መስከረም 16 ቀን 2012 ዓ.ም በመስቀል ደመራ በዓል ላይ የተላለፈ መልእክት
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
ከመስቀሉና ከቃሉ የተነሣ አባቶቻችንን በክብርና በዘለዓለማዊ ሕይወት ከፍ ከፍ ያደረገ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ!!!
“በመስቀሉ ወበቃሉ አዕበዮሙ ለአበዊነ፤
በመስቀሉና በቃሉ አባቶቻችንን ከፍ ከፍ አደረጋቸው።”
(ቅዱስ ያሬድ)
የክርስትና ሃይማኖት እምነትና አስተምህሮ መሠረታዊ ይዘት ድኅነተ ዓለም በክርስቶስ መስቀል ተፈጽሞአል፤ ወደፊትም ይፈጸማል የሚል እንደሆነ ሁሉም የሚያውቀው ነው፡፡ የጌታችን ግብረ አድኅኖ ፍጹም እንደመሆኑ መጠን ወደኋላም ወደፊትም ያሉትን ሁሉ ያካተተ እንደሆነ በቅዱስ መጽሐፍ ተረጋገጦአል፡፡ በፍዳ ኀጢአት ተግዘው ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመናት በግዞት ይማቅቁ የነበሩ ነፍሳተ አበው በአጠቃላይ በመስቀል ላይ በተፈጸመው የቤዛነት መሥዋዕት ምክንያት ነፃነትን አግኝተው ወደቀድሞው የክብር ቦታቸው እንደገቡ “ወሖረ ኀበ እለ ሙቅሕታ ትነብር ነፍሶሙ ወሰበከ ሎሙ ግዕዛነ፤ ተግዘው ወደነበሩት ነፍሳት ሄዶ ነፃነትን ሰበከላቸው ወይም አወጀላቸው” በማለት ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የምሥራቹን ያስረዳናል፡፡ ከዚህ እውነታ በመነሣት ኢትዮጵያዊው ነባቤ መለኮት ቅዱስ ያሬድ በዜማ መጽሐፉ የአባቶቻችን ክብር የተረጋገጠው በቅዱስ ወንጌል በተነገረውና በቅዱስ መስቀል በተፈጸመው የቤዛነት መሥዋዕት እንደሆነ በጣዕመ ዜማው ይነግረናል፡፡
ቅዱስ መጽሐፍም እንደሚያስረዳን በመስቀሉና በቃሉ የከበሩ ከክርስቶስ በፊት የነበሩ ቀደምት አበው ብቻ አይደሉም፤ ከዘመነ ክርስቶስ ጀምሮ እስካሁን ያሉት ሕዝበ ክርስቲያንም በመስቀሉና በቃሉ ከብረዋል እንጂ ይለናል፡፡ ከዚህ አንጻር በዚህ ዘመን የምንገኘውም ሆን እስከ ዕለተ ምጽአት የሚነሣው ትውልድ ሁሉ የክብር ክብርና የዘለዓለም ሕይወት የሚያገኘው በመስቀሉና በቃሉ መሆኑን ያሳየናል፡፡
ጌታችን ወደዚህ ዓለም በመጣ ጊዜ ያከናወናቸው ተግባራት ሁሉ በሁለት ዐበይት ነገሮች የሚጠቃለሉ ናቸው፤ እነሱም፡- አንደኛው እግዚአብሔርንና መንግሥቱን ፈቃዱንም ጭምር ለሰው ልጆች መግለፁ ነው፤ ይኸውም በቅዱስ ወንጌል ተጽፎ የምናገኘው ቅዱስ ቃሉ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በሰው ልጆች ፈንታ እሱ ራሱ በመስቀል ላይ መሥዋዕት በመሆን የሰው ልጆችን ማዳኑ ነው፡፡ ጌታችን በእነዚህ ሁለት ዐበይት ነገሮች ትዝምደ ሰብእን ወይም የሰው ዘርን አድኖአል፤ ስለሆነም መዳናችን ቃሉ በተመዘገበበት በቅዱስ ወንጌልና የቤዛነት አዳኝነቱ በተከናወነበት በቅዱስ መስቀል ላይ የተፈጸመ በመሆኑ ቅዱስ መስቀልንና ቅዱስ ወንጌልን በከፍተኛ ደረጃ ማክበራችን ተገቢ ብቻ ሳይሆን ከተገቢም በላይ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ክቡራንና ክቡራት የበዓለ መስቀሉ ተሳታፊዎች፡- የፍቅረ መስቀሉ መንፈሳዊ ተመሥጦ ያደረባት የታላቁ ቈስጠንጢኖስ እናት ቅድስት ዕሌኒ መስቀሉን ለመፈለግ ከዛሬዋ የቱርክ ሀገር እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ የተጓዘችው መስቀሉ የክብሯ ምንጭና የዘለዓለማዊ ሕይወቷ መገኛ መሆኑን ከቃሉ በመረዳትዋ፣ በተግባርም በማየቷ እንደሆነ መገንዘቡ አይከብድም፡፡ ቅድስት ዕሌኒ በዛሬው ዕለት የልቧ ምኞት በእግዚአብሔር ፈቃድ ተሳክቶ ዕጣንና ዕንጨት አንድ ላይ ደምራ በማቃጠል በጢሱ አማካኝነት መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ ያወቀችበት ዕለት በመሆኑ በዚህ ምክንያት ይህንን ቀን ቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ በታላቅ ድምቀት ታከብረዋለች፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ የሰው ልጆች ድኅነት በምልአት የተፈጸመበት ቅዱስ መስቀል ከምንም በላይ ሊከበርና ሊደመጥ ይገባል፡፡ የመስቀል ነገረ ድኅነት በአንድ ጊዜ ተከናውኖ የተጠናቀቀ አይደለም፤ ዛሬም ነገረ መስቀሉ በየሰከንዱ ብዙዎችን ያድናል፡፡ ነገረ መስቀሉ የተለያዩትን አሰባስቦ አንድ የሚያደርግ ነው፤ ነገረ መስቀሉ የተጣሉትን አስታርቆ በአንድ ማእድ የሚያስቀምጥ ነው፡፡ ነገረ መስቀሉ ቂምንና በቀልን ከሥሩ መንግሎ የሚጥል፣ በምትኩም ሰላምንና ፍቅርን የሚያድል አምላካዊ ምሥጢር ነው፡፡ ነገረ መስቀሉ ኀጢአትን በደልንና መርገምን ደምስሶ ነፃነትን፣ ጽድቅን፣ ሕይወትንና ክብርን የሚያጐናጽፍ ነው፤ ግን ይህ ሁሉ እውን ሊሆን የሚችለው ነገረ መስቀሉ በትክክል ሲደመጥና ሲከተሉት እንደሆነ መዘንጋት የለብንም፡፡ ቀደምት ኢትዮጵያውያን አበው ነገረ መስቀሉን በትክክል አዳምጠውና ተከትለው በነፃነት፣ በአንድነት፣ በወንድማማችነት፣ በይቅር ባይነትና በሰላም ኖረዋል፡፡
አባቶቻችን በዓለም ብቸኛ የሆነ የሀገር ነፃነትና አንድነት ጠብቀው ለእኛ ሊያስረክቡ የቻሉት የነገረ መስቀሉን አስተምህሮ ብቻ በመከተላቸው እንደሆነ ማስተዋል ይገባናል፤ ይህንን እውነት የማንገነዘብና የማናስተውል ኢትዮጵያውያን ካለን ራሳችንን አላወቅንም ማለት ነው፡፡ ደግሞስ አብያተ ክርስቲያናትን እየተዳፈሩና እያቃጠሉ፣ እየዘረፉና እየገደሉ፣ ሰላምንና አንድነትን፣ ፍቅርንና ልማትን ማምጣት ይቻላል ወይ? እንደዚህ ዐይነቱ አጒል አስተሳሰብና ድፍረት በእግዚአብሔርና በሕዝበ ክርስቲያኑ ላይ እየተፈጸመ ያለ ክፉና አጥፊ ድርጊት መሆኑ ታውቆ በአስቸኳይ መቆም አለበት፤ እስከ መጨረሻውም መገታት አለበት፤ በዚህ ዙሪያ በሚሆነው ነገር ሁሉ በጭራሽ መግባባት አይኖርም፡፡ ኢትዮጵያውያን አበው መስቀልን ይሳለሙታል እንጂ አያቃጥሉትም፤ ኢትዮጵያውያን አበው መስቀልን የአክብሮት ስግደት ይሰግዱለታል እንጂ አይረግጡትም፣ ኢትዮጵያውያን አበው መስቀልን ያከብሩታል እንጅ አያዋርዱትም፤ ምክንያቱም በመስቀሉና በቃሉ ክብራቸውንና ድኅነታቸውን እንዳገኙ አሳምረው ያውቃሉና ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ “ትመኛላችሁ፤ ለእናንተም አይሆንም፣ ትገድላላችሁ፣ በብርቱም ትፈልጋላችሁ፣ ልታገኙም አትችሉም፣ ትጣላላችሁ፣ ትዋጉማላችሁ፣ ነገር ግን አትለምኑምና ለእናንተ አይሆንም” እንዳለው ምኞታችን ሁሉ ሊሳካ ያልቻለው ከመስቀሉ እየራቅን ስለሄድን ነው፤ ልመናችንም ወደ እግዚአብሔር ለማቅረብና በፈቃዱ ለመኖር እንደ አሳፋሪ ነገር ስለቈጠርን ነው፡፡
ይህም በመሆኑ እግዚአብሔር በነቢዩ በኢሳይያስ በኩል “አንትሙኒ ተሐውሩ ግድመ ግድመ፤ ወአነኒ አሐውር ግድመ ግድመ፤ እናንተም ዳር ዳሩን ትሄዳላችሁ፤ እኔም ዳር ዳሩን እሄዳለሁ” ያለውን በኢትዮጵያ ላይ እየተፈጸመ ይገኛል፡፡ ኢትዮጵያውያን መሪዎችና ልሂቃን ከኃምሣ ዓመታት ላላነሱዘመናት ከእግዚአብሔር ርቀዋል፡፡ ከመስቀሉ ሥርም ጠፍተዋል፡፡ ይህ ዐይነቱ አመለካከት በኢትዮጵያ ውስጥ አያስኬድም፣ እንደማያስኬድም በግልጽ እያታየ ነው፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ተዉ ወደ እግዚአብሔር እንመለስ፤ እንደ ቀደምት አባቶቻችን ከቤተ ክርስቲያን ዐጸድና ከመስቀል ሥር እንገኝ፡፡ የጎደለንን ፍቅርና ሰላም፣ አንድነትና እኩልነት፣ ፍትሕና ወንድማማችነት በመስቀሉ ውስጥ ተትረፍርፎ እናገኘዋለን፡፡ ይቅርታና መተባበር፣ መከባበርና መተማመን በመስቀሉ ውስጥ ሞልቶአል፡፡ የኢትዮጵያ ፈውስ ከመስቀሉ ሥር እንደሆነ ሁላችንም እንወቅ፤ እንደ አባቶቹ በመስቀሉና በቃሉ ለመክበር የሚፈልግ ትውልድ ወደ መስቀሉና ወደቃሉ ሊመለስ ግድ ይለዋል፤ ያለዚያ ግን ምኞቱ ሁሉ ቅዠት ከሚሆን በቀር ሊሳካ አይችልም፡፡
በመጨረሻም፤ የመስቀል ትሩፋት ግኝት የሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከሁሉም በላይ እኩልነትን ከአንድነት ጋር፣ ነፃነትን ከወንድማማችነት ጋር አጥብቆ እንደሚወድ፣ ይህንንም ከመስቀሉ ቃል ያገኘው ዕሴት እንደሆነ ዐውቃችሁ፣ የሀገሪቱ ምሁራን፣ ፓለቲከኞች፣ ልኂቃንና አክቲቭስቶች ከጥላቻና ከመወራረፍ፣ ከስድብና ከመጠላለፍ፣ ከመፎካከርና ከመዘለዓለፍ ተቈጥባችሁ በቅንነት፣ በአርቆ አስተዋይነት፣ በይቅርታና በፍቅር ይህንን ታላቅ ሕዝብ በእኩልነት እንድናገለግል፣ አንድነታችንንና ሰላማችንንም የጋራ ሀብት አድርገን እንድንጠብቅ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡ መልካም የመስቀል በዓል ያድርግልን፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡