ከግንቦት 1 ቀን እስከ ሰኔ 14 ቀን 2009 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡

ከግንቦት 1 እስከ ግንቦት 14 ቀን 2009 ዓ.ም የተደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡ በመጀመሪያም በ2008 ዓ.ም. ርክበ ክህነት ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አዳዲስ ኤጲስ ቆጶሳትን መርጦ ክፍት በሆኑ አህጉረ ስብከት ለመሾም ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት ጊዜውን መዋጀት የሚችሉ ቆሞሳትን መልምለው የሚያቀርቡ ከቅዱስ ሲኖዶስ አባላት መካከል የተወሰኑ አባቶችን በኮሚቴነት በተሰየሙ ሊቃነ ጳጳሳት አቅራቢነት የሊቃነ ጳጳሳቱ ኮሚቴ በዕጩነት መልምሎ ካአቀረባቸው 108 ቆሞሳት መካከል 31 ቆሞሳትን ጨምቆ በማውጣት ለሢመተ ጵጵስና ውድድር በማቅረቡ ከግንቦት 1 ቀን እስከ ግንቦት 14 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ የተካኼደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ኮሚቴው ጨምቆ ካአቀረባቸው 31 ቆሞሳት ውስጥ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው፣ በሁለገብ ዕውቀታቸውና በአገልግሎታቸው ያመዝናሉ፤ ጊዜውንም ይዋጃሉ ብሎ ያመነባቸውን 16 ቆሞሳት ብቻ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ ከአድባራትና ከገዳማት፣ ከአብነት ት/ቤቶች፣ ከውስጥና ከውጭ አህጉረ ስብከት በጥልቀት አጣርቶና እንደገና ጨምቆ በማውጣት 16ቱን ቆሞሳት ብቻ ለሢመተ ጵጵስና መርጦአቸዋል፡፡ ለሢመተ ጵጵስና የተመረጡትም ቆሞሳት

1. ቆሞስ ዶ/ር አባ ኀይለ ማርያም መለሰ የጠ/ቤተ ክህነት ም/ሥራ አስኪያጅ፣
2. ሊቀ ሊቃውንት ቆሞስ አባ ዘርዐ ዳዊት ኀይለ ሥላሴ በአዲስ አበባ የመርካቶ ደብረ ኀይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ፣
3. መልአከ ምሕረት ቆሞስ አባ ሄኖክ ተክለ ጊዮርጊስ በአዲስ አበባ የመካኒሳ ቅዱስ ሚካኤል ደብር አስተዳዳሪ፣
4. መልአከ ኀይል ቆሞስ አባ ወልደ መድኅን ተክለ ብርሃን በአዲስ አበባ የዕንጦጦ ደብረ ኀይል ቅዱስ ራጉኤል ደብር አስተዳዳሪ፣
5. መልአከ ገነት ቆሞስ አባ ገብረ እግዚአብሔር ኀይሉ የመቀሌ ደብረ ገነት መድኀኔ ዓለም ደብር፣ የኪዳነ ምሕረትና የልደታ ለማርያም አብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪ፣
6. ቆሞስ አባ ገብረ ሥላሴ ተስፋ ከኢየሩሳሌም ገዳም፣
7. ቆሞስ አባ ኀይለ ሚካኤል ወልደ አምላክ በደብረ ሊባኖስ ገዳም የብሉያትና የሐዲሳት መምህር
8. ቆሞስ አባ ብርሃነ መስቀል ዕንቈ ባሕርይ በቅዱስ ላሊበላ ገዳም የብሉያትና የሐዲሳት መምህር፣
9. ቆሞስ አባ ዮሐንስ ገ/ሥላሴ የወላይታ ዳውሮና ኮንታ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ፣
10. ቆሞስ አባ ወልደ ሐና ጸጋው በባሕር ዳር ሀገረ ስብከት የሊቃውንት ጉባኤ ኀላፊ፣
11. መጋቤ አዕላፍ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ንጉሤ የጋምቤላ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ፣
12. መጋቤ ሐዲስ ቆሞስ አባ ሳሙኤል ገላነው የሰዋሰወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ መምህር፣
13. ቆሞስ አባ ፊልጶስ አሻግሬ በአሜሪካ የሚችጋን ደብረ ገነት አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪና በኒወርክ ሀገረ ስብከት የስብከተ ወንጌል ኀላፊ፣
14. ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ገብረ ሕይወት ፍሥሓ በጀርመን የሙኒክ ደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ፣
15. መልአከ ገነት ቆሞስ አባ ብርሃነ መስቀል ተድላ በጀርመን የበርሊን ደብረ ገነት ቅዱስ አማኑኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ፣
16. መልአከ ሕይወት ቆሞስ አባ ዘድንግል ኑርበገን በፓሪስ የፈለገ ሕይወት አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ሲሆኑ ሥርዐተ ሢመቱ ሐምሌ 9 ቀን 2009 ዓ.ም. እንደሚፈጸምና የሚሾሙበት ሀገረ ስብከትም በዚያው ወቅት እንደሚገለጽ ታውቋል፡፡

ከዚህም ሌላ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ባሳለፈው ውሳኔ ሚያዝያ 10 ቀን በሚነበበው መጽሐፈ ስንክሳርና በፍትሕ መንፈሳዊ መጽሐፍ ላይ ኢትዮጵያውያን ከራሳቸው ሊቃውንት ጳጳሳትን እንዳይሾሙ ማዕቀብ የሚጥለው በ7ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ግብጻውያን አበው በስርዋጽ ያስገቡት ሕገ ወጥ ጽሑፍ እንዲሰረዝ ወስኗል፡፡

እንዲሁም ከቤተ ክርስቲያናችን እምነትና ሥርዐት ውጭ በመደራጀት የኑፋቄ ትምህርት ሲያካሂድ የነበረው አሰግድ ሣህሉ የተባለው ግለሰብእ ለበርካታ ዓመታት የኑፋቄ ትምህርት ሲያሰራጭ መኖሩ በመረጃ የተደረሰበትና የተረጋገጠ በመሆኑ ከአሁን በኋላ የኑፋቄ ትምህርት ማሰራጨቱን እንዳይቀጥል ምልአተ ጉባኤው በአጽንዖት አውግዞታል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በሌሎችም ወቅታዊ በሆኑ የቤተ ክርስቲያኒቱ ዐበይት ጉዳዮች ላይ ከግንቦት 1 ቀን እስከ ግንቦት 14 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ ለሁለት ሱባኤያት ያህል በስፋትና በጥልቀት ተወያይቶ ልዩ ልዩ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡

በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጰያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች እንደሚከተለው አሳውቀዋል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ፣ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ በተደነገገው መሠረት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የዘንድሮውን መደበኛ የርክበ ካህናት ስብሰባ ከበዓሉ ዋዜማ ከግንቦት 1 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ለ14 ቀናት ያህል ሲወያይ ሰንብቷል፡፡ የቅዱስነታቸውን የጉባኤ መክፈቻ ሐዋርያዊ መልእክት በተመለከተ፡- በቤተ ክርስቲያኒቱ የሥራ ዘርፍ ዙሪያ እየተሠሩ ያሉትን ማኅበራውያን ተግባራት የዳሰሰ፣ በሀገራችን በአንዳንድ አካባቢ በዝናም እጥረት ምክንያት ድርቅ ባስከተለው ችግር ለተጎዱ ወገኖች ሊደረግ የሚገባውን ሰብኣዊ አገልግሎት ያገናዘበ፣ ለሀገራችንና ለቤተ ክርስቲያናችን ሁለንተናዊ እድገት የሚበጀውን በማመቻቸት በሁሉም አቅጣጫ ያለው ኅብረተሰብ የሥራ ተነሳችነቱን በበለጠ አጎልብቶ እንዲንቀሳቀስ የሚያስችል መልእክት መሆኑን ምልአተ ጉባኤው ተመልክቶ ለተላለፈው አጠቃላይ መመሪያ ትኲረት ሰጥቶ በቀረበው አጀንዳ ከተወያየ በኋላ በርከት ያሉ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡ ከውሳኔዎቹም መካከል ዋና ዋናዎቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡

1. ከፍ ብሎ እንደተገለጸው ሁሉ በአሁኑ ጊዜ በአገራችን በአንዳንድ አካባቢ በተከሠተው ድርቅ ለረኃብ የተጋለጡ ወገኖቻችንን ለመታደግ መንግሥት እያደረገ ያለውን ከፍተኛ ጥረት በመገንዘብ፣ ቤተ ክርስቲያናችንም የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ኀላፊነቱን ወስዶ ከእርዳታ ሰጪዎች ጋር በመነጋገርና በማስተባበር የሚገኘውን ርዳታ ድርቁ የተከሠተባቸው የክልል መሪዎች በሚሰጡት አቅጣጫ እንዲፈጸም ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
2. ከቤተ ክርስቲያናችን እምነትና ሥርዐት ውጭ በመደራጀት የኑፋቄ ትምህርት ሲያካሂድ የነበረው አሰግድ ሣህሉ የተባለ ግለሰብ ለበርካታ ዓመታት የኑፋቄ ትምርት ሲያሰራጭ መኖሩ በመረጃ የተደረሰበትና የተረጋገጠበት በመሆኑ ከአሁን በኋላ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም እንዳያስተምር፣ ምእመናንም እንዳይከተሉት ምልአተ ጉባኤው ከግንቦት 3 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ቃለ ውግዘት አስተላልፏል፡፡ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና ውጭ ምንም ዐይነት ፈቃድ ሳያገኙ በተመሳሳይ ሁኔታ አዳራሽ ተከራይተው በቤተ ክርስቲያናችን ስም ወንጌል እናስተምራለን ዝማሬ እናሰማለን የሚሉ ሕገ ወጦች ከእንዲህ ዐይነት ድርጊታቸው እንዲታረሙ፤ ምእመናንንም በተለይ ወጣቱ ትውልድ እንዲህ ዐይነት ሕገ ወጦችን ከመከተልና ሃይማኖታችሁን ከሚበርዙ ኀይሎች እንድትጠበቁ ቅዱስ ሲኖዶስ አበክሮ ያሳስባል፡፡
3. የቤተ ክርስቲያኒቱ መገናኛ ብዙኃን ጉዳይን በተመለከተ የሚዲያ ድርጅቱ በሰው ኀይል እንዲጠናከር፣ የሚያስተላልፋቸው መልእክቶችም ጥራት እንዲኖራቸው ማድረግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ተነጋግሮ ለ2010 በጀት ዓመት ብር12,000,000 (ዐሥራ ሁለት ሚሊየን ብር) ተፈቅዶለት በበጀት ተጠናክሮ ሥራውን እንዲቀጥል ተስማምቷል፡፡
4. በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስለ ዴር ሡልጣን ገዳም ችግር ጉዳይ ጉባኤው በስፋት ከተነጋገረ በኋላ ችግሩን አስመልክቶ መፍትሔ ማግኘት እንዲቻል ለኢፈዲሪ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ በኢትዮጵያ ለእስራኤል ኤምባሲና በእስራኤል ለኢትዮጵያ ኤምባሲ ደብዳቤ እንዲጻፍላቸው ተወስኗል፡፡
5. ሚያዝያ 10 ቀን በሚነበበው መጽሐፈ ስንክሳርና በፍትሕ መንፈሳዊ መጽሐፍ ላይ ኢትዮጵያውያን ከራሳቸው ሊቃውንት ጳጳሳትን አይሹሙ የሚለው በ7ኛው መቶ ዓመት ግብጻውያን አባቶች በስርዋጽ ያሰገቡት ሕገ ወጥ ጽሑፍ ስለሆነ ምልአተ ጉባኤው ተነጋግሮ ጽሑፉ የአገራችንና የቤተ ክርስቲያናችንን ክብር የሚነካ ሆኖ በመገኘቱ ከአሁን በኋላ ጽሑፉ እንዳይነበብ፤ ከመጻሕፍቱም ውስጥ እንዲወጣ ወደፊትም በሚታተሙ መጻሕፍት እንዳይገባ ተወስኗል፡፡
6. ሥርዓተ ምንኵስናና ሥልጣነ ክህነት አሰጣጥን አስመልክቶ ቀደም ባሉት ዓመታት የተወሰኑ ውሳኔዎች በአብዛኛው አፈጻጸም ላይ ችግሮች እንዳሉ ስለሚታይ ወደፊት የሚወሰነው ተጠብቆ እንዲሠራበት ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
7. ሕጋዊ ፈቃድ የሌላቸው ሰባክያንና አጥማቂዎች በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ አገልግሎት እንዳይሰጡ የተወሰነ ቢሆንም ውሳኔው መከበር ስላልቻለ ችግሮችም በስፋት የሚታዩ ስለሆነ አሁንም በውሳኔው መሠረት የቊጥጥሩ ሥራ ተጠናክሮ እንዲቀጠል ተስማምቷል፡፡
8. በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም በአዲስ አበባም ሆነ በየአህጉረ ስብከቱ በማኅበር ተደራጅተው ገዳማትን በማስጐብኘትም ሆነ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም በልዩ ልዩ አቅጣጫ የሚንቀሳቀሱ ማኅበራትን መቈጣጠር የሚቻልበት የማኅበራት ማደራጃ ደንብ እንዲወጣ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
9. የቤተ ክርስቲያኒቱ ሁለንተናዊ ችግር በባለሙያዎች ተጠንቶ እንዲቀርብ ቀደም ሲል በተወሰነው መሠረት ጥናቱ ተጠናቆ ከቀረበ በኋላ ጉባኤው ተመልክቶ የሕግ ባለሙያዎችና የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ባሉበት ተመርምሮና ተስተካክሎ ለጥቅምቱ 2010 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እንዲቀርብ ተወስኗል፡፡
10. የስብከተ ወንጌል መስፋፋት፣ የሰንበት ት/ቤትና የመንፈሳውያን ኮሌጆች መጠናከር የአብነት ት/ቤቶች መደራጀትና በበጀት እንዲደገፉ ማድረግ የቤተ ክርስቲያኒቱ ዐይነተኛ ተግባር መሆኑን ምልአተ ጉባኤው ተነጋግሮ በስብከተ ወንጌል ትምህርት አሰጣጥና በመንፈሳውያን ኮሌጆች ደቀመዛሙርት አያያዝ ጥብቅ ክትትል እንዲደረግ ጉባኤው ወስኗል፡፡
11. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የራሷ የሆነውን ሀብትና ቅርስ በባለቤትነት መጠበቅና ማስጠበቅ እንዲቻል ተዘጋጅቶ የቀረበውን ጥናት ቅዱስ ሲኖዶስ ካዳመጠና ከተወያየበት በኋላ የመጨረሻ ውሳኔ ለመስጠት በቅድሚያ በቋሚ ሲኖዶስ ታይቶ እንዲቀርብ ወስኗል፡፡
12. ብፁዓን አበው በሌሉባቸው አህጉረ ስብከት የሚመደቡ ዕጩዎች ቆሞሳት ምርጫን በተመለከተ ከሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የሚገኙ ቆሞሳትን በማወዳደር 16 ቆሞሳት ለኤጲስ ቆጶስነት ተመርጠዋል፤ በዓለ ሢመታቸውን ሐምሌ 9 ቀን 2009 ዓ.ም. እንዲፈጸም ተወስኗል፡፡
13. ኤጲስ ቆጶሳት የሌሉባቸውን የውጭ አህጉረ ስብከት በተመለከተም በጥቅምቱ 2010 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እየታየና እየተጠና ብፁዓን አበው እንዲመደቡባቸው ለማድረግ ቅዱስ ሲኖዶስ ተስማምቷል፡፡
14. በኦሮምያ ክልል በሰባት ዞኖች በሚገኙ ዩንቨርሲቲዎች የሚማሩ ተማሪዎች መንፈሳዊውን ትምህርት በቋንቋችን እንዳንማር ማኀበረ ቅዱሳን በደል አድርሶብናል በሚል ባቀረቡት አቤቱታ ዩንቨርሲቲዎቹ ያሉበት አህጉረ ስብከት ጉዳዩን ግራና ቀኝ አጣርተውና ተመልክተው መፍትሔ እንዲሰጡና ውጤቱ ለቅዱስ ሲኖዶስ እንዲቀርብ ተወስኗል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ በላይ በተገለጹት የውሳኔ ነጥቦችና በሌሎችም ዐበይት ጉዳዮች ላይ ለ14 ቀናት ሲወያይ ሰንብቶ ስብሰባውን በጸሎት አጠናቋል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፡፡ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡