሰ መልኩ ራሳቸውን በራሳቸው ጳጳስና ፓትርያርክ አድርገው የሾሙ፡-

1. መምህር ሄኖክ ፈንታ
2. መምህር አባ ኪዳነ ማርያም
3. መሪጌታ ሙሉ

ከግንቦት 19 ቀን 2013ዓ.ም. ጀምሮ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ተወግዘዋል፡፡ የገዳሙንም ሀብትና ንብረት አስረክበው ከገዳሙ እንዲወጡ ተወስኗል፡፡ የዚህ ተባባሪ የነበሩ መነኮሳት ካህናትና ዲያቆናትም የተወገዙ ሲሆን በዚህ የዶግማና የቀኖና ጥሰት ምክንያት በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ተሳስተው ድጋፍ ሲሰጡና ሲከተሏቸው የነበሩ ምእመናን ንስሓ እየገቡ ይቅርታ እንዲደረግላቸው ጉባኤው ወስኗል፡፡

12. በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን ኢትዮጵያ እየታየ ያለው፡-

• የእርስ በርስ አለመግባባት እንዲቆም ፣
• ሞትና ስደት እንዲያበቃ ፣
• ተላላፊ በሽታ ከምድራችን ጠፍቶ ሰዎች በጤንነት እንዲኖሩ ፣
• መጪው ሀገራዊ ምርጫ በኢትዮጵያዊ ጨዋነት በአንድነትና በሰላም እንዲጠናቀቅ ፣
ለዚሁ ሁሉን ቻይና ሁሉን አድራጊ የሰላም አምላክ እግዚአብሔር ሀገራችንና ሕዝባችንን በሰላምና በምሕረቱ እንዲጐበኝ ሁላችንንም ይቅር እንዲለን ከአሁን ጀምሮ በግልም ሆነ በማህበር ጸሎት በማድረግና ችግረኞችን በመርዳት እንድንተባበር ሆኖ ከምርጫው ሰኔ 14 ቀን 2013ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ሐምሌ 4 ቀን 2013ዓ.ም. ድረስ በመላው ሀገራችንና በውጭም ባለችው ቤተ ክርስቲያን ጸሎተ ምሕላ እንዲደረግ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በመጨረሻም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ከግንቦት 17 እስከ ግንቦት 23 ለስድስት ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን ጉባኤ አጠናቅቆ በጸሎት ዘግቷል፡፡

እግዚአብሔር ሀገራችንን ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይጠብቅ፡፡

ግንቦት 18 ቀን 2013 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ 4ኛው ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፤
ብፁዕ አቡነ ያሬድ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅና የአርሲሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤
ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊና የሲዳማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፡-

የምሕረት አባት፣ የሰላም አለቃ የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን ለዓመታዊው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ ስላደረሰን በስሙ ልንወያይም ስላበቃን ክብርና ምስጋና ሁሉን ለሚችል ለኀያሉ አምላካችን ለእግዚአብሔር ይሁን፡፡

“ወተጸመዱ ለጸሎት ኵሎ ጊዜ በእንተ ኩሎሙ ቅዱሳን
ስለ ቅዱሳን ሁሉ ዘወትር ለጸሎት የተጠመዳችሁ ሁኑ”
(ኤፌ. 6፥18)

ከእግዚአብሔር ጋር የሚያገናኘን የቤተ ክርስቲያናችንና የሃይማኖታችን ቊልፍ፣ የግንኙነት መሣርያ ጸሎት እንደሆነ ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም፡፡እግዚአብሔር በሁሉም ያለና የሚገኝ ምሉእ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሔር ሁሉንም ያውቃል፣ ያያልም፡፡ ነገሮች ከመሆናቸው ወይም ከመታሰባቸው በፊት ሳይቀር ድንበርና ወሰን በሌለው ዕውቀቱ ያውቃል፡፡ ይሁንና ቢያውቅም ለፍጡራን ሁሉ በተለይም አእምሮና ለብዎ ላላቸው መላእክትና ሰዎች የተሰጣቸውን ብሩህ አእምሮ ተጠቅመው የሚበጃቸውን በራሳቸው እንዲመርጡና እንዲወስኑ ፍጹም ነፃነትን አጎናጽፎአቸዋል፡፡

ሰዎችም ሆኑ መላእክት ይህንን ነፃነት ተጠቅመው ያለ ምንም ተጽዕኖ ሲወስኑ በውሳኔአቸው ላይ እግዚአብሔር ተጽዕኖ አያደርግም፡፡ ውሳኔአቸውን ተከትሎ በሚመጣው ውጤት ግን ይጠይቃል፣ ዳኝነትም ይሰጣል፡፡ የመላእክትም ሆነ የሰዎች ውድቀት ሊከሠት የቻለው በዚህ ነፃ ምርጫና ውሳኔ እንደሆነ ቤተ ክርስቲያን የምታስተምረን እውነት ነው፡፡ ዛሬም በዓለም እየሆነ ያለው ይኸው እውነት ነው፡፡ ሰው የከፋ ኀጢኣትን ለመፈጸም ሲሮጥ ምክርና ትምህርት ከመስጠት ባለፈ እግዚአብሔር በነገሩ ጣልቃ ገብቶ ሲያስቆም አናይም፡፡ “አቅረብኩ ለከ እሳተ ወማየ ደይ እዴከ ኀበ ዘፈቀድከ — እሳትንና ውኃን አቅርቤልሃለሁ፤ እጅህን ወደ ፈለግኸው ክተት” የሚለውም ይህንን እውነታ ያመለክታል፡፡ ከዚህ አንጻር ሰው መከራዎችንና ፈተናዎችን እየሳበና እየጎተተ የሚያመጣቸው በራሱ ነጻ ምርጫና ውሳኔ እንጂ በሌላ ተጽዕኖ እንዳይደለ እናስተውላለን፡፡ የርኩሳን መናፍስት ተጽዕኖ እንዳለ የምናይበት ጊዜ ቢኖር እንኳ መግቢያቸው የሰው ነፃ ዝንባሌ እንደሆነ በአዳምና በሔዋን ያየነው እውነት ነው፡፡ከዚህ ሌላ ደግሞ ሰዎች በሌሎች ምክንያቶች ሲፈተኑና መከራ ላይ ሲወድቁ የምናየው እውነት ነው፤ ከዚህም አኳያ በቃየን ምክንያት አቤል ሕይወቱን ሲያጣ እንመለከታለን፡፡ ስለዚህ ሰዎች በኀጢአት ምክንያት ከወደቁ በኋላ በራሳቸው ምርጫና ውሳኔ ወይም በሌላ ወገን ግፊት ፈተና ላይ ሲወድቁ እናያለን፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን፤ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

የምንኖርባት ዓለመ ሰብእ ከላይ በተጠቀሱት ምክንያቶች ምን ጊዜም ከመከራና ከፈተና ተለይታ አታውቅም፡፡ ይህ የማይቀር ነገር መሆኑን የሚያውቅ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠን መርሕ ቢኖር፡- “ትግሁ ወጸልዩ ከመ ኢትባኡ ውስተ መንሱ ማለትም ወደ ፈተና እንዳትገቡ ተግታችሁ ጸልዩ” የሚለው ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ጌታችንን ተከትሎ ዘወትር ስለ ቅዱሳን እንድንጸልይ አስተምሮናል፡፡ ከዚህ አንጻር ከመከራና ከፈተና ለመዳን የተሰጠን የመዳኛ ስልት ተግቶ መጸለይ ነው፤ ስንጸልይም ለራሳችን ብቻ ሳይሆን ለቅዱሳን ሁሉ ተግተን ዘወትር መጸለይ እንዳለብን ተነግሮናል፣ ኀላፊነትም አለብን፡፡ ቤተ ክርስቲያን በደመ ክርስቶስ አንጽታ ስለ ቀደሰቻቸው ምእመናን ልጆቿ ዘወትር ስትጸልይ የምትኖረውም ከዚህ የተነሣ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን ስለሆኑ ምእመናን ብቻ ሳይሆን ስለ ዓለሙ ሁሉ ማለትም ስለ ሰማዩም፣ ስለ ምድሩም፣ ስለ እንስሳቱም፣ በአጠቃላይ ስለ ፍጥረት ሁሉ ትጸልያለች፡፡ ይሁንና በአሁኑ ጊዜ ደግሞ በሀገራችን፣ በሕዝባችንና በደመ ክርስቶስ በተቀደሱ ክርስቲያን ልጆቻችን ላይ ከበድ ያለ ፈተና እየተከሠተ ስለሆነ ከምንም ጊዜ በላይ ወደ እግዚአብሔር አጥብቀን ልንጸልይ፣ ልናለቅስና ልናዝን ይገባናል፡፡ገዳማትና አድባራት፣ መነኮሳትና ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና ወጣቶች፣ ምእመናንና ምእመናት ፈተና ላይ ሲወድቁና መከራ ሲጸናባቸው ቅዱስ ሲኖዶስን በቀጥታ የሚመለከተው ስለሆነ የመፍትሔው አካል ሆኖ መሥራት ይጠበቅበታል፡፡ ይህንን የፈተና ጊዜ አይተን እንዳላየን፣ ሰምተን እንዳልሰማን በዝምታ የምናልፈው ከሆነ ለቤተ ክርስቲያናችን ጠባሳ ታሪክ መሆኑ አይቀርም፤ በእግዚአብሔርም ተጠያቂነትን ማስከተሉ አይቀርም፡፡ ምእመናን ልጆቻችንም በዚህ ጉባኤ ላይ አመኔታ እንዳያጡ በጣም መጠንቀቅ አለብን፡፡

ይህ ጉባኤ በሀገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች እየተጎዱ ለሚገኙት ምእመናንና ምእመናት እንደዚሁም በአጠቃላይ ያለ ፍትሕ እየተጎዱ ለሚገኙ ሰዎች መፍትሔ አምጪ አካል ሆኖ ከጎናቸው ሊቆም ይገባል፡፡ይህንንም ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በተሰጠው የጥበቃ ኀላፊነት መሠረት በጸሎት፣ በማስታረቅ፣ በቊሳቊስ ማለትም መጠልያ፣ ምግብ፣ መጠጥ፣ ልብስና መድኀኒት በማቅረብ ሊያከናውነው ይገባል፡፡ ይህ መሰሉ ቅዱስ ተግባር ለቤተ ክርስቲያናችን አዲስ ነገር ሳይሆን ስታደርገው የነበረና አሁንም እያደረገችው የሚገኝ ነው፡፡ የአሁኑ ከሌላው ጊዜ ልዩ የሚያደርገው ነገር ቢኖር የችግሩ ክብደትና ውስብስብነት ማየሉ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ሕልም ተፈርቶ መተኛት እንደማይቀር ሁሉ ክብደቱን አይተን የምንሸሸው ሳይሆን የቤተ ክርስቲያናችን የውስጥ ዐቅምን በማየት የምእመናንን ትብብርና እገዛ በመጠየቅ፣ እንደዚሁም የዓለም አብያተ ክርስቲያናትና ልዩ ልዩ በጎ አድራጊዎችን በማስተባበር መከራውንና ፈተናውን መቋቋም ይኖርብናል፤ ለዚህም የዛሬ ሠላሳ ዓመት ገደማ የነበረው ዐይነት አሠራር ዘርግተን ብንሠራ ሰውን ከረኃብ እልቂት ማዳን እንችላለን፡፡ ስለሆነም ቅዱስ ሲኖዶስ በዚህ ዙርያ በሰፊው መክሮበት ውሳኔ እንዲያሳልፍ በዚህ የመክፈቻ ጉባኤ በአጽንዖት እናሳስባለን፡፡

በመጨረሻም፤ ለመንግሥትም ሆነ ለሁሉም ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ እንደዚሁም ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ማስተላለፍ የምንፈልገው የአደራ መልእክት ቢኖር፣ የሁሉም ነገር መሠረትና የችግሮቻችን ሁሉ መፍትሔ ሰላምና ሰላም ብቻ መሆኑን በመገንዘብ ለሰላም ሲባል አስፈላጊ የሆነ ዋጋ መክፈል እጅግ አስፈላጊ መሆኑ ነው፡፡ ዋስትና ያለው ሰላም በሀገራችን ሊረጋገጥ የሚችለው ደግሞ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በጠረጴዛ ዙሪያ ተሰባስበው መወያየት፣ መግባባትና ሀገራዊ ስምምነትን መፈጸም ሲችሉ ነው፡፡ ስለሆነም ይህ ለነገ የማይባል፣ የህልውናችን ጥያቄ መልስ መሆኑን ዐውቀን ሁላችንም በዚህ መልካም ሥራ እንድንተባበር በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር የተባረከ የተቀደሰ ጉባኤ ያድርግልን
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ሚያዝያ 24 ቀን 2013 ዓ.ም ቅዱስነታቸው የትንሣኤ በዓልን አስመልክተው የሰጡት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያት ሁሉ፤

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ። የትንሣኤ በኲር፣ የሰላም መበሥር የሆነው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ፡፡
“ወመጽአ እግዚእ ኢየሱስ ወቆመ ማእከሌሆሙ ወይቤሎሙ ሰላም ለክሙ
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መጣ በመካከላቸውም ቆሞ ሰላም ለእናንተ ይሁን አላቸው።”
(ዮሐ. 2ዐ፥19)፡፡

ይህ ቃል ቅዱሳን ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ከተማ፣ቀራንዮ በተባለው ስፍራ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ በሆነው ነገር ሁሉ በኀዘንም በፍርሀትም ተውጠው በተዘጋ ቤት ውስጥ ሳሉ የተነገረ ቃለ ሰላም ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እሑድ እኩለ ሌሊት በኀይለ መለኮቱ ሞትንና መቃብርን ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ ለማርያም መግደላዊትና ለሌሎች ቅዱሳት አንስት በመጀመሪያ ተገልጾአል፡፡ ቀጥሎም በኤማሁስ ለሁለት ደቀ መዛመርቱ ተገልጾላቸዋል& በዚህ ቀን አመሻሹ ላይ ደግሞ ሐዋርያት በጽርሐ ጽዮን ሳሉ በሩም መስኮቱም እንደተዘጋ በአምላክነቱ ኀይል ገብቶ በድንገት በመካከላቸው በመገኘት “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ሲል የኋላ ኋላ የሕይወት ኀይል፣ የትንሣኤ ኀይል፣ የሰላም ኀይል አሸናፊ መሆኑን አብሥሮአቸዋል፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከትንሣኤው በኋላ ለደቀ መዛሙርቱ ያሰማው ዐቢይ ኀይለ ቃል ሰላም ለእናንተ ይሁን የሚለው አጽናኝ ቃል ነው፡፡

በእርግጥም በዚያች ቀውጠኛ ሳምንት ለሐዋርያት ከሰላም የበለጠ የሚያስፈልጋቸው ሌላ ነገር አልነበረም፤ ምክንያቱም ቅዱሳን ሐዋርያት ሰላም ከማጣታቸው የተነሣ ዕለታዊ ተግባራቸው ከመቋረጡም በላይ ሕይወታቸውም ከባድ ሥጋት ላይ በመውደቁ በአንድ ቤት በመሰባሰብ በሩንም መስኮቱንም ክርችም አድርገው በመዝጋት ራሳቸውን መሠወር መርጠዋል፡፡ ታድያ በዚህ ጊዜ ነበረ የሰላም ባለቤት የሆነው መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ መጣ በዚህ ገባ ሳይባል መስኮቱና በሩ እንደተዘጋ ድንገት በመካከላቸው ተገኝቶ የሰላምን ቃል ያሰማቸው ቅዱሳን ሐዋርያትም አጥተውት የነበረውን የሰላም ድምፅ በመስማታቸው እጅግ ደስ አላቸው፤ ፍርሀታቸው ተወገደላቸው፤ ፍጹም ሰላምና ነፃነትም በውስጣቸው አበራ& የተማመኑበት ጌታ ሞትና መቃብር ይዘው የማያስቀሩት መሆኑን በተግባር ሲያዩ ጭንቀቱና ሥጋቱ ሁሉ ስፍራውን ለቀቀ፤ በምትኩም ደስታው፣ በጌታ መታመኑና ሰላሙ ውስጣቸውን ሞላው፤ ነገሮች በቅጽበት ተለዋውጠዋልና የተዘጋውን በር ራሳቸው ከፈቱት፤ ከዚህ ቀን ጀምሮ የጌታን ትንሣኤ ለመመስከርና ለዓለም ሁሉ ለማድረስ አንድ ብለው ጒዞውን ለመጀመር በልበ ሙሉነት ዝግጁ ሆኑ፤ የጌታችን መሰቀል መሞትና መነሣት በመመስከሩና በማስተማሩ ረገድ በዚህ ዓለም ሊገድባቸው የሚችል ኀይል እንደማይኖር እርግጠኞች ሆኑ፤ በአካላቸው ላይ ሊቃጣ የሚችል መከራ ሁሉ ከቊጥር ላለማስገባት በሕሊናቸው ደመደሙ፤ በሂደትም ይህንን በተግባር አሳዩ፣ ይህንን ሁሉ ድፍረትና ቈራጥነት የሰጣቸው ሌላ ሳይሆን የትንሣኤው ኀይል እንደ ነበልባለ እሳት ግሎ በልቡናቸው ውስጥ በመቀጣጠሉ ነበር፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤

ከጌታችን ትንሣኤ በፊት የነበረው ፍርሐትና ሥጋት ዛሬም ከዓለማችን አልወጣም፤ ዛሬም ሰዎች ውስጣዊም ሆነ ውጫዊ ሕይወታቸው በፍርሀት በጭንቀትና በሥጋት እንደተከበበ ነው፡፡ ዛሬም ልክ ሐዋርያት እንደነበሩበት ዝግ ቤት ቤታቸውን የዘጉ፣ አሊያም ጥለው የሸሹ፣በመካከላቸውም ሕይወታቸውን ያጡ፣ሕይወታቸው ቢተርፍም የሚላስ፣ የሚቀመስ፣ የሚጐረስ፣ የሚለበስ፣ ያጡ ብዙ ናቸው፡፡ ከዚህ አኳያ ሰዎች ነንና ይህ ለምን ሆነ ብለን ልንጠይቅ ተፈጥሮና ሃይማኖት ያስገድዱናል፤ መልሱ ግን አንድና አጭር ነው፡፡ እሱም ሰላም በመጥፋቱ ነው፡፡ ይህንን ሰላም ያጣነው በሌላ ሳይሆን በእኛው በራሳችን ነው፤ መፍትሔ የሌለው ነገር ያለ ይመስል ቁጭ ብለን በአንድነትና በጋራ ተወያይተን ችግራችንን መፍታት አቅቶን ያመጣነው ጣጣ ነው፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔር የሰጠንን ብሩህ አእምሮ ተጠቅመን የራሳችንን ችግር በራሳችን መፍታት ካልቻልን በማንም ይሁን በማን ብናመካኝ የሚቀበለን አናገኝም፤ እግዚአብሔር እንደሆነ በተፈጥሮም ሆነ በቅዱስ መጽሐፉ የሰላም መገኛዋና መጠበቂያዋ ዕርቅና ይቅርታ እንደሆነ ባለማወላወል ነግሮናል፡፡ እሱ ያለውን የማንቀበል ከሆነ እኛን በሚቀጣበት ሥልጣኑ ቀጥቶ በኀይለ መለኮቱ ሰላሙን ለድሆቹ ፍጡራን ያጐናጽፋል&ይህ የእግዚአብሔር አሠራር ስለሆነ እሱም አያልፈውም እኛም አናስቀረውም፤ ነገር ግን ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚመክረን እሱ ሳይፈርድብን በይቅርታና በዕርቅ እኛው በእኛው ላይ ብንፈርድ ትልቅ ጥበብና ብልኅነት ነው&አሁንም የእኛ ቀን የጨለመ ቢመስልም ለእግዚአብሔር ቀኑ ሁሉ አይጨልምምና ኢትዮጵያውያን ልጆቻችንና ወገኖቻችን እባካችሁ ሁሉን ነገር እርግፍ አድርገን በመተው ለዕርቅና ለሰላም፣ ለይቅርታና ለአንድነት፣ ለእኩልነትና ለወንድማማችነት ያለ ማቋረጥ ብንተጋ መልካምና ጣፋጭ የሕይወት እሸት እንቀምሳለን፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤

የሰው ልፋት ምንም ቢበዛ እግዚአብሔር ካልፈቀደው የሚሆን እንዳልሆነ የምንዘነጋው አይደለም፤ እግዚአብሔርን ፊት ለፊታችን አድርገን የማንሠራው ሥራ ሁሉ ብላሽ እንደሆነ የምንገነዘበው እግዚአብሔርን ከፊት ለፊታችን ገለል አድርገን ለብቻችን የሮጥንባቸው የዓመታት ጒዞ የት እንዳደረሱን በአእምሮአችን አስተውለናል& በዓይናችንም አይተናል፣ በጆሮአችን ሰምተናል፤ ከእግዚአብሔር ኮብልለን ማምለጥ እንደማንችልም ከኛ በላይ ሌላ ምስክር አያስፈልገንም&ለእኛ ያሉን ተመራጭና ብቸኛ ዕድሎች እግዚአብሔርንና ሰላም፣አንድነትና እኩልነት፣ ዕርቅና ይቅርታ ብቻ ናቸው፡፡ ከዚህ ውጭ ምንም ተመራጭ ዕድል የለንም&ጌታችንም በትንሣኤው ዕለት ሰላሙን በቃለ ብሥራት ያበሠረን ከሰላም የተሻለ እኛን የሚጠቅም ሌላ አማራጭ እንደሌለ ስለሚያውቅ ነው፡፡

በመጨረሻም በዓለ ትንሣኤውን ስናከብር በሰላም ዕጦት ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው በየመጠለያው የሚገኙ ልጆቻችንና ወገኖቻችንን በመመገብ፣ በማጠጣትና&በማልበስ ከኛ ጋር የፋሲካውን በዓል በመጽናናት እንዲያሳልፉ ሁሉም ሕዝበ ክርስቲያን የበኩሉን ድጋፍ እንዲያደርግ፣ ከዚህ ጐን ለጐንም ሰላም እንዲሰፍን የሰላም ኀይሎች ሁሉ የበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉ፣እግዚአብሔርንም ለሰላማችን መረጋገጥ መለኮታዊ ሥራውን እንዲሠራ እንድንማፀነው አባታዊና መንፈሳዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

መልካም በዓለ ትንሣኤ ያድርግልን!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር