መስከረም 16 ቀን 2008 ዓ/ም የመስቀል ደመራ በዓል (የእስክንድርያ ፓትርያርክ መገኘት ጋር)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

“ወደምሰሰ ለነ መጽሐፈ ዕዳነ በሥርዐቱ እምእድውነ ወአእተቶ እማእከሌነ ወቀነዎ በመስቀሉ —
በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዝ የተጻፈውን የእዳ ጽሕፈት ደመሰሰው፡፡ እርሱንም በመስቀል ጠርቆ ከመንገድ አስወግዶታል” (ቆላ. 2፥14)።

የተወደዳችሁ በዚህ በዓል ላይ የተገኛችሁ ሁሉ፤

እንኳን ለጌታችንና ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ መስቀል በሰላም አደረሳችሁ

በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከሚከበሩት ታላላቅ በዓላት አንዱ በዓለ መስቀል ሲሆን ስለ መስቀል መናገር ማለት ስለ ሰው ልጅ የድኅነት ታሪክ መናገር ነው፡፡ መስቀሉ የመዳናችን ብቻ ሳይሆን የሕይወትና የድል አድራጊነት ምልክታችንም ነውና፡፡ በመስቀሉ ዕርቅና ሰላም፣ ነፃነትና ተስፋ ይሰበካሉ፤ ቅዱስ መስቀል ዕርቅ የተፈጸመበት አደባባይ፣ አማናዊው የሐዲስ ኪዳን መሥዋዕት የተሠዋበት መንበር ነው፡፡ በመስቀሉ ጌታችን በሰው ላይ የተፈረደውንና የሕይወት ዕንቅፋት የነበረውን ሞትን በራሱ መሣሪያ አቅርቦ ከመንገድ ያስወገደበት፣ እርሱ ጌታችን የሕይወት ንጉሥ ሆኖ የነገሠበት ዙፋን ነው፡፡የተቀደሰ ነው የምንለውም በክርስቶስ ደም የተቀደሰ ስለሆነ ነው፡፡

ጌታችን እኛን ከሰይጣን ቍራኝነት ነፃ ያወጣን፤ ወደራሱ ያቀረበን፣ ጠብን እንድናሳድድ ጥላቻን እንድናስወግድ፣ከጥፋት እንድንድን ያደረገን በመስቀሉ ስለ ሆነ ይህ በዓል ለእኛ የድኅነታች ማስታወሻ አድርገን እናከብረዋለን፤ ከቅዱሳት መጻሕፍትና ከታሪክ እንደምንረዳው ጌታችንን የሰቀሉት አይሁድና የወቅቱ መሪዎች ከሙታን መነሣቱ ስለቈጫቸው የተሰቀለበትን መስቀል ዓለም እንዳያስታውሰው ቀበሩት፡፡ ይሁን እንጂ በመስቀሉ የተፈጸመውን ድኀነትና ፍቅር መቅበር ስላልቻሉ፤ፍቅሩ በልባቸው የታተመው ክርስቲያኖች በንግሥት እሌኒ መሪነት ከሦስት መቶ ዓመት በኋላ ቅዱስ መስቀሉን ከተቀበረበት አወጡት፡፡ አስቀድሞ በመስቀሉ የተገኘውን ድኅነትና ሰላም፣ የተገለጸው ፍቅር፣ የተደመሰሰው የዕዳ ጽሕፈት፣ የተወገደው ጥላቻና ሞት በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ ዋና ጉዳዮች ስለሆኑ በክርስቲያኖች ዘንድ መስቀሉን ማክበር ተቋርጦ ዐያውቅም፡፡ እኛም በሀገራችን በአንድነትና በፍቅር ሁነን ጥንታዊ ትውፊቱን በጠበቀ መልኩ በዓለ መስቀሉን በአደባባይ ወጥተን ደመራ ደምረን እያከበርን እንገኛለን፡፡

የዘንድሮውን የ2008 ዓ/ም በዓለ መስቀል ልዩ የሚያደርገው ብፁዕ ወቅዱስ ፖፕ ታዋድሮስ ዳግማዊ የእስክንድርያ ፖፕና የመንበረ ማርቆስ ፓትርያርክ ከግብጽ ሀገር በመምጣት በመካከላችን መገኘታቸውና በዓለ መስቀሉ በዩኔስኮ የዓለም ቅርስ ሁኖ በተመዘገበበት ማግስት መሆኑ ነው፡፡

በዚሁ አጋጣሚ ብፁዕ ወቅዱስ ፖፕ ታዋድሮስ ዳግማዊ ጥሪያችንን ተቀብለው በመምጣታቸው የተሰማኝን ደስታ እየገለጽኩ በድጋሚ እንኳን ደኅና መጡ እላለሁ፡፡ እንደሚታወቀው በኢትዮጵያና በግብጽ መካከል ለብዙ ዘመናት የቆየ ግንኙነት ያለሲሆን፣ ግንኙነቱ በእግዚአብሔር ፈቃድና በተፈጥሮ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ይህ ግንኙነት ቆይቶ ወደማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሃይማኖታዊ ግንኙነት እያደገ አሁን ያለበት ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ ቀደም ሲል እንደተባለው ግንኙነቱ የተመሠረተው በተፈጥሮ ላይ ስለሆነ ወደፊትም አይቋረጥም፡፡ ለዚህ አንዱ ምሳሌ የዐባይ ወንዝ ነው፡፡ ይህ በቅዱሳት መጻሕፍት ሳይቀር ስሙ የተጠቀሰው ታላቁ ወንዝ ለዘመናት ሁለቱን ሀገሮች እያጠጣ ይገኛል፡፡

በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያውያን ከራሳቸው አልፎ ለጎረቤት ሀገሮች ሳይቀር የሚጠቅም ግድብ እየሠሩ ይገኛሉ፡፡ የግድቡ መገንባትም በማንም ላይ ጒዳት እንማያደርስ በዓለም ዐቀፍ ባለሙያዎችም ጭምር መረጋገጡ ሁላችንም ያስደሰተ ጉዳይ ሆኗል፡፡ በወንድም ላይ ጒዳት ሳያደርሱ ራስን መጥቀም ደግሞ ወገናችን የሆነው የግብጽ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ፈጣሪንም የሚያስደስት የሥነ ልቦና ነፃነትን የሚሰጥ ሰላማዊ ተግባር ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር የመስቀል በዓልን ስናከብር ፍቅርን ወዳጅነት እንደምንዘክር ሁሉ የቅዱስነታቸውም በመካከላችን መገኘት ለሁለቱ ሀገሮች ሕዝቦች የወደፊት ትብብር ብቻ ሳይሆን የሃይማኖት አባቶች ለዓለም ሰላምና ደኅንነት ለምናሰማው የጋራ ድምፅ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡ በተለይ በአሁኑ ጊዜ ባለ መቻቻል፣ በጽንፈኝነት፣ በሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር፣ በስደት፣ በእርስ በእርስ ጦርነት፣ በአየር ንብረት ለውጥ፣ እና በመሳሰሉት ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ችግሮች የሰው ልጅ ሕይወት ለአደጋ በተጋለጠባቸው የዓለማችን ክፍሎች መፍትሔ ለመስጠት የሚመለከታቸ ሁሉ የበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ታሳስባለች፡፡

በቅርቡ ከሀገራቸው የወጡ የኢትዮጵያና የግብጽ ወጣቶች የዚሁ ችግር ሰማዕታት ሲሆኑ የሁለቱም ሀገሮች አባቶች ተመሳሳይ መልእክትን ለዓለም አስተላልፈዋል፡፡ ኢትዮጵያውያንና ግብጻውያንም በችግርና በደስታ ያለቸውን አንድነት ገልጸዋል፡፡ ከወራት በፊት ቅዱስነታቸው ባስተላለፉልን ጥሪ መሠረት ከብፁዓን አባቶች ጋር በመሆን ግብጽን የጎብኝን ሲሆን አሁን ደግሞ እኛ ባቀረብንላቸው ጥሪ መሠረት ወደ ሀገራችን መጥተው በመካከላችን ተገኝተዋል፡፡ ቅዱስነታቸው በኢትዮጵያ የሚኖራቸው ቆይታ ታሪካዊ እንደ ሚሆንና የሁለቱን ሀገሮች መልካም ግኑኝነት የበለጠ እንደሚያጠናክር ጽኑ እምነት አለን፡፡

በዓሉን የሰላምና የፍቅር ያድርግልን፣ እግዚአብሔር ይባርካችሁ ይጠብቃችሁ፣ እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ

መስከረም 1 ቀን የ2008 ዓ.ም አዲስ ዓመት የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤ የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤ በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤ የዘመናት ፈጣሪ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር ያለፈውን ዓመት በሰላም አስፈጽሞ እንኳን ለአዲሱ የሁለት ሺሕ ስምንት ዓመተ ምሕረት ዘመነ ዮሐንስ በሰላም አደረሰችሁ!!

‹‹ወኀሊ ዓመተ ለትውልደ ትውልድ
የብዙ ትውልድን ዓመታት አስብ።››
(ዘዳ. 32፥7)፡፡

የሁሉም አስገኝና ፈጣሪ የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን ከፈጠራቸው ፍጥረታት መካከል አንድ ስንኳ ጥቅም የለሽ የሆነ ፍጥረት አይገኝም፡፡ ፍጥረታት ሁሉ በእርሱ ዘንድ ውብና የየራሳቸው ዐላማና ተግባር ያላቸው ናቸው (ዘፍ.1፥25)

እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት በፍጡር ዐቅም ሙሉ በሙሉ ተቆጥረው የሚዘለቁ አይደሉም፤ ከጥቂቶቹ በስተቀር ሁሉንም በዐይነ ፍጡራን ማየት ስለማይቻል ቅዱስ መጽሐፍ ፍጡራንን ጠቅለል አድርጎ በአጭር ቃል ሲገልጽ ‹‹በሰማይና በምድር ያሉት፣ የሚታዩትና የማይታዩት›› ይላቸዋል፤ (ቈላ. 1፥15) በምድር ላይ እያሉ ከማይታዩት መካከል አንዱ ዘመን ወይም ጊዜ ነው፤ ጊዜ በድርጊት ከሚታወቅ በቀር በዐይን የሚታይ ግዙፍ አካል ወይም ልዩ ቀለም ያለው ፍጡር አይደለም፡፡

ይሁን እንጂ ባለመታየቱ ብቻ የለም ብሎ መደምደም ወይም መናገር አይቻልም፤ ምክንያቱም ከድቁቅ ስፍረ ጊዜ አንሥቶ ሰዓታትን በቀናት፣ ቀናትን በሳምንታት፣ ሳምንታትን በወራት፣ ወራትን በዓመታት ከዚያም በልዩ ልዩ አዕዋዳት እየጠቀለለ ሲያሽከረክር በተግባር እናያለንና ነው፡፡ ዘመን የድርጊት መሣሪያ ስለሆነ በአንድ ወቅት በተፈጸመ መልካም ወይም መጥፎ ነገር ይገለጻል፤ ከዚህም የተነሣ ዘመኑ መልካም ነው ወይም መጥፎ ነው ሲባል እንሰማለን ፡፡ ይሁንና የእኛ መሠረታዊ ጉዳይ ሊሆን የሚገባው የዘመን መታየትና አለመታየት ሳይሆን ለፍጡራን ከሚሰጠው ጥቅም አኳያ ግንዛቤ ወስደን ተጠቃሚ ለመሆን መንቀሳቀሱ ላይ ነው ፡፡

ዘመን ከዓለም መፈጠር በፊት ያልነበረ ከዓለም ጋር አብሮ የተፈጠረ፣ በሰማይ የሌለና ለምድራውያን ፍጡራን ብቻ አገልግሎት ሊሰጥ የተፈጠረ ነው፤ (ዘፍ.1፡14) ፡፡ የዘመን ሀብት ባይኖር ሰው ምድራዊ ሕይወቱን በትክክል መምራት አይችልም ነበር፡፡ በመሆኑም ምድራውያን ፍጥረታት በአጠቃላይ፣ በተለይም ደግሞ የሰው ልጅ ሥርዐት ባለውና ቅደም ተከተሉን ጠብቆ በዕቅድ ሥራውን በማከናወን ሕይወቱን በትክክል መምራት ይችል ዘንድ ሀብተ ዘመን ያስፈልገዋል ፡፡

ዘመን ለተግባር ከሚያበረክተው አገልግሎት በተጨማሪ በትምህርት ሰጪነቱ እጅግ አስፈላጊ በመሆኑ ያለፈውን ዘመን እንድናስታውስ እንጂ እንዳንረሳ የልጅ ልጅ ዘመናትን አስብ ብሎ እግዚአብሔር ይነግረናል፡፡ ምክንያቱም ለወደፊቱ የተሻለ ሥራ መሥራት የምንችለው ካለፈው ዘመን ትምህርት ቀስመን፣ ልምድና ተሞክሮ ወስደን ስለሆነ ነው፤ ሥራን ከዘመን ለይቶ ወይም ነጥሎ ማስቀመጥ በፍጹም አይቻልምና ፡፡ ስለሆነም ዘመን ለአጠቃላዩ ሥራችን ተቀዳሚ መሣሪያ ሆኖ እንዲያገለግለን እግዚአብሔር የሰጠን ሀብት ነውና ጊዜን በከንቱ ሳናባክን በምልአት ልንጠቀምበት ይገባል ፡፡

ሀገራችን ኢትዮጵያ ሁሉንም የተፈጥሮ ሀብት ተሟልቶ የተሰጣት፣ ድንቅና ውብ ሀገር ናት፤ ምድራዊት ገነት በሆነች በዚች ሀገር ተቀምጠን ስለድህነት ማውራት ከእንግዲህ ወዲህ እንዲያከትም ሁሉም ኢትዮጵያዊ በአንድነት መረባረብ አለበት፤ ልማታችንን በአስተማማኝ ደረጃ ዘላቂ ለማድረግ የድህነታችን ምሥጢር የት እንዳለ በውል ማወቁ ይጠቅማል ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ የድህነታችን ምሥጢር ተደብቆ ያለው የሥራ ባህልን አዳብሮ፣ የጊዜን ጥቅም ዐውቆና አንዲት ደቂቃ ስንኳ ሳያባክን በሀገሩ ውስጥ ሠርቶ ለመለወጥ ያለን ተነሣሽነት አናሳ መሆኑ ላይ ነው፡፡ በተለይም ወጣቱ ትውልድ ይህንን ተገንዝቦ መሠረታዊ የአስተሳሰብና በጊዜ ሠርቶ የመለወጥ ባህል ሊያጎለብት ይገባል፤ ይህንን ክፍተት በውል ስናውቅና በሥራ ስንታገለው ድህነትን ከሥር መሠረቱ ነቅለን መጣል እንችላል ፡፡

ዛሬ አደጉ በለጸጉ ተብሎ የሚነገርላቸው ሀብታም ሀገሮች አብዛኛዎቹ እንደ ኢትዮጵያ ያለ ለእርሻና ለልዩ ልዩ አዝርእት የተመቸ ለም መሬት፤ ለእንስሳ ርባታና ለሰው ኑሮ የተመቸ አየርና ንጹሕ ውኃ፣ በልዩ ልዩ ማእድን የተሞላ ነገር ግን ገና ያልተፈተሸ ድንግል መሬት ኖሮአቸው ሳይሆን፣ ያላቸውን ውሱን ሀብት በበለጸገ የሥራ ባህል ማለትም ሥራን ሳያማርጡ፣ ጊዜን በከንቱ ሳያባክኑ ያለ ዕረፍት ሌት ተቀን በመሥራታቸው ያገኙት ጸጋ እንደሆነ ማስተዋል አለብን፡፡ በመሆኑም ኅብረተ ሰባችን በአጠቃላይ በተለይም ወጣቱ ትውልድ አዲሱን ዘመን ሲቀበል አዲሱን ዓመት ከሀገራችን የሕዳሴ መርሐ ግብር ጋር በማቀናጀትና ጠንክሮ በመሥራት ግዙፍ የሆነ የልማትና የእድገት ስኬት ለማረጋገጥ ከዳር እስከ ዳር ተባብሮ እንዲንቀሳቀስ አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን መልካም አዲስ ዓመት ያድርግልን፡፡ እግዚአብሔር ይባርካችሁ ይቀድሳችሁ አሜን፡፡