መስከረም 16 ቀን 2011 ዓ.ም. የመስቀል ደመራ በዓል ሐዋርያዊ መልእክት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

የጥል ግድግዳን በመስቀሉ አፍርሶ ሁላችንንም በፍቅርና በይቅርታ አንድ አድርጎ ወደ እርሱ ያቀረበን አምላካችን እግዚአብሔር እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ አንድ ዓመተ ምሕረት በዓለ መስቀሉ በሰላም አደረሳችሁ።

«ወወሀበነ ሰላመ ለርሑቃን ወሰላመ ለቅሩባን በመስቀሉ
በመስቀሉ ርቀው ለነበሩትም፥ ቀርበን ለነበርነውም ሰላምን ሰጠን።»
(ኤፌ. 2፥17)

የእግዚአብሔር ቃል እዚህ ላይ እንደሚነግረን ስሕተት ባመጣው ኀጢአት ምክንያት ሰዎች በአንድ ወቅት በመንፈስ ተለያይተውና ተራርቀው እንደ ነበሩ ነው። በእርግጥም የቀደመው ሰው በመስሐቲ ፍጡር ተገፋፍቶ ስሕተትን በመፈጸሙ ለኀጢአት ተዳርጎ ከእግዚአብሔር ተለይቶ፥ ከገነትም ወጥቶ ወደ ምድረ ፍዳ እንደተሰደደ እናውቃለን። በምድረ ፍዳ መኖርን አንድ ብሎ የጀመረው የሰው ልጅ ንጽሐ ባሕርዩ ስለአደፈበት በስሕተት ላይ ስሕተት እየፈጸመ በመቀጠሉ የእርስ በርስ መለያየትና መራራቅ እያሰፋ የጨለማ ሕይወትን ማስተናገድ ቀጠለ። ሰዎች በመለያየትና በመራራቅ የኖሩበት ያ ዘመን የጨለማና የሞት ጥላ ዘመን እንደነበረ ቅዱስ መጽሐፍ ‘በጨለማና በሞት ጥላ የሚኖር ሕዝብ’ እያለ ይገልጸዋል። በዚያን ወቅት ሰዎች ከሰማያውያን ፍጡራን ብቻ ሳይሆን እርስ በርሳቸውም ተለያይተውና ተራርቀው የኖሩበት፥ ከሁሉም በላይ ደግሞ ሕይወት፥ መድኀኒት ከሆነው ከእውነተኛው አምላክ ከእግዚአብሔር ተለይተውና ርቀው፥ በባዕድ አምልኮ ተዘፍቀው የኖሩበት ያ የፍዳ፥ የመርገም፥ የኵነኔ፥ የመለያየትና የመራራቅ ዘመን እውነትም የጨለማና የሞት ጥላ ተምሳሌት ነበረ። ሆኖም የሰው ድኅነቱን እንጂ ጥፋቱን የማይሻ እግዚአብሔር አምላካችን በፍጹም ፍቅሩ እኛን ሊታረቀንና ወደራሱ ሊያቀርበን ቍርጥ ፈቃዱ እንደሆነ በቅዱሳን ነቢያት ደጋግሞ ገለጸልን። ጊዜው ሲደርስም ራሱ በሥጋ ተገልጾ በመስቀል ላይ በፈጸመው ቤዛነት ፍጹም ይቅርታን ሰጥቶ፥ በሩቅም በቅርብም ያለነውን አንድ ላይ አገናኝቶ የአንዲት መንግሥቱ ዜጎች አድርጎናል።

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤

የመስቀልን በዓል በየዓመቱ በታላቅ ድምቀት የምናከብርበት ዋና ምክንያት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የራቁትንና የቀረቡትን አሰባስቦ አንድ ያደረገበትን ምሥጢር ተረስቶና ተዳፍኖ እንዳይቀር ሲባል የተካሄደውን መንፈሳዊ ተጋድሎ ለማስታወስና በትምህርተ መስቀል ውስጥ ያለውን የሰላም ጸጋ በምእመናን ልቡና ውስጥ ለማሠረጽ ነው። ከመስቀሉ የምንሰማው እጅግ በጣም ላዕላዊ አስተምህሮ «እየተበደሉም ቢሆን ለበዳዮች ይቅርታ መስጠት፥ በፍቅርም መቀበል» ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደል ሳይኖረው በዐመፅና በአድማ ተነሣሥተው በችንካር እጁንና እግሩን ቸንክረው፥ በገመድ አስረው ለሰቀሉት ሰዎች በዚያችው ሰዓት በመስቀል ላይ እያለ «የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው» ብሎ ይቅርታ መስጠቱ፥ በመስቀሉ ላይ የተገነባው የይቅርታ፥ የምሕረትና የፍቅር ከፍታ ምን ያህል አስገራሚ እንደሆነ በአድናቆትና በተመስጦ እንድናየው ያስገድደናል። በመሆኑም ከዚህ ዐቢይ በዓል ልንወስደው የሚገባን ዐቢይ አስተምህሮ ፍቅርን፥ ይቅርታንና አንድነትን እንደ ልዩ የሕይወት ጸጋ አድርጎ መያዝ ለዘላቂ ሰላም ዋስትና አለው የሚለው ነው።

ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ጥፋትና በደል በምልአት የሚያውቅ አምላክ ሆኖ ሳለ በመዋዕለ ሥጋዌው ሁሉን በፍቅር እየተቀበለ ይቅር ተብለሃል፥ ይቅር ተብለሻል ከማለት በስተቀር በአንድ ሰው እንኳ አልፈረደም። ታዲያ የተደረገውንና የተነገረውን ብቻ ሳይሆን በልብ የታሰበውንም ሳይቀር የሚያውቅ አምላክ ሁሉንም በፍቅር፥ በይቅርታና በምሕረት የሚቀበል ከሆነ የራሳችንን እንጂ የሌላውን በደል በአግባቡ የማናውቅ፥ በዚያውም ላይ ሌላውን ከምንተችበት በደል ነፃ ሳንሆን ለመፍረድ እንዴት እንደፍራለን? ምክንያቱም መፍረድ በራሱ ኀጢአት እንደሆነ «በማንም ላይ አትፍረዱ» ተብሎ ተነግሮናልና ነው። የመስቀል አስተምህሮ አንድነትና አንድነት ብቻ እንደሆነ የምንገነዘበው ለበደለኞች በተደረገው ይቅርታ ነው። በደለኞች ይቅርታ ከተደረገላቸው ይቅርታ የተደረገላቸው በደለኞችና ያልበደሉ ወገኖች አንድ ላይ ይውላሉ ማለት ነው፤ ታዲያ አንድነት ማለት ይህ አይደለምን? ቅድስት ዕሌኒ ከብዙ ሠራዊቷ ጋር ረጅም ጒዞ የተጓዘችው የፍቅር፥ የይቅርታና የአንድነት አስተምህሮ ዋና መገለጫ የሆነው ዕፀ መስቀል ተቀብሮ፥ ተዳፍኖና ተረስቶ መቅረት የለበትም፥ ዓለምና ትውልዶች ሊማሩበት፥ ሊያውቁትና ሊመሩበት ይገባል በሚል ጽኑ መለኮታዊ እምነት እንደነበረ ጥርጥር የለውም። በመሆኑም ህልምዋና ጥረትዋ ተሳክቶ እነሆ በዛሬው ዕለት በደመረችው ጢሰ ዕጣን አመልካችነት መስቀሉ የተቀበረበትን ለማወቅ ችላለች። ባደረገችውም ቊፋሮ መጋቢት 10 ቀን እውነተኛውን መስቀል ለማውጣት ችላለች። ወዲያውኑም ቤተ ክርስቲያኑን ማሠራት ጀምራ መስከረም 17 ቀን ቅዳሴ ቤቱን በማክበር መስከረም 21 ቀን ዕፀ መስቀሉን በጎልጎታ ባሠራችው ቤተ ክርስቲያን አስገብታለች። እኛም በዓለ መስቀሉን በየዓመቱ የምናከብረው ከዚህ ሃይማኖታዊ ትውፊት በመነሣት ነው።

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤

የደመራን በዓል ስናከብር ደመራ ማለት የተበታተኑትንና ተራርቀው የነበሩትን ዕንጨቶች አንድ ላይ ማሰባሰብ ማለት እንደሆነ አንዘነጋውም። ታዲያ ዕንጨቶችን ሰብስቦ አንድ ላይ በመደመር አንድነትንና እውነተኛነትን ያስተማረ ቅዱስ መስቀል አይደለምን? እኛስ ከመስቀል ባገኘነው መሠረታዊ አስተምህሮ ደመራን በመደመር መስቀሉን ለማክበር የተሰበሰብነው አንድነታችንን ለማረጋገጥ አይደለምን? ይህንን ተገንዝበን በዓለ መስቀሉን እያከበርን ከሆነ የመስቀሉ ትምህርት በሚገባ ገብቶናል ማለት ነው። መስቀል ማለት ወዳጅን ብቻ ሳይሆን ጠላትንም ጭምር እንደራስ አድርጎ መውደድ ነው፤ መስቀል ማለት ለወዳጅ ብቻ ሳይሆን ለበዳይም ጭምር ይቅርታን መጸለይ ነው፤ መስቀል ማለት ከወዳጅ ጋር ብቻ ሳይሆን ከባላጋራም ጋር ታርቆና ተቻችሎ በአንድነት መኖር ነው። ይህ ዐይነቱ ሕይወት ሰዎችን ወደ ፍጹም ፍቅር ያደርሳቸዋል። ፍቅርና ይቅርታ ሲጠቅሙ እንጂ ሲጎዱ ታይተው አያውቁም። ለዚህም ነው ሕዝባችን በየዓመቱ በመላ ሀገራችን በሚከበረው በዓለ መስቀል የተጣላው ታርቆና ይቅር ይቅር ተባብሎ በየሰፈሩ በአንድነት ተቀምጦ እግዚአብሔር የሰጠውን በረከተ ማእድ በኅብረት እየተቋደሰ አንድነቱንና ፍቅሩን የሚያድሰው። ቅዱስ መስቀል ያወረሰንን ይህንን ባህል እናክብረው፥ እንጠብቀው፥ እንመራበት።

በመጨረሻም፤ በዛሬው ዕለት ለመላ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት የምናስተላልፈው የእግዚአብሔር መልእክት ገና ያልሰከኑ የሚመስሉ የጥላቻ፥ የመጠራጠር፥ የመለያየትና ያለመተማመን፥ ራስን የመውደድና የመሳሰሉ ዝንባሌዎች እንዲገቱ፥ ሁሉም ኢትዮጵያውያን የኢትዮጵያ አንድነት ከሁሉም በላይ እንደሆነ እንዲገነዘቡ፤ ኀይልና ጒልበት፥ እድገትና ብልጽግና፥ መከበርና መታፈር፥ መወደድና መፈራት በአስተማማኝ ሁኔታ የሚገኘው ከአንድነት ብቻ እንደሆነ በአጽንዖት እንዲያስተውሉ፤ ከእኛ ውስጥ አንድ ስንኳ ሳይጠፋ በሰላም ዘመኑን የይቅርታና የአንድነት ዘመን አድርገው እንዲቀበሉና ይህንንም እንዲጠብቁ በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን።

በዓለ መስቀሉን የሰላም የፍቅርና የአንድነት በዓል ያድርግልን እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር። አሜን።

የመስከረም 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ዘመን መለወጫ በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ፤

ምድራችንን በልምላሜ፣ በአበባ፣ በእሸት በአጠቃላይ በፍጹም በረከት እያደሰ ዘመንን በዘመን እየተካ ጸጋውን ያበዛልን እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከሁለት ሺሕ ዐሥር ዓመተ ምሕረት ዘመነ ማርቆስ ወደ ሁለት ሺሕ ዐሥራ አንድ ዓመተ ምሕረት ዘመነ ሉቃስ በሰላም አደረሳችሁ!!

“ሐድሱ መንፈሰ ልብክሙ፤የልቡናችሁን ዕውቀት አድሱ፤እግዚአብሔር ያደሰውን አዲሱን ሰውነት በእውነት በቅንነትና በንጽሕና ልበሱት፤ ሐሰትን ተዉአት፣ ሁላችሁም ከወንድሞቻችሁ ጋር እውነትን ተናገሩ፤ እኛ አንድ አካል ነንና” (ኤፌ 4፥23)፡፡

እግዚአብሔር ለፍጥረቱ ከለገሳቸው ስጦታዎች አንዱና ዋነኛው የመታደስ ጸጋ ነው፤ እግዚአብሔር፣ እያረጀ እንደገናም እየታደሰ የሚኖር የግዙፋን ፍጥረታት ዓለምና እርጅና የማይነካው የመንፈሳውያን ፍጥረታት ዓለም በድምሩ ሁለት ዐይነት ዓለም እንደፈጠረ ይታወቃል፡፡ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ከግዙፋኑ ወገን ቢሆንም ለተወሰነ ጊዜ በግዙፉ ዓለም ከቆየ በኋላ ታድሶ ወደ ረቂቁ መንፈሳዊ ዓለም በመሻገር ያለ እርጅና ለዘለዓለም ጸንቶ ለሚኖር ሕይወት የታደለ ፍጡር እንደነበረ በመጽሐፍም በተግባርም የተረጋገጠ ነው፤ ይህ ዐይነቱ የሰው ዕድል በኀጢአት ምክንያት ለጊዜው ቢደናቀፍም የተዘጋጀልንን ጸጋ በውል እንድናውቅ እነ ሄኖክና እነ ኤልያስ የመሳሰሉትን ሞትና እርጅና ወደ ሌለበት ዓለም በመውሰድ በተግባር አሳይቶናል፡፡

የሰው ልጅ የመታደስ ጸጋ በእግዚአብሔር ቃል ኪዳን እንደገና እንደሚቀጥል በነቢያቱ በኩል ተስፋው ሲገለጽ ከቆየ በኋላ፣በባሕርይ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ዳግመኛ ዕድሉ ተሰጥቶን እነሆ ሙሉ በሙሉ ታድሰን ወደማያረጀው መንፈሳዊ ዓለም ለመሸጋገር የጌታ ቀንን እየጠበቅን እንገኛለን፡፡ የሰው ልጅ በአጠቃላይ በመንፈሳዊ ሕይወቱ ታሪክ ሁለት ታላላቅ ነገሮች አጋጥመውታል፤ እነሱም ብልየትና ሕዳሴ ወይም ማርጀትና መታደስ ናቸው፤ እነዚህ ሁለቱ በዘመን ውስጥ ያለፉ በመሆናቸው ዘመነ ብሉይ፣ ዘመነ ሐዲስ ተብለው ይታወቃሉ፤ ዘመነ ብሉይ የሚባለው ከአዳም ውድቀት ጀምሮ እስከ ልደተ ክርስቶስ ያለው ሲሆን፣ ከልደተ ክርስቶስ ጀምሮ ያለው ደግሞ ዘመነ ሐዲስ ይባላል፤ ይህ ዘመን መጨረሻ የሌለው ሐዲስ ሕይወት የተገኘበት ስለሆነ እስከ የለውም፤ከዚህ አንጻር ከልደተ ክርስቶስ ጀምሮ ባለው ዘመን የምንኖር ሁላችን በመታደስ ዘመን ውስጥ የምንገኝ ስለሆን ጽዉዓን ኅሩያን ማለትም የተጠሩ የተመረጡ እንባላለን፤ ዘመኑም ዓመተ ምሕረት ይባላል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፡ በፀሓይ አቈጣጠር መስከረም አንድ ቀን በየዓመቱ የምናከብረው የርእሰ ዐውደ ዓመት ወይም የዓመት ዙር መነሻ ራስ በዓል በውስጡ የተፈጥሮ፣ የብሉይና የሐዲስ ኪዳናት ምሥጢርን አምቆ የያዘ ነው፡፡ ከጥንተ ተፈጥሮ አንጻር ሲታይ የኢትዮጵያ ዘመን መለወጫ የቀደሙ አበው እነ አዳም፣ እነ ኖኅ ከዚያም ጥንታውያን የምሥራቅ አገሮች በተለይም ከለዳውያን፣ ግብጻውያንና አይሁዳውያን ጭምር ይከተሉት የነበረ ነው፤የኢትዮጵያ ርእሰ ዐውደ ዓመት፣ በጨረቃ አቈጣጠር ከመሆኑ በቀር ዛሬ ድረስ በእስራኤላውያን ተጠብቆ የሚኖር ከሁሉም የዘመን መለወጫ ይልቅ የዕድሜ ባለ ጸጋ የሆነ ርእሰ ዐውደ ዓመት መሆኑ ለጥንታዊነቱ በቂ ማስረጃ ነው ፤ ከዚህም ጋር ፀሓይና ጨረቃ በየዐሥራ ዘጠኙ ዓመት ዑደታቸውን ጳጕሜን አምስት ቀን እያጠናቀቁ መስከረም አንድ ቀን ሁለቱም ማለትም ፀሓይና ጨረቃ በአንድ ቀን ከአንድ የጊዜ መነሻ ነጥብ አንድ ላይ መነሣታቸው ይህ ቀን እነሱ የተፈጠሩበት ቀን ሊሆን እንደሚችል የሚጠቁም ነው፤ የቤተ ክርስቲያናችን የቊጥር መጽሐፍም ዐሥራ ዘጠነኛው ዐውደ አበቅቴ፣ ፀሓይና ጨረቃ መንገዳቸውን ፈጽመው በተፈጠሩበት ኆኅት ተራክቦ ያደርጉበታል በማለት ይህንን መሠረተ ሐሳብ ያጠናክራል፡፡
ከዚህ አኳያ የኢትዮጵያ የዘመን መለወጫ መስከረም አንድ ቀን ላይ እንዲሆን መደረጉ ከቀደምት አበው ትውፊትና የመስከረም አንድ ቀን ዐውደ አበቅቴ የፀሓይና የጨረቃ መነሻና መድረሻ ሆኖ ከመገኘት አንጻር የዘመን መነሻ ቊጥር የተጀመረው መስከረም አንድ ቀን ሊሆን እንደሚችል ግንዛቤ ስለተያዘበት እንደሆነ በዚህ እናስተውላለን፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ የዘመነ ብሉይ ማብቃት የዘመነ ሐዲስ መግባት ያበሠረ መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ በመሆኑ፣ ከመስከረም አንድ ቀን በፊት የተጠናቀቀው አሮጌው ዘመን እንደ ዘመነ ብሉይ፣ ከመስከረም አንድ ቀን ጀምሮ የምንቀበለው አዲሱ ዓመት እንደ ዘመነ ሐዲስ በአንድ ወገን፣የአሮጌውን ዘመንና የሐዲሱን ዘመን መለያ ርእሰ ዐውደ ዓመትና የዘመነ ብሉይና የዘመነ ሐዲስ መለያ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በሌላ ወገን በምሥጢራዊ ንጽጽር ተመሥጥሮ ርእሰ ዐውደ ዓመትና ቅዱስ ዮሐንስ አንድ ላይ እንዲከበሩ ተደርጎአል፤ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ይህንን አስመልክቶ ሲናገር “ውስተ ርእሰ ዐውደ ዓመት ተጽሕፈ ተዝካርከ፤ መታሰቢያህ በርእሰ ዐውደ ዓመት ላይ እንዲከበር ተጻፈ” ብሎአል፡፡ ዋናው መልእክት ርእሰ ዐውደ ዓመት የአሮጌውን ዘመን ማብቃት የሐዲሱን ዘመን መግባት በማብሠር አዋጅ ነጋሪ እንደሆነ ሁሉ፣ መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስም የብሉይ ኪዳንን ማብቃት የሐዲስ ኪዳንን መግባት በማብሠር አዋጅ ነጋሪ እንደሆነ በማነፃጸር በንስሓ መታደስን ይሰበክበታል፡፡ እንዲሁም አሮጌው ዘመን ከኅልፈተ ዓለም፣ አዲሱ ዘመን ከአዲሱ የመንግሥተ ሰማያት ዘመን፣ ርእሰ ዐውደ ዓመት ከዕለተ ምጽአት በንጽጽር ተመሥጥሮበት የጌታ ምጽአትና የመንግሥተ ሰማያት አዲስ ዘመን ይታሰብበታል፡፡

ከዚህም ሌላ የሀገራችን ሥነ ተፈጥሮ እንደሚያሳየን ከመስከረም አንድ ቀን በፊት ያለው ወርኀ ክረምት ነጐድጓድ፣ መብረቅ፣ የነፋስና የዝናም ውሽንፍር፣ የደፈረሰ ጐርፍ፣ የጉምና የደመና ጽልመት የሚነግሥበት፣ እህሉ አልቆ ሰው ለምግብ እጥረት የሚጋለጥበት ወቅት ነው፡፡ ከመስከረም አንድ ቀን በኋላ ግን ሁሉም ነገር የሚታደስበትና የሚለወጥበት ነው፤ ማለትም የምግብ ዕጥረቱ በአዲስ እሸት የሚተካበት፣ ጨለማው ደመናው ጉሙ መብረቁ ነጐድጓዱ ቦታውን የሚለቅበት፣ በምትኩ ደግሞ የፀሓይ የጨረቃና የከዋክብት ብርሃናት በጠራ ሰማይ ላይ ፍንትው ብለው ደማቅ ብርሃናቸውን የሚያሳዩበት፣ በየዋሻውና በየቋጥኙ ተወሽቀው የነበሩ አእዋፍና ሌሎች ፍጥረታት ሁሉ እንደልባቸው ወዲያ ወዲህ እየበረሩ በደስታ የሚዘምሩበት፣ ድፍርሱ የጐርፍ ውኃ ወለል ብሎ የሚጠራበት በአጠቃላይ የሥነ ፍጥረት ውበት የሚታደስበት ወቅት፣ ከመስከረም አንድ ቀን በኋላ ነው፤ ከዚህ አኳያ በመንፈስ ቅዱስ የተሟሟቁ ፣ በዕውቀት የተራቀቁ ቀደምት ኢትዮጵያውያን አበው የወርኀ ክረምቱን አስጨናቂ ሥነ ተፈጥሮ የዘመነ ብሉይ መከራና ፍዳ ተምሳሌት አድርገው አመሥጥረውታል፣ በሌላ በኩል ከመስከረም አንድ ቀን ጀምሮ ያለውን የሥነ ፍጥረት መታደስ የዘመነ ሐዲስ ተምሳሌት አድርገው በማመሥጠርና በመቀመር በሥነ ፍጥረት ውበት ላይ የመንፈስ ውበትን አላብሰውታል፤ ይህ እጅግ ውብና ድንቅ የሆነ መንፈሳዊና ተፈጥሮኣዊ ሀብተ አበው በሚገባ ጠብቆ ለትውልደ ትውልድ ማስተላለፍ ከነፍስ ወከፍ ኢትዮጵያዊ ይጠበቃል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፡ ኢትዮጵያዊው የዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ ዓመት በዋናነት የሚያስተምረን ትምህርት መታደስን፣ መለወጥን፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን መውጣትን፣ ከድህነት ወደ ልማት መሸጋገርን፣ ከማጣት ወደ ብልጽግና መራመድን ነው፣ አዲሱ ዓመት ስንፍናን በትጋት፣አለማወቅን በዕውቀት የምንለውጥበትን፣ ካለፈው ዓመት ይልቅ እጥፍ ድርብ የሆነ ሥራ በመሥራት ምርታችንን በከፍተኛ ሁኔታ የምናሳድግበትን አዲስ መንፈስ ሰንቀን ለተሻለ ልማትና እድገት የምንነሣበት መሆን ይኖርበታል፡፡ ታድያ ይህን ሁሉ እውን ማድረግ የምንችለው ከሁሉ በላይ የሆነውን ሀብተ ፍቅር በእያንዳንዳችን የልቡና ኪስ ሲሞላ ነው፡፡ ፍቅር የሁሉም መሠረት ነው፤ ፍቅር ሰላምን ይወልዳል፣ ሰላም አንድነትን ይወልዳል፣ አንድነት ጒልበትን፣ ልማትን፣ እድገትን፣ መታፈርን፣ መፈራትን፣ መከበርን፣ መደመጥን ይወልዳል፤ እንደሚታወቀው ሀገራችን ኢትዮጵያ የቀደመውን ደማቅ ገናንነትዋን መልሶ ለማረጋገጥ ሲሉ ውድ ልጆቿ ለለውጥ ሲባክኑ እነሆ ከስድሳ ዓመታት በላይ ተቆጥሮአል፡፡ ነገር ግን ከሚፈለገው ደረጃ ላይ ሳይደረስ ነገሮች እየተወሳሰቡ ከለውጡ ይልቅ ጥፋት እየቀደመ አሁን ላለንበት ደረጃ ደርሰናል፡፡ ይህ ለምን ሆነ ቢባል ዋና ምክንያት ሆኖ የሚታየው በሀገሪቱ ውስጥ ለዘመናት በበለጸገ ቅዱስ ባህል የተገነባውን የሕዝቡን መንፈሳዊና ሥነ ልቡናዊ ርእዮት ተከትሎ እርሱን ማእከል ባደረገ የእድገትና የለውጥ አስተዳደር ማስፈን ሲቻል በእሱ ፈንታ የውጭ ርእዮትን እንዳለ ተቀብሎ በሕዝቡ ጫንቃ ላይ በግድ ለመጫን የሚደረገው የተሳሳተ አካሄድ እንደሆነ መዘንጋት የለበትም፡፡ ለውጡ ሲጀመር ይቅር ይቅር በመባባል ወደዋናው የለውጥ ተግባር በመሸጋገር ፈንታ የበቀል እርምጃ ወደ መውሰድ ይዞራል፤ ከዚህም የተነሣ መግባባት ስላልተቻለ የሀገር አንድነትና የዜጎች ደኅንነት ሥጋት ላይ እየወደቀ የሀገሪቱና የዜጎችዋ ዕጣ ፈንታ ዋስትና የለሽ እየሆነ መቀጠል ግድ ሆኖበታል፡፡

ከሁሉ በላይ ደግሞ ከሦስት ሺሕ ዘመናት በላይ የእግዚአብሔር የመመለኪያ ቤተ መቅደስ የታቦቱና የመስቀሉ ታማኝ መንበር በሆነች ኢትዮጵያ ስመ እግዚአብሔርን እየጠሩና እግዚአብሔርን እየፈሩ ሕዝቡን መምራት የሚያስችል እምነትና ድፍረት መታጣቱ ነገሩ ሁሉ የኋልዮሽ እንዲመለስና ውኃ ቅዳ ውኃ መልስ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ አሁንም ከሁሉ በላይ ለኢትዮጵያ አንድነት የሚበጀው እግዚአብሔርንና ሕዝቡን ማእከል አድርጎ መሥራት ነው፤ እግዚአብሔርን ስናደምጥ ይቅርታ እንጂ መለያየት፣ የለም መጠራጠርና አለመተማመን ቦታ አይኖራቸውም፡፡ በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን እየተካሄደ ያለው ለውጥ እንደ ካሁን ቀደሞቹ ፈተና እንዳይገጥመው ሁሉም ኢትዮጵያዊ ለፍቅርና ለይቅርታ ሰፊውን ቦታ ይስጥ፣ የኀይለ ቃላት ውርወራን ያቁም፤ ኀይለ ቃልን የምንጠቀም ከሆነ መቃቃርን ያስከትላል፣ መቃቃር ጥላቻን ያሳድጋል፣ ጥላቻ ግጭትን ይወልዳል፤ ስለዚህ የሚወረወሩ ኀይለ ቃላት ወገንን አስከፍተው ዋጋ እንዳያስከፍሉን ከአዲሱ ዘመን መለወጫ ከመስከረም አንድ ቀን ጀምሮ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ገድለን እንቅበራቸው፤ የቀደመውን ግድፈት ሁሉ ለታሪክ ትተን ለቀጣይዋ ኢትዮጵያ አንድነትና ለዜጎችዋ ደኅነንት መልካም የሆነውን ማሰብ የዘወትር ተግባራችን ይሁን፤ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎችና አክቲቪስቶች ለሀገር አንድነትና ለዜጎች ደኅንነት ቅድሚያ እየሰጣችሁ በሰላምና በሰላም ብቻ መንገድ እየተጓዛችሁ ለሀገር የሚበጀውን በማድረግ ኀላፊነታችሁን እንድትወጡ፣ የጥበብ ባለሙያዎች፣ ወጣቶች፣ ምሁራን ሁላችሁም የቃላት ውርወራን አቁማችሁ ፍቅርንና ይቅርታን፣ የዜጎች ደኅንነትንና የሀገር አንድነትን እንድትሰብኩ በዚህ አጋጣሚ በእግዚአብሔር ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም፡ ባለፈው ዓመት በሀገራችን የታዩ የሰላምና የአንድነት ጠንቅ የሆኑ ግድፈቶች እንደአሮጌው ዘመን አሳልፈንና ፋይላቸውን ዘግተን በአዲስ ፍቅር፣ በይቅርታ፣ በአንድነት የሕዝቡን መንፈሳዊና ሥነ ልቡናዊ ነባር ዕሴትን በመጠበቅ እግዚአብሔርን በመፍራትና እሱን የበላይ ዳኛ አድርጎ በመቀበል የሀገር አንድነትንና የዜጎችን ደኅንነት በማስጠበቅ አዲሱን ዘመን በፍጹም መታደስ እንድንቀበለው አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡ አዲሱ ዘመን የተባረከና የተቀደሰ የሰላም፣ የፍቅናር የይቅርታ ዘመን ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡