ከግንቦት 05 ቀን እስከ ግንቦት 06 ቀን 2012 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቍጥር 164 ድንጋጌ መሠረት ከግንቦት 4 እስከ ግንቦት 6 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ የተካሄደውን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ውሳኔዎች፤

1. በዓለማችንና በሀገራችን በኢትዮጵያ ጭምር ከቅርብ ወራት ወዲህ የተከሠተው የኮረና ቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝ እስከ አሁን በብዙ ሚሊየን የሚቈጠሩ ሰዎችን በመያዙና ከመቶ ሺሕዎች ላላነሱ ሰዎች ሕይወት መጥፋት ምክንያት በመሆኑ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤን በእጅጉ ያሳዘነ ሲሆን ጉባኤው፣ በቫይረሱ የተጠቁትን ምሕረት እንዲሰጥልን እስከ አሁን በቫይረሱ ያልተጠቁትንም እንዲጠብቅልን ተማሕፅኖውን ለእግዚአብሔር አቅርቧል፡፡
2. ይኸው ተላላፊና የሰው ልጆችን በሞት እየነጠቀ ያለውን ቫይረስ እግዚአብሔር አምላክ በምሕረቱ እንዲያጠፋልን ምእመናን እንደ አንድ ልብ መካሪና እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ በመሆን እንዲጸልዩ ተይዞ የነበረውን የሱባዔ ጊዜ በአግባቡ መከናወኑን ጉባኤው ተገንዝቦ ለወደፊቱም ካህናትም ሆኑ ምእመናን ወደ እግዚአብሔር የሚያደርጉትን ጸሎት በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በቤታቸው አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጉባኤው አበክሮ አሳስቧል፡፡
3. በዚሁ ወረርሽኝ መከሠት ምክንያት በየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ የሚሰጠው መንፈሳዊ አገልግሎት መቋረጡ በምእመናን ሕይወት ላይ ችግር እየፈጠረ መሆኑና ምእመናን ከቤተ ክርስቲያን ተለይተው መኖር ስለማይችሉ በቀጣይም የሕዝቡን ጤና መጠበቅ በሚያረጋግጥ መልኩ የሚመለከታቸው የሃይማኖት አባቶች እና የጤና ባለሙያዎች በሚሰጡት ሙያዊ ምክርና መንግሥትም በሚሰጠው መመሪያ መሠረት አሁንም የአካላዊ ርቀትና ንጽሕና አጠባበቅ ከምንጊዜውም በላይ ትኵረት ተሰጥቶት፣ ለዚሁ ተግባር በየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ በተመደቡ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች አስተናጋጅነት ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ እንዲከናወን፣
4. ሀገራችን ኢትዮጵያ ሀገረ እግዚአብሔር፣ ሕዝቧም ሕዝበ እግዚአብሔር እየተባለ እንደሚጠራ ይታወቃል፡፡ መጠራትም ብቻ ሳይሆን ሕዝባችን በፈሪሀ እግዚአብሔር ተከባብሮ እንኳን የራሱ የሆነውን ወገኑን ቀርቶ ሌላውን እንደራሱ አድርጎ የሚወድ፣ ያለው ከሌለው ጋር የሚካፈልና በደግነቱ የሚታወቅ ሕዝብ መሆኑን ዓለም የሚመሰክረው ነው፡፡ በመሆኑም ይህ የደግነት ምሳሌነታችን በተለይም በዚህ የኮረና ቫይረስ ወረርሽኝ በጸናበትና ሁሉም ወገን የችግሩ ተጋላጭ ሆኖ በተገኘበት በአሁኑ ጊዜ ያለውን ለሌለው በማካፈል ይበልጥ ደግነታችን ጐልቶ እንዲታይ የሚያስፈልግበት ወቅት ላይ እንደምንገኝ የተገነዘበው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ሁላችንም ባለን ነገር ሁሉ በመረዳዳት ይህን ፈታኝ ጊዜ እንድናልፈው ጥሪውን ያቀርባል፡፡
5. ከዚህም ጋር ዜጋው እንደ ሀገር በሁለት እግሩ ቁሞ ህልውናው ተጠብቆ ሊኖር የሚችለውና ሀገራዊ ልማትም ሆነ ሕዝባዊ እድገት ሊመጣ የሚችለው በሁሉም ዘንድ ሰላምና አንድነት መግባባትም ጭምር ሲኖር እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ሆኖም በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን በፖለቲካ ድርጅቶች መካከል እየታየ ያለው አለመግባባትና የቃላት መወራወር በአጭሩ ካልተገታና ወደ መግባባት በመምጣት መፍትሔ ካልተበጀለት ተጨማሪ ሀገራዊ ቀውስ ሊያስከትል፣ ከፍተኛም ዋጋ ሊያስከፍል እንደሚችል በመገንዘብ የሚመለከታችሁ የፖለቲካ ድርጅቶች ሁሉ ለሀገራዊ ሰላምና ለሕዝባዊ አንድነቱ በጋራ እንድትቆሙ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ያቀርባል፡፡
6. ሀገራችን ኢትዮጵያን ለከፍተኛ እድገት ያበቃል ሕዝባችንን ከድህነት አረንቋ ያወጣል በሚል እምነት ከረጅም ጊዜ አንሥቶ ሕዝባችን ትኵረት ሰጥቶ ምንም ሳይኖረው ጦሙን እያደረ አስተዋፅኦ በማድረግ እዚህ ደረጃ ላይ ያደረሰው የሕዳሴ ግድባችን አብዛኛው የግድቡ ሥራ እየተጠናቀቀና ወደ ፍጻሜውም እየደረሰ መሆኑን ስለተገለጸ ጉባኤው በከፍተኛ አድናቆት ተመልክቶታል፡፡ በቀጣይም የግድቡን ፍጻሜ ለማየት፣ የመላውን ሕዝባችን ርብርብ እንደሚጠይቅ ግንዛቤ የተወሰደ በመሆኑ እንደአባቶቻችን ለትውልድ የሚተርፍ ታሪክ ለመሥራት ሕዝባዊ አንድነቱና ተሳትፎው እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡

በመጨረሻም ከግንቦት 4-6 ቀናት በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ማኅበራዊ፣ እንዲሁም ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ሲነጋገር የቆየው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ተጠናቅቆ በዛሬው ቀን በጸሎት ተዘግቷል፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

ግንቦት 05 ቀን 2012 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣

በየተሰማራንበት ሁሉ እግዚአብሔር እየረዳን መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና የምግብና ሥራችንን እየተወጣን ከቆየንበት ሀገረ ሰብከት በሰላም አምጥቶና አንድ ላይ አሰባስቦ ስለ ሃይማኖታችንና ስለሀገራችን ለመወያየት የሰበሰበን እግዚአብሔር አምላካችን ስሙ የተመሰገነ ይሁን፡፡

“ትግሁ ወጸልዩ ከመ ኢትባኡ ውስተ መንሱት፤ ወደፈተና እንዳትገቡ ተግታችሁ ጸልዩ” (ማቴ-6፡1)፡፡ ፈጣሬ ፍጥረታት እግዚአብሔር ሕዝቡን የሚወድ ብቻ ሳይሆን ከሕዝቡ መለየት የማይፈልግ አምላክ ነው፣ የእግዚአብሔር መኖሪያ በሰው እጅ በተሠራው ቍሳዊ ነገር ሳይሆን እሱ ራሱ በሠራው በሰው ልቡና ስለሆነ፣ ከሰው ጋር መገናኘት የሚፈልገውም በዋናነት በዚሁ ስፍራ እንደሆነ እሱ ራሱ ነግሮናል፤ ታዲያ እግዚአብሔር ከሰው ልቡና መለየት እንደማይፈልግ ሁሉ ሰውም ምንም ደካማ ቢሆንም ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር መለየት አይፈልግም፤ ይህም የጋራ ፍላጎት ሊከናወን የሚችለው በእምነትና በጸሎት ነው፡፡ ይህ ግንኙነት የደጋፊና ተደጋፊ ዐላማ ያለው ግንኙነት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችንን በዚህ መልኩ በጸሎት ስንቀርብ በቀላሉ እንደምናገኘው እናምናለን፤

“ወሀቦ ለልዑል ጸሎተከ ትጼውዐኒ በዕለተ ምንዳቤከ አድኅነከ ወተአኵተኒ — ጸሎትህን ለልዑል እግዚአብሔር አቅርብ፤ በመከራህ ቀን ትጠራኛለህ፤ እኔም አድንሃለሁ፤ አንተም ታመሰግነኛለህ” ሲል ቃል ገብቶልናል፡፡ ይህ ወቅት በመላ ክፍለ ዓለም ተሰራጭቶ የሚገኘው የኮረና ቫይረስ በሽታ ፍጥረተ ሰብእን በጠቅላላ ከባድ ሥጋት ላይ የጣለበት ወቅት ነው፤ “በእንቅርት ላይ—-” እንደሚባለው ሀገራችን በሌሎች ውስብስብ ነገሮች በተወጠረችበት ወቅት ይህ ዐይነቱ መድኀኒት የለሽ በሽታ መከሠቱ በሀገራችን ላይ ሥጋት እንዲበዛ አድርጓል፡፡

ይህ ወቅት ለሀገራችንም ለቤተ ክርስቲያናችንም ለሕዝባችንም ከባድ የፈተና ወቅት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ እንደ ትናንቱ የመሰለ አካሄድና አስተሳሰብ ጭራሽ የሚያስኬድ አይሆንም፤ እኛ ሊቃነ ጳጳሳት የሕዝበ እግዚአብሔር እረኞች ሆነን እዚህ ላይ የተሰበሰብነው ሕዝቡን በሁለንተናዊ ሕይወቱ ከፈተና ለመጠበቅ መሆኑን በውል የምንገነዘበው ነው፡፡ ይህ ሕዝብ በአሁኑ ጊዜ በብዙ መልኩ እየተፈተነ ነው፤ ሕዝቡ በሰላም ዕጦት የኅሊና ጭንቀት ላይ ነው የሚገኘው፤ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ በቀጣዮቹ ዓመታት በእጅጉ ሊጎዳ እንደሚችል የበሽታው ተጽዕኖ ምልክት እያሳየ ነው፤ የተከሠተው በሽታ መቼ ሊወገድ እንደሚችል የሚታወቅ ነገር የለም፤ ስለሆነም በዚህ ሁሉ ፈተና ተጎጂው ማን ነው? ሲባል እኛ እረኛ የሆንለት ሰፊው ሕዝብ በተለይም በዝቅተኛ ኑሮ የሚኖር ድሀው ሕዝባችነ ነው፡፡

ይህ ሕዝብ እየታዩ ባሉት ችግሮች በመከራ ቢለበለብ በእግዚአብሔር ዘንድ ያስጠይቀናል፤ ሕዝቡም ይታዘበናል፤ ይህም እንዳይሆን በተቻለ ዐቅም በጸሎትም፣ በትምህርትም፣ በምክርም፣ በማስታረቅም ሰፊ የማግባባትና የሕዝብ አድን ሥራ መሥራት አለብን፤ አሁን ያለው ጥያቄ ሀገርንና ሕዝብን ከፈተና የመታደግ ጥያቄ ነው፤ ይህንን ፈተና መሸጋገር የምንችለው በአንድነት ሆነን ስንቆም ብቻ ነው፤ አንድነትን ለማምጣት ደግሞ የማግባባት ሥራ የግድ መሥራት አለብን፤ በዚህ ጉዳይ ላይ ይህ ጉባዔ በጥልቀትና በአጽንዖት ተወያይቶ ወደ ተጨባጭ ሥራ እንዲገባ ያስፈልጋል፡፡

ሕዝባችን በውስጣዊና አካባቢያዊ የአስተሳሰብ ልዩነት ምክንያት ብዙ ውጣ ውረድ ባለበት ወቅት ተጨማሪ ሸክም ሆኖ የመጣብንን የኮረና በሽታም በአጭር ታጥቀን ሕዝቡን በማስተማር፣ በጸሎት በመትጋትም ክፉውን ቀን በሰላም እንድናሸጋግረው ጠንክረን መሥራት አለብን፡፡ እስከ አሁን ድረስ ቤተ ክርስቲያናችን፣ ሌሎች አብያተ ሃይማኖት፣ መንግሥትና ሕዝብ፣ እንደዚሁም የተለያዩ የሚድያ አውታሮች በጋራ ሆነው በሠሩት ሥራ ቢያንስ የወረርሽኙ በሽታ የከፋ አደጋ እንዳያደርስ በመከላከላቸው በዚህ አጋጣሚ ሳናመሰግን አናልፍም ለወደፊቱም በዚሁ እንዲቀጥል በጋራ እየተባበሩ መሥራቱን ማጠናከር ይኖርብናል፡፡

በመጨረሻም፡ ሁላችንም እንደምናየውና እንደምንገነዘበው በሀገራችን እየተከሠቱ ያሉት የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ችግሮች ሁሉ መንግሥትና የፖለቲካ ተፎካካሪ ፓርቲዎች እግዚአብሔርና ታሪክ የጣለባችሁን አደራ በላቀ አስተውሎት ነገሩን በማጤን ሀገርንና ሕዝብን በሰላም፣ በጤና እና በአንድነት የማሻገር ከፍተኛ ኀላፊነት በእጃችሁ እንዳለ አውቃችሁ ይህንን ሕዝብና ሀገር ወደ ተሻለ አስተማማኝ ሰላም፣ ጤንነትና እድገት በፍቅርና በአንድነት ሁናችሁ እንድታሸጋግሩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አደራ ትላችኋለች፡፡ በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምን ጊዜም ከሕዝቡ ጎን መሆኑን እየገለጽን የሁለት ሺ ዐሥራ ሁለት ዓመተ ምሕረት የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባዔ በዛሬው ዕለት መከፈቱን እናበሥራለን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!