መስከረም 16 ቀን የ2006 ዓ.ም. የመስቀል ደመራ በዓል
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትኖሩ፣ የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣ በሕመም ምክንያት በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ በቅዱስ ደሙ ፈሳሽነት ከኀጢአት፣ ከሞተ ነፍስና ከሲኦል ግዞት ነፃ አድርጎ ያዳነን ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ በሰላም አደረሳችሁ!!
‹‹መስቀል ዓለም የዳነበት የእግዚአብሔር ኀይልና ጥበብ ነው፤››
(1ቆሮ.1÷18-24)
የተወደዳችሁና የተከበራችሁ በመላ ኢትዮጵያና በተለያዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን ሆይ፡-
እኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማንያን፣ መስቀልን በታላቅ ድምቀት የምናከብርበት ዋናው ምክንያት፤ መስቀል ሰዎችን ለድኅነት፣ ዲያብሎስን ለሽንፈት ያበቃ የእግዚአብሔር ኀይልና ጥበብ በመሆኑ ነው፤ ቅዱስ መጽሐፍ እንደሚነግረን፣ ከሰው ልጅ ውድቀት ጀምሮ እስከ ስቅለተ ክርስቶስ ድረስ በነበረው ዘመን፣ በኀጢአት ምክንያት ሞተ ሥጋና ሞተ ነፍስ በሰው ላይ የሰለጠኑበት፣ ዲያብሎስ ኀጢአትን መሣርያ አድርጎ፣ በሞት አቀባይነት፣ ሰውን በሲኦል ውስጥ አጉሮ ያሠቃየበት ዘመን ነበረ፤ ሰው ለዚህ ዐይነቱ መከራ የተዳረገበት ምክንያት፣ የፈጣሪውን ትእዛዝ ተላልፎ በሠራው ኀጢአት በደለኛ ሆኖ በመገኘቱ ነው፤ በዚህም ተግባሩ እግዚአብሔር ተለየው፤ እግዚአብሔር ሰውን ሲለየው፣ ለሠራው ኀጢአት ቅጣት የሚሆን የሞት ፍርድም ፈርዶ ነው፤ ስለሆነም ሰው የተፈረደበት ጥፋተኛ በመሆኑ፣ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት አልነበረውም፤ ጠባቂ የሌላቸው በጎች፣ ለተኲላ ንጥቂያ የተጋለጡ እንደሚሆኑ ሁሉ፣ ሰውም እግዚአብሔር ሲለየው፣ ለዲያብሎስ የመከራ ግዛት የተጋለጠ ሆነ፤ ከአዳም ውድቀት እስከ ስቅለተ ክርስቶስ ባሉት ዘመናት፣ ሰው ሁሉ በፍዳ ኀጢአት እየተሰቃየ በዲያብሎስ ከተማ በሲኦል ውስጥ ግዞተኛ ሆኖ ቁም ስቅሉን አየ፤ (1ጴጥ. 3÷18-19 )
ይሁንና እግዚአብሔር ሰውን ካጋጠመው መከራ አንድ ቀን እንደሚገላግለው በነቢያት አድሮ ትንቢት ሲያናግር፣ ምሳሌ ሲያስመስል፣ ሱባዔ ሲያስቈጥር ቆይቶ ዘመኑ በደረሰ ጊዜ፣ በሰው ላይ የተላለፈውን ፍርድ ወደ ራሱ አዙሮ፣ ሕጉ የጣለውን የሞት ቅጣት እሱ ራሱ ለመቀበል፤በመስቀል ላይ ተሰቅሎ መሥዋዕት ሆነ፤ በመሥዋዕትነቱም ሰውን ከፍዳ ኀጢአትና ከሞተ ነፍስ ነፃ አወጣው፤ ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ እንደጻፈው፡- በፊት የተሠራውን ኀጢአት ለመተውና በእርሱ የሚያምኑትንም በኋላ ከሚመጣው ኀጢአት ለማዳን እግዚአብሔር፣ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ማመንን የኀጢአት ማስተሥረያ አድርጎ አቆመው፤ ብሎአል፡፡ (ሮሜ 3÷25-26)
ጌታችን በዚህ በመስቀሉ ላይ በፈጸመው መሥዋዕትነት ምክንያት፣ ያለፈው ኀጢአትም ሆነ የኋላው ኀጢአት የሚደመሰስበት ሁኔታ ተፈጠረ፤ ከዚህ በኋላ ኀጢአትም፣ ሞትም፣ ዲያብሎስም ተሸንፈው ባዶአቸውን ቀሩ፤ ለሰው ከእግዚአብሔር መለየትና መቀጣት ዋና መንሥኤው ለእግዚአብሔር አለመታዘዝ ነው፤ አለመታዘዝ የኀጢአት ምንጭ ሆነ፤ ኀጢአትም ሰውን ለፍርድ አጋለጠ፣ ፍርድም ለሞት የኀይል ምንጭ ሆነ፤ ሞትም በበኩሉ ለዲያብሎስ ከተማ ለሲኦል በኀጢአተኞች መሞላት ዋና ምክንያት ሆነ፤ አሁን ግን ክርስቶስ ለኀጢአተኞች ቤዛ ሆኖ በሰዎች ፈንታ በመስቀል ላይ በመሠዋቱ፣ የሰውን የኀጢአት ዕዳ ራሱ ከፈለና ሰውን ከኀጢአት ዕዳ ነፃ አደረገው፤ በዚህም የኀጢአትና የሞት ግንኙነት ተቋረጠ፤ ዲያብሎስም ከሰረ፤ ምክንያቱም በክርስቶስ ሞት ኀጢአት ተደመሰሰ፤ ኀጢአት ሲደመሰስ፣ ሰውም ከፍርድ ነፃ ሆነ፤ ሞት ይዞ የሚያቀርበውን ሲያጣ፤ ሲኦል የሚውጠውን አጣ፣ ዲያብሎስም ከሰረ፤ ማለትም ድል ሆነ፤ ተሸነፈ፤ መስቀል ያስገኘልን ድል ይህንን ነው፤ ለዚህም ነው መስቀል ሞዐ፤ ሞት ተሞአ፤ ወዲያብሎስ ወድቀ፤ መስቀል ድል አደረገ፤ ሞት ድል ሆነ፤ ዲያብሎስም ወደቀ፤ ብለው ቅዱሳት መጻሕፍት የምሥራቹን የሚነግሩን፤ (1ቆሮ.15÷54-57፤ ኤፌ.2÷16፤ ተሰ. 2÷14-15) እግዚአብሔር በዚህ ምክንያት ሰውን ታረቀው፤ ሰው ቀድሞ ከውድቀቱ በፊት የነበረውን ጸጋና ክብር ተመልሶለት ከእርሱ ጋር ኅብረት እንዲኖረው ፈቀደ፤ ኅብረቱም በእምነት፣ በጥምቀትና በቅዱስ ቊርባን ምሥጢር እንዲፈጸም አደረገ፤ ኀጢአት በዚህ ሲወገድ ሀብተ ጸጋ መጣ፣ ሀብተ ጸጋ ሲመጣ፣ ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ተመሠረተ፣ ሞተ ነፍስ ተሻረ፣ የሲኦል በር ተሰባበረ፣ ዲያብሎስም ባዶውን ቀረ፤ ሰው ግን ዘለዓለማዊ ሕይወትና ክብርን ተቀዳጀ፤ ስለሆነም በመስቀሉ ላይ በተፈጸመው የመሥዋዕትነት ኀይል በኀጢአታችን ከሚመጣብን ሞተ ነፍስና ከኵነኔ ሲኦል ድነናል፤ መስቀል የእግዚአብሔር ኀይልና ጥበብ ነው ብለን የምናምነውም በዚህ ኀይልና ጥበብ በመዳናችን ነው፤ መስቀልን ስናከብር በዋነኛነት የምናስበው፣ ክርስቶስንና የእርሱ የደም መሥዋዕትነትን ነው፤ ታላቁ ምሥጢርና የመዳኛችን አስኳልም ያለው በእርሱ ደም ውስጥ ነው፤ ይሁንና ደሙ የፈሰሰበት ትእምርተ መስቀልም ትልቅ ክብር ያለው ነው፤
ከኢትዮጵያ ሰንደቅ ዐላማ በስተጀርባ ያለው ትልቅ መልእክት የኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነትና ሉዓላዊነት ነው፤ ሆኖም የኢትዮጵያውያንን ነፃነትና ሉዓላዊነት በውክልና የተሸከመው ሰንደቅ ዐላማም ልዩ ክብር አለው፤ እንደዚሁም ሁሉ በክርስቶስ ደም የተገኘው ዕርቅና ድኅነት በስተጀርባው ያዘለና የዳንንበት ደሙም የፈሰሰው በእርሱ ላይ መሆኑን የሚያስታውሰንና የሚያሳስበን ትእምርተ መስቀልም ከፍ ያለ ክብር የሚገባው በመሆኑ እናከብረዋለን፤ መስቀል በክርስትና ሃይማኖት ጠላቶች ተቀብሮ ደብዛው እንዲጠፋ የተደረገው ሤራ እንዲከሽፍ የሆነበትም ዋና ምክንያት፣ መስቀል በዓለም ላይ የክርስቶስን መሥዋዕትነትና አዳኝነት እንዲመሰክርና እንዲያሳስብ ተፈልጎ ነው፤ ስለዚህ ትእምርተ መስቀሉን ባየን ቊጥር የክርሰቶስን መሥዋዕትነትና ድኅነታችንን እናስባለን፤ እናስታውሳለንም፡፡
ስናስበውም ቀላል በሆነ ነገር ሳይሆን፣ ለታላቅ የአዳኝነት ምሥጢሩ በሚገባ፣ በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዐትና በታላቅ ድምቀት መሆን ይገባዋል፣ መስቀል በክርስትና ሃይማኖት ጠላቶች ከተቀበረ በኋላ፣ በንግሥት ዕሌኒ መንፈሳዊ ጥረት ከተቀበረበት ጒድጓድ የወጣበትን ታሪክ ለማስታወስ፣ እኛ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በየዓመቱ መስከረም 17 ቀን ከፍ ባለ ሥነ ሥርዐትና በታላቅ ድምቀት እናከብረዋለን፤ እግዚአብሔር በመጀመሪያ ሰውን ከረቀቀ ጭንቅላት ጋር ፈጠረው፤ ሰውም ከእግዚአብሔር በተሰጠው አእምሮ እየተመራመረና እየተራቀቀ አሁን በዐይናችን የምናያቸውን የጥበብ ውጤቶች ሠራ፤ ከዚህ አኳያ ሰውን ለመርዳት የሚያገለግል መልካም የጥበብ ሥራ ሁሉ የእግዚአብሔር ጥበብ ነው ብሎ መቀበል እውነት እንጂ ስሕተት አይሆንም፤ ዓለም በየጊዜው የሚያጋጥሙአትን ችግሮች ከእግዚአብሔር በተገኘ ጥበብ መከላከል ኀጢአት አይደለም፡፡
ከዚህ አንጻር በአሁኑ ጊዜ እግዚአብሔር ለሰዎች በሰጠው የሕክምና ጥበብ በዓለም አስከፊ የሆነውን የኤች አይ ቪ ቫይረስን መቀነስ የሚያስችል የዕድሜ ማራዘሚያ መድኀኒት መገኘቱ መልካም ነው፤ በሌላ በኩል ደግሞ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ወገኖቻችን ፈጣሪን በማመንና በመማፀን፣ እግዚአብሔር የመፈወስ ኀይልን ባሳደረበት በቅዱስ ጸበል እየተጠቀሙ ፈውስ ማግኘቱ የእግዚአብሔር የምሕረት ስጦታ ነው፤ ስለሆነም ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ወገኖቻችን፣ መድኀኒቱና ጸበሉ ሰውን ለማዳን ከእግዚአብሔር የተሰጡ መሆናቸውን አምነው ሁለቱንም በመውሰድ በሽታውን ቢከላከሉ ኀጢአት አይሆንባቸውም፡፡
ከዚህም ጋር የእናቶችን ሞትና ሥቃይ ለመቀነስ ታስቦ በሀገራችን እየተካሄደ ያለውን እናቶችን በእርግዝና እና በወሊድ ጊዜ የመርዳት ሕክምና፣ እግዚአብሔር እናቶችን ለማዳን ብሎ የገለጸው ጥበብ እንደሆነ መገንዘቡ ብልህነት ነው፡፡ በተለይም በነፍስ አባትነት የጥበቃ ሥራ የተሠማሩ ቀሳውስትና መምህራን፣ እንዲሁም ሰባክያነ ወንጌል፣ ሕዝቡን በሚያስተምሩበት ጊዜ፣ እናቶች የተለመደው የሃይማኖታችን እምነትና ጸበል እየጠጡና እየተቀቡ፣ እንዲሁም የሚወዷትን እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን እየተማጸኑ፣ በሕክምና እየተረዱ ቢወልዱ በእግዚአብሔር የተወደደና የተፈቀደ ቅዱስ ተግባር መሆኑን በማስተማርና በማስረዳት፣ እናቶችን በወሊድ ከመሞት የመቀነስ መርሐ ግብሩ እንዲሳካ በሰፊው እንዲሠሩ ያስፈልጋል፡፡
የእግዚአብሔር ዐላማ ምን ጊዜውም ሰውን በሁለመናው ማዳን እንደሆነ እናውቃለን፤ በመሆኑም የእርሱ መልእክተኞች የሆን ሁላችን ሰው የሚድንበትን ሁሉ የማስተማርና የማስረዳት ግዴታና ኀላፊነት እንዳለብን መዘንጋት የለብንም፤ የመስቀል ምሥጢርም መዳንና ማዳን ነውና፣ አሁንም የማዳን ሥራውን ያለመታከት ማስተማር አለብን፤ ማስተዋልና ትጋት፣ ፍቅርና ስምምነት፣ መከባበርና መረዳዳት፣ መቻቻልና መተማመን ምንጊዜም መሣሪያዎቻችን እናድርጋቸው፤ ኢትዮጵያውያን አባቶቻችን ሃይማኖትና ቋንቋ፤ ብሔርና ባህል ሳይለያያቸውና ሳይነጣጥላቸው፤ ለዚህ ዓይነቱ ስሜትም ሳይበገሩ፣ ሁሉም እንደ መስቀል ችቦ አንድ ሆነው የዚህችን ሀገር አንድነትና ነፃነት፣ ታሪክና ሉዓላዊነት ጠብቀው ያስረከቡን በፍቅር፣ በስምምነትና በአንድነት መሥዋዕትነትን እየከፈሉና በኅብረት እየሠሩ ነው፤ ስለሆነም ከጥንት ጀምሮ ተጠብቆ የቆየውን የሕዝባችን አንድነት፣ በሃይማኖት የመቻቻልና የመከባበር፣ ተስማምቶና ተጋግዞ በፍቅር የመኖር ልዩ ጸጋችን፣ ከሀገራችን አልፎ ለዓለም ሁሉ መልካም አርኣያ እንዲሆን፣ እንደዚሁም በመላ ሀገራችን ተቀጣጥሎ የሚገኘው ልማታችንን ከሚፈለገው ግብ ለማድረስ ዋናውና መሠረታዊ ግብአት ሆኖ የሚያገለግለን ስለሆነ፣ ሁላችንም ኢትዮጵያውያን እንደ ዐይን ብሌን ልንጠብቀው ይገባል፡፡ ይህ የሆነ እንደሆነ ሀገራችን ከድህነትና ከጒስቊልና ተላቃ ከበለጸጉ የዓለማችን ሀገሮች እኩል የምትሰለፍበት ጊዜ እንዲመጣ በጒጉት እንጠብቃለን በብርቱም እንጸልያለን፡፡ ይህ እንዲሆንም ጠንክረን እንሥራ፤ በማለት ለመላ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት መልእክታችንን አደራ ጭምር እናስተላልፋለን ፡፡ መልካም የመስቀል በዓል ያድርግልን ፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ፡፡አሜን፡፡