የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የውጭ አህጉር ሐዋርያዊ ጒዞ
መድኀኔ ዓለም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላካዊ የማዳን ሥራውን ወደ ዓለም እንዲያዳርሱ ዐሥራ ሁለት ደቀ መዛሙርትን ከዐሥራ ሁለቱ ነገደ እስራኤል መርጦ ለሦስት ዓመት ከአራት ወር ከዐሥር ቀን አምላካዊ ትምህርተ ወንጌልን አስተምሮአቸዋል፡፡ ከዋለበት እየዋሉ ካደረበት እያደሩ አምላካዊ ትምህርቱን ሰምተው፣ መለኮታዊ ገቢረ ተኣምሩን አይተው፣ ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ መሆኑን ተረድተዋል፡፡ (ዮሐ. 6) ካመኑ በኋላ “ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ ወንጌልን ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ፤ ያመነ የተጠመቀ ይድናል ያላመነ ግን ይፈረድበታል”፡፡ (ማር.16፥15-16) ብሎ አዘዛቸው፡፡
በክርስትና ትምህርት ይህ ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ የሰጠው ወንጌልን ለዓለም ሁሉ የማስተማር (የመስበክ) ተልእኮ “ዐቢይ ተልእኮ” (great mission) ተብሎ ይጠራል፡፡