ጥር 11 ቀን 2009 ዓ.ም. በበዓለ ጥምቀት የተላለፈ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ሆናችሁ ይህንን ታላቅ በዓል በማክበር ላይ የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፤

በተጠምቆቱ ለዳግም ልደትና ለሐዲስ ሥርዐት ያበቃን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት በዓለ ጥምቀቱ አደረሳችሁ።

“ወይርአይ ኵሉ ዘነፍስ አድኅኖቶ ለእግዚአብሔር
ነፍስ ሁሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ።”
(ሉቃ. 3፥6)

ከዚህ ሕያው ቃል መገንዘብ እንደሚቻለው ዓለም ወይም ሥጋ የለበሰ ነፍስ ሁሉ በጽኑ ደዌ ኀጢአት ተይዞ እንደነበረ ነው፣ ያ ባይሆን ኖሮ ስለ መዳን ማንሣቱ ወይም ማውራቱ ተገቢ አይሆንም ነበርና ነው፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ በስፋት ተጽፎ እንደምናገኘው፣ በቅዱስ ትውፊትም እንደተረዳነው፣ ከመጀመሪያው ሰው ከአዳም ጀምሮ እስከ ዘመነ ክርስቶስ ድረስ በኀጢአተ-አዳም ምክንያት ደዌ ኀጢአት ሥጋ በለበሰ ሁሉ ላይ ተሰራጭቶአል፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ ይህንን እውነታ ሲያረጋግጥ እንዲህ ይላል፡- “ሁሉም ኀጢአትን ሠርተዋልና የእግዚአብሔር ክብር ጐድሎአቸዋል” (ሮሜ 3፥23)፡፡

የኀጢአትም ደመወዝ ሞት በመሆኑ በተሰራጨው ደዌ ኀጢአት ምክንያት ሞት በሰው ሁሉ ላይ እንደተዳረሰ ለማንም ግልጽ ነው (ሮሜ 6፥23፤ 5፥12)፡፡ በመሆኑም ከቀዳማዊ አዳም ጀምሮ እስከ ዳግማዊ አዳም እስከ ክርስቶስ ድረስ የሰው ልጅ በአጠቃላይ በኀጢአት፣ በሞትና በመቃብር ቊጥጥር ሥር ዋለ፡፡ ያ ዘመን የሰው ልጅ ስቃይና መከራ የተሞላ ሕይወትን ያሳለፈበት መራራ ዘመን በመሆኑ፣ ዓመተ ፍዳ፣ ዓመተ መርገም፣ ዓመተ ኵነኔ ተብሎ ተሰይሞአል (ሮሜ 5፥12-21)፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ ድቅድቅ የጨለማ ዘመንም ቢሆን፣ መሓሪውና ርኅሩኁ አምላካችን እግዚአብሔር የመዳን ተስፋ እንደሚመጣ በቅዱሳን ነቢያት አማካኝነት ተስፋውን በተደጋጋሚ ይገልጽ ነበር፡፡ በተለይም የሞትና የመቃብር ዋና መልእክተኛ ሆኖ ሰውን ሁሉ ለከባድ ጕዳት የዳረገው ደዌ ኀጢአት በጥምቀተ ማይና በልደተ መንፈስ እንደሚወገድ እግዚአብሔር በሚከተለው አገላለጽ አስታውቆ ነበር፡፡ እንዲህ ብሎ “እነዝኀክሙ በማይ ንጹሕ ወትነጽሑ እምርኵሰክሙ፤ በንጹሕ ውኃ እረጫችኋለሁ ከርኵሰታችሁም ትነፃላችሁ”፤ (ሕዝ. 36፥25)፤ “ወእሰውጥ መንፈስየ ዲበ ኵሉ ዘሥጋ፤ መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ አፈስሳለሁ” (ኢዩ. 2፥28)፡፡ ኀጢአት ወንድ ሴት፣ ሕፃን ሽማግሌ፣ ቀለም ዘር ሳይለይ የሰው ዘር የሆነውን ሁሉ በጅምላ ያሰቃየ ክፉ በሽታ ቢሆንም፣ ከጊዜ በኋላ አስተማማኝ የሆነ መድኀኒት እንደሚገኝለት ተስፋውን በዚህ ሁኔታ ሲገልጽ የቆየው መሓሪው አባታችን እግዚአብሔር አምላክ በመድኀኒትነቱ ይፈውሰን ዘንድ፣ የባህሕርይ ልጁ የሆነውን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በሥጋ-ሰብእ ወደ እኛ ላከው፡፡ ጌታችንም ወደኛ መጥቶ በሰው ፈንታ ለሰው ሁሉ ቤዛ ሆኖ በመሞት የድኅነት በሩን ከፈተልን፡፡

ክብርና ምስጋና ለእርሱ ይሁንና ዛሬ የመዳን ዘመን ሆኖልናል፡፡ ዘመናችን በሃይማኖት፣ በንስሐና በጥምቀት ምሕረት በገፍ የሚታፈስበት ስለሆነ “ ዓመተ ምሕረት፣ መዋዕለ ንስሓ፣ ዘመነ ሥጋዌ” እየተባለ ይጠራል፤ ዛሬ ደዌ ኀጢአትን በሃይማኖት፣ በንስሓና በጥምቀት ማስወገድ ይቻላል፡፡ ታዲያ ይህ ሁሉ የሆነው የእግዚአብሔር የማዳን ኀይል በሆነው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ነውና ሰው ሁሉ ይህንን የማዳን ኀይል እንዲመለከትና እንዲፈወስ የእግዚአብሔር መንግሥት ማእከል የሆነች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዛሬም እመኑ፣ ንስሓም ግቡ፣ መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና እያለች ድምፅዋን ከፍ አድርጋ ትጣራለች፡፡ የጥምቀተ ክርስቶስን በዓል የምናከብርበት ዐቢይ ምክንያት ይህንን የመዳን ጥሪ በማስተጋባት ሰውን ከደዌ ኀጢአት ለማዳን ነው፡፡ በዓለ ጥምቀትን ስናከብር እግዚአብሔር ወልድ በፈለገ ዮርዳኖስ ሲጠመቅ፣ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ሲወርድ፣ እግዚአብሔር አብ በደመና ሆኖ ድምፁን ሲያሰማ፣ እግዚአብሔር በአካል ሦስት በባሕርይና በህልውና አንድ መሆኑን እናውቃለን፡፡ በዓለ ጥምቀትን ስናከብር አብ በደመና ሆኖ “ይህ የምወደው ልጄ ነው ብሎ ሲመሰክር፣ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል በክርስቶስ ላይ ሲቀመጥ አይተን፣ በዚሁ ጥምቀተ ክርስትና ከደዌ ኀጢአት ድነን የእግዚአብሔር ልጆች፣ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪዎች የመሆን ትልቅ ጸጋ የምንቀዳጅ መሆናችንን እንገነዘባለን፡፡

በዓለ ጥምቀትን ስናከብር “ሰማያት ሲከፈቱ ተመልክተን ጥንት በግብረ ኀጢአት መነሻነት ከገነተ ተድላ የተባረርን እኛ፣ ጌታችን በእኛ ፈንታ ቤዛ ሆኖ በከፈለልን መሥዋዕትነት ምክንያት፣ ከምሥጢረ ጥምቀት ከምናገኘው ጸጋ የተነሣ ከኀጢአት ነጽተን የእግዚአብሔር ልጆችና የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያዎች ስንሆን፣ መንግሥተ ሰማያት ለእኛ ክፍት መሆኗን እናስተውላለን፡፡ በዓለ ጥምቀት ይህን ሁሉ የመዳን ጸጋና ምሥጢር የምንማርበትና የምናውቅበት፣ እንደዚሁም በሃይማኖት፣ በንስሓና በጥምቀት የመዳን ቍልፉን እጅ የምናደርግበት ልዩ፣ ታላቅና ቅዱስ በዓል በመሆኑ በታላቅ ድምቀት ማክበራችን ተገቢ ብቻ ሳይሆን ከተገቢም በላይ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ከእግዚአብሔር ተልኮ እንደነገረን ይህንን ታላቅ በዓል ከላይ የተገለጸውን የእግዚአብሔር የማዳን ኀይል ብቻ በመመልከት በዓሉን ማክበር አለብን፡፡ በሌላ በኩል በዓለ ጥምቀትን ስናከብር ማየት ያለብን የመዳን ገጽታውን ብቻ አይደለም፤ በማኅበራዊ ገጽታውም ትልቅ ፋይዳ ያለው በዓል እንደሆነ ማስተዋል አለብን፡፡ በዓሉ ዛሬ የሀገራችንም ሆነ የዓለማችን የልማት ዕንቅፋት እንደሆነ በስፋት የሚነገርለት የራስ ያልሆነውን ሀብት በተለያየ መንገድ የራስ ለማድረግ የሚደረገውን አዝማሚያ በመቃወም “በማንም ላይ ግፍ አትሥሩ፤ ደመወዛችሁ ይብቃችሁ፤ ከታዘዘላችሁ በላይ አብዝታችሁ አትውሰዱ” ብሎ የሚያስተምር ስለሆነ ሙስናን ከሁሉ ቀደሞ ያወገዘ በዓል ነው፡፡ ይህ በዓል ሁሉም ተጋግዞ፣ ተረዳድቶና ተዛዝኖ በሰላም፣ በፍቅር፣ በስምምነት፣ በአንድነት፣ በእኩልነት፣ በመከባበርና በመተማመን ይኖር ዘንድ “ሁለት ልብስ ያለው ለሌለው ያካፍል፤ ምግብ ያለውም እንዲሁ ለሌለው ያካፍል፤ ማንም ሰው ወገኑን በሐሰት አይክሰስ፤” በማለት መጨካከንን ያስቀረ በዓል ነው፡፡ የእገሌ ልጆች ነን እያሉ አባትን በመጥራትና የዘር ሐረግን በመምዘዝ መመካትን ያወገዘ፤ ይልቁንም ከዚህ በተለየ መልኩ መልካም የሥራ ፍሬን በማሳየት የሃይማኖትና የሥራ ታታሪ መሆንን የሚያስተምር ልማታዊ በዓል ነው (ሉቃ. 3፥8-14)፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የበዓለ ጥምቀትን አከባበር ሃይማኖታዊና ማኅበራዊ አስተምህሮን አጒልቶ ሊያሳይ በሚያስችል መልኩ በየጎዳናው፣ በየመንደሩ፣ በየወንዙ ቅዱስ የሆነውን የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ታቦት ይዛ እግዚአብሔርን በመዝሙር፣ በጭብጨባ፣ በሆታ፣ በዕልልታ፣ በውዳሴ፣ በማሕሌት፣ በቅኔ፣ በስብከተ ወንጌል ፣ በጸሎት የከበረውን ውኃ ባርኮ በመርጨት ልዩና ደማቅ በሆነ የአምልኮ ጒዞ እንዲከበር በማድረጓ ለኢትዮጵያ ሀገራችን ልዩ የሆነ መለኮታዊ ግርማ ሞገስን አጎናጽፋ ትገኛለች፡፡ መላ የሀገሪቱ ሕዝብ በነፃነት፣ በአንድነት በደስታና በፍቅር ከቤተ ክርስቲያኑ አንሥቶ እስከ ባሕረ ጥምቀቱ፣ ከባሕረ ጥምቀቱ እስከ ቤተ ክርስቲያኑ ድረስ እንደ ዐባይ ወንዝ እየተመመ ምንም መለያየት ሳይኖር፣ ጥላቻ ሳያጋጥም፣ ከኃምሳ ሚሊየን በላይ የሚሆን ሕዝብ በየቋንቋው፣ በየባህሉ ፈጣሪውን እያመሰገነ ሕብረ ብዙ የሆነ የእግዚአብሔር ሠራዊት ሆኖ ከዳር እስከ ዳር ሲተም በፊቱ ከደስታ ሌላ የሚታይ ነገር ሳይኖር ማክበር ማለት፣ ይህ ሁሉን የሚገዛ የእግዚአብሔር ኀይል መገለጫ ነው ከማለት ሌላ ሊገልጸው የሚችል አገላለጽ አይኖርም፡፡ ይህ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅድስና ሕይወትና የሥራ ፍሬ ምን ያህል ታላቅ እንደሆነ የሚያረጋግጥ ሕያው ምስክር ነው፡፡

ይህ በዓል የኢትዮጵያውያን ቅዱሳን አበው የማይፈርስ ጽኑ ግንብ ነው፡፡ ይህ በዓል የኢትዮጵያና የእግዚአብሔር የሆነ ጽኑ የቃል ኪዳን ትስስር የሚያረጋግጥ ማስረጃ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን ይህንን ጸጋ እግዚአብሔር እስከ መጨረሻው ሊጠብቁትና ሊንከባከቡት፣ ሊያሳድጉትና ሊያበለጽጉት እንደዚሁም በተባበሩት መንግሥታት የባህል የሳይንስና የትምህርት ድርጅት በማስመዝገብ ፣ ለዓለም ሊያስተዋውቁትና የማኅበራዊነት ጸጋ ሊያስተምሩበት ይገባል፤ በዓለ ጥምቀት መተኪያ የማይገኘለት የኢትዮጵያውያን ታላቁና ግርማ ሞገስ የተሞላ በዓላችን ነው፤ በዓሉን ልዩ የሚያደርገው ሕዝቡ አንድ ሆኖ ከእግዚአብሔር ጋር የሚጓዝበት ቀን በመሆኑ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር የሚጓዝ ሕዝብ ግርማ ሞገሱ ይህ ነው ተብሎ አይነገርም፤ ከቋንቋ በላይ ነውና፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መላ የኢትዮጵያ ሕዝቦችን በእኩልነት ተቀብላ የምታስተናግድ የሁሉም ሕዝቦች ቅን አገልጋይና እናት መሆኗን በተጨባጭ የሚመሰክር ይህ የጥምቀት በዓላችን ነው፡፡ በዓሉ የኢትዮጵያ ሕዝብን በአንድነት አስተሳስሮ የሚኖር፣ የሁሉም ሕዝቦች ቋንቋና ባህል በእኩልነት አስተናግዶ በመከባበር፣ በመተማመንና በወንድማማችነት ስሜት ጠብቆ ሕዝቡን እርስበርስ የሚያቀራርብና የሚያስተሳስር በመሆኑ ከዚህ የበለጠ የነበረ፣ ያለና የሚኖር በዓል ይኖራል ተብሎ አይገመትም፡፡ በመሆኑም በዓለ ጥምቀትን ማክበር ማለት ኢትዮጵያ ያላትን ሰማያዊና ምድራዊ ገጽታ ምን እንደሚመስል በሚገባ ማየት ማለት ነው፡፡ በዓለ ጥምቀት ማለት የኢትዮጵያን ግርማ ሞገስ ኀይልና ክብር በትክክል መገንዘብ መቻል ማለት ነው፡፡ በዓለ ጥምቀት የኢትዮጵያን ሕዝቦች አንድነት መጠበቂያ ጠንካራ ኀይል እንደሆነ በተግባር የሚያሳይ ሃይማኖታዊ ዕሴት ነው፡፡

በመጨረሻም፡ የቀደሙት ኢትዮጵያውያን አበው የበዓለ ጥምቀትን ሃይማኖታዊ ማኅበራዊና ሥነ ምግባራዊ ጠቀሜታ ግምት ውስጥ በማስገባት “ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ” ብለው ሃይማኖታዊ ማኅበራዊና ባህላዊ ጸጋቸውንና ክብራቸውን እንዳወረሱን፤ እኛም የእግዚአብሔርን ማዳን በመመልከት እንደዚሁም የኢትዮጵያ ግርማ ሞገስ የሆነውን ይህን በዓል በማክበርና በመጠበቅ ሕዝባችንም ኑሮውን በፍቅር፣ በአንድነት፣ በስምምነት፣ በእኩልነትና በሰላም እየቃኘ እንደጀመረው ለልማትና ለእድገት እንዲተጋ በማነሣሣት ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ተልእኮአችንን እንድንወጣ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡ መልካም የጥምቀት በዓል ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡