ጥቅምት 12 ቀን 2010 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ወኤጲስ ቆጶሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት
እግዚአብሔር አምላካችን በተለመደው ቸርነቱ ከየመንበረ ጵጵስናችሁ በሰላም አሰባስቦ በዚህ ዐቢይ ዓመታዊ ስብሰባ ተገናኝተን ስለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አንድነት፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በስሙ እንድንመካከር ለፈቀደልን ለእርሱ ምስጋና ከአምልኮት ጋር እናቀርባለን፡፡ እናንተም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት እንኳን በደኅና መጣችሁ፡፡ እንኳንም ለዚህ ሐዋርያዊና ቀኖናዊ የቅዱስ ሲኖደስ ዓመታዊ ጉባኤ በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ፡፡

“ወዘንተ ባሕቱ አእምር ከመ በደኃረ መዋዕል ይመጽኣ ዓመታት እኩያት ወይከውኑ ሰብእ መፍቀርያነ ርእሶሙ፡፡ ነገር ግን በኋለኞቹ ዓመታት ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱበት ክፉ ዘመን እንደሚመጣ ዕወቅ” (2ኛ ጢሞ.9.1) ይህ መልእክት ቅዱስ ጳውሎስ ለሚወደው ደቀ መዝሙሩ ለጢሞቴዎስ ያስተላለፈው ምክር አዘል ትምህርት ነው፡፡

በቤተ ክርስቱያን ታሪክ እንደሚታወቀው ዐይነቱ ስልቱና መጠኑ ይለያይ እንደሆነ ነው እንጂ ከሆነ ጊዜ ጀምሮ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከፈተና ተለይታ አታውቅም፡፡ ይሁን እንጂ ወደ መጨረሻው ዘመን አካባቢ የሚሆነው መከራ ግን ከሁሉ የባሰ እንደሚሆን በቅዱሳት መጻሕፍት በተደጋጋሚ የተገለጸ ነው፡፡

ከዚህ አኳያ ቅዱስ ጳውሎስ ተማሪውን ጢሞቴዎስን ሊያስገነዝበው የፈለገው ነገር በመጨረሻ ዘመን የሚከሠተውን ፈተና ምእመናን ዐውቀው ጥንቃቄ ያደርጉ ዘንድ እንዲያስተምር ነው፡፡ ለወደፊት የሚሆነውን ነገር አስቀድሞ ማሳወቅና ወዳጆቹን የማስጠበቅ ኩነት ከጥንት ጀምሮ የነበረ የእግዚአብሔር አሠራር ነው፡፡ በዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ለተከታዩ ትውልድ ስለመጨረሻው ዘመን ሁናቴ የማሳወቅ ሥራን ሲሠራ እናስታውላለን፡፡

በተጠቀሰው ክፍለ ምንባብ ላይ የመጨረሻው ዘመን ገጽታ ምን እንደሚመስል በዝርዝር ተገልጾአል፡፡ ይዘቱን ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው በመጨረሸው ዘመን አካባቢ ነገሩ ሁሉ የተመሰቃቀለ እንጂ አንዳች የሚያስደስት ነገር እንደሌለው ነው፤ በተለይም በጥቅሱ ላይ እንደሚታየው የመጨረሻው ዘመን ሰዎች ከምንም በላይ ራሳቸውን የሚወዱበት ጊዜ መሆኑ ተነግሮአል፡፡ ይህ ዐይነቱ አመለካከት ቃለ ቅዱስ ወንጌልን ሙሉ በሙሉ የሚጻረር ነው፡፡

ጌታችን ለተከታዮቹ ያስተማረው “የኔ ሊሆን የሚወድ ሁሉ ራሱን ይካድ” የሚል ነው፡፡ ይህም ማለት የኋለኛው ትውልድ ራስን የሚወድ ከሆነ ጌታ የሚያዘው ደግሞ ራሱን መውደድ ሳይሆን ራስን መካድ ከሆነ ነገሩ “ሆድና ጀርባ” ሆኖአል ማለት ነው፡፡ ከዚህ አንጻር የዘመናችን ክሥተት በዚህ ፈተና ላይ ያለ እንደሆነ በግልጽ ማየት ይቻላል፡፡

ዛሬ የመንፈስ እናታቸው ብቻ ሳትሆን የማንነታቸውና የታሪካቸው ጭምር ማኅደር ከሆነች እናት ኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እያፈተለኩና እየኮበለሉ የሚገኙት በርካታ ወገኖች ራሱን ከመውደድ የተነሣ ካልሆነ በቀር ሌላ ትርጒም ሊሰጠው አይችልም፡፡

ክርስቶስ ሌላ አዲስ ክርስቲያን የፈጠረ ይመስል ክርስቲያን የሆነውን ሰው በተለያየ አባባል ወደሌላ የክርስቲያን ጎራ እንዲኮበልል መጣጣር አስኮብላይም ኮብላይም ራስን ከመውደድ የተነሣ የሚያደርጉት ነው እንጂ አንዳች የሚጨበጥ ክርስቲያናዊ ትርጒም የለውም፡፡

ራስን በመውደድ የሚታወቀው የዘመናችን ባሕርየ ሰብእ በዚህ ብቻ ሳይወሰን በትምህርትም በሐሳብም በአስተያየትም በሥራም ወዘተ የሚገለጸው ራስን ከፍ ከፍ የማድረግና የኔ ከሁሉ ይበልጣል እያሉ ሌላውን የማንኳሰስ አባዜ የሃይማኖት መዐዛ ምግባርን እየበከለው ይገኛል፡፡

ከዚህም የተነሣ የእኔ ዐውቅልሃለሁ ባይነት ዝንባሌ ሥር እየሰደደ ትሕትናና ፈሪሀ እግዚአብሔር የራቀው ትውልድ እየተበራከተ ይገኛል፡፡ ዛሬ እንደትናንቱ አበው ባሉት እንመራ፣ እንታዘዝ፣ አበውን እናዳምጥ የሚል ትውልድ ሳይሆን ከእናንተ ይልቅ እኛ እናውቃለንና እኛ የምንላችሁን ተቀበሉ በማለት ወደ ላይ አንጋጦ የሚናገር ራስ ወዳድ የሆነ መታዘዝን የሚጠላ ከሃይማኖታዊነት ይልቅ አመክንዮታዊነትን የሚያመልክ ትውልድ እየመጣ ነው፡፡ ይህ ራስ ወዳድ አስተሳሰብ የሚመነጨው ዘመኑ ካፈራው የሥነ ልቡና ፍልስፍና እንጂ ራሱን በመንፈስ ድሀ አድርጎና ሌላው ከእርሱ እንደሚሻል አድርጎ ከሚያስተምር በመንፈሰ እግዚአብሔር ከተጻፈው ከቅዱስ መጽሐፍ የመነጨ አይደለም፡፡
ቤተ ክርስቱያን ደግሞ መመሪያዋ በመንፈሰ እግዚአብሔር የተጻፈ ቅዱስ መጽሐፍ እንጂ በሰዎች ውሱን ጥበብ የተቀነባበረ ሰው ሠራሽ ፍልስፍናና ዘመን አመጣሽ ስልት አይደለም፡፡ በመሆኑም ቤተ ክርስቲያን ስትጠብቀው የኖረች ለወደፊም የምትጠብቀው በመንፈሰ እግዚአብሔር በታጀበ ጥበብና ስልት እንጂ ከፍልስፍና ብቻ በተገኘ የተውሶ ዕውቀት ሊሆን አይችልምና ሁሉም ሊያስብበት ይገባል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ለሁለት ሺሕ ዓመታት ያህል በአንድነትና በጥንካሬ ጠብቆ ያቆየ ጥበብ ኦርቶዶክሳዊና ሲኖዶሳዊ የሆነ የውሉደ ክህነት አመራር ጥበብ እንጂ የምዕራባውያንና የሉትራውያን ምክር ቤታዊና ዘመን አመጣሽ ፍልስፍና አይደለም የቤተ ክርስቲያናችን መርሕ እንደዚያ ቢሆን ኖሮ ዛሬ የምናያት አንዲት ሐዋርያዊትና ኀያል ቤተ ክርስቲያን ሳትሆን የተበታተነች የደከመችና መዐዛ ሐዋርያት የሌላትና የተለያች ቤተ ክርስቲያን ነበር የምናየው፡፡

ይሁን እንጂ አባቶቻችን ካህናት መሪዎች ሕዝቡ ተመሪ ሆኖ በአንድ የእዝ ሰንሰለት እየተደማመጠ ካህኑ ተናገረ ማለት እግዚአብሔር ተናገረ ማለት ነው በሚል ቅንና ትሕትና የተመላ ታዛዥነት እንደዚሁም በውሉደ ክህነት አመራር ሰጪነት የቤተ ክርስቲያናችን አንድነት እስከዛሬ ድረስ ተጠብቆ ቆይቷል፡፡

አሁን ግን ይህ ቀርቶ በአባቶች ላይ ተደራቢ አመራር ሰጪ በአባቶች ላይ የስድብ ናዳ አውራጅ ትውልድ መበራከቱን ካየንና ከሰማን ውለን አድረናል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ከጎናችን ሳይሆኑ ከጎናችሁ አለን የሚሉ ወገኖችም ስለ ድርጊቱ አፍራሽነት በተመለከተ አንድ ቀንስንኳ የተቃውሞ ሐሳብ አለመሰንዘራቸው በስተጀርባው እነርሱ ራሳቸው ያሉበት እንደሆነ የሚያመለክት መስሎ አሳይቶባቸዋል፡፡

አሁን ዋናው ጥያቄ ይህ ራስ ወዳድ የሆነውን አመለካከት ተቀብሎ የሚመጣውን ጥፋት ማስተናገድ ይሻላል ወይስ ራስን መካድ የሚለውን የጌታ ትምህርት አሥርጾ ነገሮች ሁሉ በንስሓ ወደነበሩበት መመለስ ምርጫው ለዚህ ዐቢይ ጉባኤ አቅርበነዋል፡፡

በሌላ በኩል ቤተ ክርስቲያናችን ያላትን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ተልእኮ በሚገባ ለማከናወን ግልጽነታችንና ታማኝነትን በማረጋገጥ መልካም አስተዳደርን ማስፈን ለነገ የማይባል የቤተ ክርስቲያኒቱን ዐቢይ አጀንዳ ሆኖ ይገኛል፡፡ ከዚህ አኳያ የቤተ ክርስቲያናችንን ዙሪያ መለስ ምጣኔ ሀብት በሚገባ ለመያዝና ለማሳደግ እንዲሁም የሰው ኀይላችንን በአግባቡ ለመጠቀም የዘመኑን አሠራር መከተል የግድ ያስፈልገዋል፡፡

ሌላው በሀገራችን እየተመዘገበ ያለውን የልማትና የእድገት ግንባታ በአስተማማኝ ለማስቀጠል የሕዝቡን አንድነትና ሰላም ማረጋገጥ ወሳኝነት አለው ፣ ቤተ ክርስቲያናችን ከሆነ ጀምሮ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሰላም እናት ሆና ሕዝቡን በማስተማር ያስመዘገበችው ጒልህ ታሪክ ዛሬም ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ ሁላችንም የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ኀላፊነታችንን እንድንወጣ በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም፡ ይህ ቅዱስ ጉባኤ የቤተ ክርስቲያኒቱን አንኳርና ዐበይት ጉዳዮችን በጥልቀት በመመርመርና በማጥናት ለቤተ ክርስቲያናችን ሊጠቅሙ የሚችሉ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ጉባኤው እንዲቀጥል እያሳሰብን ዓመታዊው የጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ መከፈቱን በእግዚአብሔር ስም እናበስራለን፡፡

እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ ይቀድስ ሀገራችንንም ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!