ጥር 11 ቀን 2012 ዓ.ም የጥምቀት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
“ሀለወክሙ ትትወለዱ ዳግመ
ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል፤”
(ዮሐ. 3፥7)
ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ልደትንና አስፈላጊነቱን አስመልክቶ ያስተማረው ተቀዳሚ ትምህርት በዚህ ምዕራፍ ተጽፎ ይገኛል፡፡ ጌታችን በዚህ ትምህርቱ የልደት ዐይነት ሁለት እንደሆኑ እነሱም ሥጋዊና መንፈሳዊ ልደት እንደሚባሉ በአጽንዖት አስተምሮአል፡፡ ሥጋዊ ልደት ሰው ሁሉ ከእናቱና ከአባቱ በግዘፍ የሚወለደው ነው፤ ይህ ሁሉም የሚያየውና የሚያውቀው ስለሆነ ተጨማሪ ማብራርያ አያስፈልገውም፤ መንፈሳዊ ልደትን በምንመለከትበት ጊዜ ግን እንደ ስሙ መንፈሳዊ ወይም ረቂቅ ስለሆነ ማስተዋልን በእምነት መነጽር መመልከትን ይጠይቃል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ አስተምህሮው ሰው ሁሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የሚገባበትን ምሥጢር ገልጾአል፤ ቅዱስ መጽሐፍ ደጋግሞ እንደሚያስተምረን ሰው ለክብር የተፈጠረ ታላቅ ፍጡር ነው፤ ይህንንም ማስተዋል የምንችለው ከሰው በቀር በእግዚአብሔር መልክና አምሳል የተፈጠረ ፍጡር በሰማይም ሆነ በምድር የሌለ በመሆኑ ነው፤ ይህ መልክና አምሳል ውጫዊውን የመልክ ገጽታ ብቻ የሚያሳይ ሳይሆን በእግዚአብሔርና በሰው መካከል ያለውን ጥብቅ ግንኙነት የሚያመለክት ነው፤ ይህ ግንኙነት በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ በአባትና በልጅ፣ በባልና በሚስት፣ በወይን ግንድና በቅርንጫፍ ወ.ዘ.ተ… ምሳሌነት ተገልጾአል፡፡ እግዚአብሔር ሰውን አክብሮና ከራሱ ጋር አስተሳስሮ የፍጡራን ሁሉ አዛዥና አስተናባሪ አድርጎ እንደዚሁም በምድር ላይ ብቸኛ የእግዚአብሔር ምስለኔና እንደራሴ አድርጎ መሾሙ በቅዱስ መጽሐፍ ተጽፎአል፡፡
ይሁን እንጂ ይህ ግንኙነት በምክረ ሰይጣን ስለተቋረጠ ሰው በጣም አሳዛኝ በሆነ ሁኔታ ወደቀ፤ በዚህም ውድቀት የሰው ሁለንተና ሕይወቱ ተናጋ፤ ሥጋዊ ሕይወቱ በመከራ አረም ሙሉ በሙሉ ከመዋጡም ሌላ፣ ንጹሕ አእምሮው ተቃወሰ፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ መውጫውንና መግቢያውን ትንፋሹንም ጭምር ከያዘና ሁሉን ከሚችል ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር ልጅነት ተገለለ፤ ህላዌው ሁሉ በጨለማ የተዋጠ ሆነ፤ ሰው በዚህ ዓለም የሚቆይበት ሕይወት ተጠናቅቆ ሥጋው ወደ መቃብር ሲወርድ ነፍሱ ደግሞ ወደ መከራና ሥቃይ ቦታ ወደ ሲኦል ጒድጓድ መጣል ዕጣ ፈንታው ሆነ፡፡ ይህ ሁሉ አሰቃቂ ሕይወት ሊከሠት የቻለው ሰው የእግዚአብሔርን ምክር ንቆና ትቶ፣ የሰይጣንን ምክር አምኖና ተቀብሎ በፈጸመው ስሕተት ጠንቅ ነው፤ የበደለን መቅጣት፣ የታመነን መሸለም በፍጡር የማይጣስ ሕገ መለኮት ነውና ጥፋተኛ የሆነው የሰው ልጅ ከመቀጣት በቀር የሚያገኘው ሽልማት አልነበረውም፤ ሰውም ያለውድ በግድ ቅጣቱን ተቀብሎ መራራ ኑሮውን በሰማይም በምድርም ቀጠለ፤ ይህ ሁኔታ ጌታችን በሞቱ እስኪያስወግደው ድረስ ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመናት ያህል ዘልቆአል፤ ከጌታችን ሞት በኋላ ግን ለሰው ልጆች እንደገና አዲስ ጒዞ ተጀምሮአል፤ እሱም በጌታችን ደም የሰው ልጅ በደል በመሠረዙ ምክንያት ከሞት በኋላ የሰው ነፍስ ጒዞ ወደ ሲኦል ጉድጓድ ሳይሆን ወደ ገነት ሆኖአል፤ ይህንንም ጌታችን በመስቀል ላይ ሳለ አምኖ ንስሐ ለገባው ወንበዴ “ ዛሬውኑ ከኔ ጋር በገነት ትኖራለህ” ባለው የማይሻር ቃሉ አረጋገጠው፤ በገነት መኖር ማለት አዳም ከመውደቁ በፊት ወደ ነበረው ጣዕመ ሕይወትና ቦታ እንደገና መመለስ ማለት ነው፡፡
እንግዲህ በአሁኑ ጊዜ የሰው ልጅ ሁሉ ትልቁ ጥያቄ ይህንን ገነታዊ ጣዕመ ሕይወት እንዴት እናግኝ የሚል ነው፤ ጥያቄው ትክክለኛና የአስተዋይ ሰው ሁሉ ጥያቄ ነው፤ ነገር ግን ጥያቄው የዛሬ ሁለት ሺሕ ዓመት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አስተምህሮ አጥጋቢና እውነተኛ መልስ ያገኘ በመሆኑ እሱን በሚገባ መረዳትና መፈጸም ያሻል፡፡ ጌታችን አንድ የአይሁድ መምህርና ዐዋቂ፣ ሊቅና አስተዋይ ካቀረበው ጥያቄ ተነሥቶ ሲመልስ፡-“ እውነት እውነት እልሃለሁ፡- ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያያትም” ብሎአል፤ ጌታችን በዚህ ትምህርቱ የእግዚአብሔር መንግሥት በማለት የገለጸው ቦታ፣ ቃል ሊገልጸው ከሚችል በላይ ለኑሮ በጣም ምቹ የሆነና ራሱ በመስቀል ላይ ሳለ ገነት በሚል ስያሜ የጠራው ቦታ ነው፤ ማንኛውም ሰው ወደዚህ ቦታ ለመግባት ከሁሉ በፊት ዳግመኛ መወለድ ያስፈልገዋል፡፡ ዳግመኛ ካልተወለደ ግን መግባት ይቅርና በዐይን አሻግሮ ማየት እንኳ አይችልም፤ ጌታችን አያያትም ብሎአልና፡፡ ከዚህ አንጻር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት የሚቻለው እንዴት ነው ለሚለው ጥያቄ መልሱ “ዳግመኛ በመወለድ ነው” የሚል መልስ ከጌታችን ተሰጥቶአል፤ ነገር ግን አእምሮው ውሱን የሆነው የሰው ልጅ አሁንም ጥያቄውን በማራዘም ሰው ካደገ በኋላ እንደገና ተመልሶ ወደ እናቱ ማሕፀን ሊገባና ዳግመኛ ሊወለድ እንዴት ይችላል በማለት ጠይቆአል፤ነገር ግን ጌታችን ለዚህም ሰፊ ማብራሪያና መልስ ጥልቅ ትምህርትም ሰጥቶአል፡፡ ጌታችን ይህንን አስመልክቶ በሰጠው ትምህርት ሰው ዳግመኛ ለመወለድ እንደገና ወደ እናት ማሕፀን መግባት አያስፈልገውም፤ ዳግመኛ መወለድ የሚቻለው ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ነው ብሎአል፡፡
ጌታችን ዳግመኛ መወለድ የሚቻለው ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ነው ሲል፣ በውኃና በመንፈስ ቅዱስ በመጠመቅ ዳግመኛ መወለድ ይቻላል ማለቱ እንደሆነ ግልጽ ነው፤ እግዚአብሔር በጌታችን ሞት መነሻነት በዘረጋው ሰዎችን የማዳን አሠራር ሰዎች በፍጹም ልባቸው ሲያምኑ፣ በውኃ ሲጠመቁና በመንፈስ ቅዱስ ሲቀቡ ዳግመኛ ተወለዱ ማለት ነው፤ ዳግመኛ ልደት የሚፈጸመው በዚህ አኳኋን ነው፤ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት ዳግመኛ መወለድ ለምን አስፈለገ የሚል ጥያቄ ቢነሣ፣ ከሁሉ በፊት ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት ከኀጢአት መንጻት አለበት፤ ከዚያም በመንፈስ ቅዱስ ከብሮ መታተም አለበት፤ይህ ሲፈጸም እግዚአብሔር ተጠማቂውን ሰው በልጅነት ይቀበለዋል፤ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ተጠማቂው ሰው የእግዚአብሔር ልጅና የእግዚአብሔር የሆነውን ሁሉ ወራሽ ነው ማለትም የእግዚአብሔር የሆነውን መንግሥተ ሰማያትንና በውስጡ የሚገኙ ሕይወታዊ ስጦታዎችን ሁሉ ያገኛል፤ ይወርሳልም፤ በአንጻሩ ደግሞ ማንኛውም ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው የእግዚአብሔር ልጅ መሆን አይችልም፤ በመንግሥተ ሰማያትና በውስጡ ያሉትን ስጦታዎችም ሊያገኝ አይችልም፤ ምክንያቱም ሰውየው ከሥጋ ብቻ የተወለደ ሥጋዊ እንጂ ከመንፈስ ያልተወለደ ነው፤ ከመንፈስ ሳይወለድም የመንፈስ የሆነውን ነገር ሊያገኝ አይችልም፤ ምክንያቱም ከሥጋ፣ የተወለደ ሥጋ፣ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና የመንፈስ የሆነውን ነገር ለማግኘት ከመንፈስ መወለድ የግድ ስለሆነ ነው፤ በዚህ ምክንያት ከውኃና ከመንፈስ መወለድ ግድ በመሆኑ ጌታችን ትምህርቱን ሲያጠቃልል “ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል” ብሎ አትሞአል፡፡
ሰው በጥምቀት የሚያገኘው ሰማያዊ ሀብተ ርስት ይህን ያህል ታላቅና ለሰው ልጅ ሁሉ አስፈላጊ በመሆኑ ጌታችን ራሱ ለሁላችን መሪና አርኣያ በመሆን በእደ ዮሐንስ፣ በፈለገ ዮርዳኖስ ተጠምቋል፡፡ ጌታችን በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀ ጊዜ ሰማይ ተከፍቶአል፤ መንፈስ ቅዱስም በነጭ ርግብ አምሳል ከሰማየ ሰማያት ወርዶ በላዩ ተቀምጦአል፤ አብም በደመና ሆኖ “ይህ የምወደው ልጄ ነው” ሲል መስክሮአል፡፡ ይህ ክሥተት በእግዚአብሔር ማንነትና በሰው ልጅነት ምሥጢር ላይ ያነጣጠረ እውነታ እንደሚያንጸባርቅ ከድርጊቱ መረዳት ይቻላል፤ ይኸውም ከእግዚአብሔር ማንነት አንጻር ሲታይ እግዚአብሔር ሦስት አካላት እንዳሉት፣ የአካላት አስማትም አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ እንደ ሚባሉ፣ በእግዚአብሔር ዘንድ አባት፣ ልጅ፣ መንፈስ፣ የሚባሉ ሦስት ህልዋን አካላት እንዳሉ ግልጽ ሆኖአል፡፡ ከሰው ልጅነት አንጻር ሲታይ ደግሞ ሰው አምኖ ሲጠመቅ እግዚአብሔር በልጅነት እንደሚቀበለው፣ ሰማያዊ በሩንም ከፍቶ ወደ ዘለዓለማዊ መንግሥቱ እንደሚያስገባው ክሥተቱ ያመለክታል፤ በመሆኑም የእግዚአብሔር ማንነት ማለትም አንድነቱ እና ሦስትነቱ የተገለጸበት፣ የጌታችንም የልጅነቱ ክዋኔ የተረጋገጠበት፣ በዚያው አንጻርም የሰው መንፈሳዊ ልደት የተመሠጠረበት ዕለት በመሆኑ በዓለ ጥምቀት በግሪክ ቋንቋ ኤጲፋንያ፣ በግእዝ አስተርእዮ፣ በአማርኛ መገለጥ ይባላል፡፡ ምክንያቱም በዓለ ጥምቀተ ክርስቶስ እግዚአብሔር ስለራሱ ማንነት፣ ስለክርስቶስ አምላክነት እንደዚሁም ስለ ሰው ልጅ ልጅነት የተገለጠበትና እግዚአብሔር ወሳኝ መልእክቱን ያስተላለፈበት ዕለት ነውና፡፡
በሌላ በኩል ጥምቀት ለሰው ልጆች ድኅነት በጣም ወሳኝ ነገር መሆኑን ከምናውቅባቸው ዐበይት ነገሮች መካከል፣ ጥምቀት ለጌታችን ትምህርት መነሻና መድረሻ ወይም ርእስና መደምደሚያ ሆኖ መሰጠቱ ነው፤ ጌታችን የማዳን ትምህርቱንና ሥራውን የጀመረው በዕለተ ጥምቀት፣ በፈለገ ዮርዳኖስ በፈጸመው ድርጊት ነው፤ ያጠናቀቀውም ሊያርግ ሲል በአስተላለፈው ገዢ የጥምቀት ትምህርት ነው፤ ይኸውም ጌታችን ሞትንና መቃብርን ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ ወደ ሰማይ የሚያርግበት ቀን ሲቀርብ፣ ለደቀ መዛሙርቱ ያስተላለፈው የመጨረሻ ትእዛዝና ትምህርት “አሕዛብን ሁሉ አስተምሩ፤ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስምም አጥምቋቸው፤ ያመነ የተጠመቀ ይድናል፤ ያላመነ ግን ይፈረድበታል” የሚል ነው፤ ስለሆነም ጌታችን ትምህርቱን የጀመረና ያጠናቀቀ በነገረ ጥምቀት መሆኑን ስናስተውል፣ ጥምቀት ለድኅነታችን ያለው ቦታ ከፍተኛ መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ እንግዲህ ጥምቀት የድኅነታችን ቊልፍ ምስጢር መሆኑን ካየን ከእኛስ ምን ይጠበቃል የሚለውን ማየት ይኖርብናል፤ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን የሰው ልጅ ድኅነት የሁለትዮሽ ውጤት ነው፤ ይህም ማለት በእግዚአብሔርና በሰው ጥምር ተግባር የሚከናወን ነው ማለት ነው፤ ሰዎች ወደዱም ጠሉም፣ ተቀበሉም አልተቀበሉም ይህ የእግዚአብሔር መለኮታዊ አሠራር ነው፤ ጌታችን ሰዎችን ከልዩ ልዩ በሽታ ሲፈውስ በራሱ ፈቃድ ብቻ አልነበረም፤ የበሽተኛው ፈቃድም የተጠበቀ ነበረ እንጂ፤ ለመዳን በሽተኛው ቢያንስ ፍላጎቱን ወይም ዝንባሌውን ማሳየትና መግለጽ ይጠበቅበታል፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን ልትድን ትወዳለህን ? ይህንን እንደማደርግ ታምናለህን? ምን ላደርግልህ ትወዳለህ? እያለ ሰዎችን ሲጠይቅ የምናየው፤ ጌታችን ይህንን የሚያደርገው እውን ሰዎች የሚፈልጉትን የማያውቅ ሆኖ ነውን? ወይስ የሚጠቅማቸው ምን እንደሆነ ያውቅ የለምን? ለምን ይጠይቃቸዋል ተብሎ ቢጠየቅ መልሱ ያውቃል ነው፤ ነገር ግን በእርሱ ዘንድ የሰው ኅሊናዊ ነፃነት የተጠበቀ መሆኑንና ምርጫው የግለሰቡ መሆኑን፣ መዳን ቢሆንም ከምርጫው ውጭ በግድ መፈጸም አግባብ አለመሆኑን ለማሳየት እየጠየቀና እያስፈቀደ ያድን ነበረ፡፡
ይህ ሁሉ የሚያስገነዝበን ነገር ቢኖር መዳን በዳኑና በአዳኙ የጋራ ፈቃድ የሚከናወን መሆኑን ነው፡፡
ይህም ማለት ፍላጎት፣ ዝንባሌ፣ ተነሳሽነት፣ ታዛዥነትና በእምነት ራስን ለእግዚአብሔር ንጹሕ መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ ከሰው ይፈለጋል፤ በይቅርታና በምሕረት ተቀብሎ ማንጻት ማክበርና ተጠማቂውን በልጅነት መቀበል ደግሞ ከእግዚአብሔር ይጠበቃል፤ እነዚህ አንድ ላይ ተጣምረው ሰውን ለድኅነት ያበቁታል ማለት ነው፤ እንግዲህ የድኅነት መንገድ ይህ ከሆነ እያንዳንዳችን ክርስቲያኖች እኔስ የት ነው ያለሁ ብለን ራሳችንን በራሳችን መጠየቅና ያለንበትን ተጨባጭ ሕይወት የት እንደሆነ ማወቅ ይገባናል፤ ሕይወታችንን በዚህ አቅጣጫ ካየነው ያለንበትን ሁኔታ በትክክል እንድናውቅ ያደርገናል፤ ማወቅ ብቻም ሳይሆን በንስሐ እየታደስን ለእግዚአብሔር ልጅነታችን በሚመጥን ሃይማኖትና ሥነ ምግባር ጸንተን እንድንኖር ያስችለናል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጥምቀትን በዓል በየዓመቱ በታላቅ ሥነ ሥርዐት የምታከብረው ይህንን የመዳን አስተምህሮ እንዳይረሳና የሰው ልጆች ወደ አጥፊ ጎዳና እንዳይጓዙ ለማድረግ ነው፤ ስለሆነም የጥምቀትን በዓል ስናከብር የመዳናችንን ነገር በማሰብ፣ በእሱ ለመጠቀምም የኅሊና ዝግጅት በማድረግና እሱን ለመተግበር ቁርጥ ውሳኔ በማሳለፍ እንጂ ሥነ በዓሉ ስለማረከን፣ ወይም ባህላዊ ገጽታው ስለሚስብ፣ ወይም ሆታውና እልልታው፣ መዝሙሩና ግብዣው ስለናፈቀን መሆን የለበትም፤ የእግዚአብሔር ፈቃድ አንድ ስንኳ እንዳይጠፋ ነውና እንደፈቃዱ መኖር ይገባናል፤ የፈቃዱ ተጋሪዎች በመሆንም ራሳችንን ከጥፋት ለማዳን ዘወትር መትጋት ይኖርብናል፡፡
መልካም የጥምቀት በዓል እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡