ታኅሣሥ 28 ቀን 2012 ዓ.ም፡ የበዓለ ልደት ቃለ በረከት አስተላልፈዋል
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤ የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤ በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ በልደቱ “ሰላም በምድር ይሁን” የሚል የሰላም መዝሙርን ያሰማን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ ሁለተኛው ዓመት በዓለ ልደቱ በሰላም አደረሳችሁ !!
‹‹ተወልደ እምአመቱ ወሰላመ ገብረ በልደቱ፤
ከአገልጋዩ ተወለደ፤ በልደቱም ሰላምን አደረገ።››
(ቅዱስ ያሬድ)
በዓለ ልደተ ክርስቶስን ባነሣን ቊጥር በኅሊናችን ፈጥኖ የሚታወሰን ትልቅ ትዝታ፣ መላእክትና እረኞች በቤተልሔም ተገኝተው ‹‹‹ ሰላም በምድር ይሁን›› በማለት በአንድነት የዘመሩትን መዝሙር ነው፤በእርግጥም ይህ መዝሙር ጌታችን ሰው ሆኖ ከቅድስት ድንግል ማርያም በመወለድ በዚህ ዓለም የተገለጠበትን ምሥጢር የሚተረጕም ነው፡፡ ሁሉም እንደሚገነዘበው የሰላም ዋጋና ጣዕም በሰማይም ሆነ በምድር መተኪያ የማይገኝለት ነው፤በሰውና በእግዚአብሔር፣ በሰውና በመላእክት እንደዚሁም በሰውና በሰው መካከል ተገድግዶ የነበረው የጥል ግድግዳ ለሰው ብቻ ሳይሆን ለመላእክት ተልእኮም ዕንቅፋት መሆኑ አልቀረም፤ ምክንያቱም መላእክት በአርኣያ እግዚአብሔር የተፈጠረው ሰው ከቅድስና ስፍራ ተባርሮ በጐስቋላ ሕይወት ኑሮውን ሲገፋ ባዩ ቊጥር ደስታቸው ፍጹም አልነበረምና ነው፡፡ የቅዱሳን መላእክት ደስታ ፍጹም የሚሆነው ሰዎች በተመደበላቸው የክብር ስፍራ ሲገኙ እንደሆነ “በአንድ ሰው ንስሓ መግባት በሰማይ ታላቅ ደስታ ይሆናል” ተብሎ የተነገረው አምላካዊ ቃል በቂ ማስረጃ ነው፡፡ በልደተ ክርስቶስ ቀን ግን ከዚህም አልፎ በጐስቋላ ይሕወት ይማቅቅ የነበረው ሰው በተዋሕዶተ መለኮት በመንበረ ጸባኦት ዙፋን ተቀምጦ አይተዋል፤ከዚህም በመነሣት እግዚአብሔር ሰውን ከመታረቁና ከመሙደዱም በላይ በተዋሕዶ የሰው አካልና ባሕርይን የራሱ አካልና ባሕርይ ማድረጉን አስተውለዋል፡፡ በዚህ ጊዜ ነበር የሆነው ድርጊት በትክክል ሊገልጥ በሚችል አገላለጽ ‹‹እግዚአብሔር ሰውን በእጅጉ ወደደው በሰላምም ጐበኘው፤ ይህንንም ስላደረገ ከፍ ያለ ምስጋና ለእግዚአብሔር ይገባል›› በማለት መላእክትና ሰዎች የዘመሩት፣ መዝሙር በደማቅ ብርሃን የታጀበ ሰማያውያን ሠራዊትና ሰዎች በአንድነት የተሳተፉበት ድንቅ የሆነ የሰላም መዝሙር ነበር፡፡
ሰላም ለምድራውያን ብቻ ሳይሆን ለሰማያውያንም ውድና በጣም ተፈላጊ ስለ መሆኗ በልደተ ክርስቶስ ዕለት የተፈጸመው ሁናቴ ትልቅ መምህራችን ነው፤ያለ ሰላም ሃይማኖታዊ ሥርዐትን በአግባቡ ማካሄድ አይቻልም፤ ትምህርተ ሃይማኖትን አስተምሮ ማሳመንም አይቻልም፤ ሰላም ሳይኖር በልቶ፣ ጠጥቶና አጊጦ መኖር አይቻልም፤ ሰላም ሳይኖር ተምሮ መመረቅ፣ነግዶ ማትረፍ፣ አርሶ ማምረት፣ወልዶ ማሳደግ፣ድሮ መኳል የለም፤ሰላም ከደፈረሰ የኅብረተሰብ ኑሮ ይናጋል፤ ልማት ይቆማል፣ ድህነትና ችግር ይንሰራፋል፤ በመሆኑም የሰላም ጥያቄ የህልውና ቊጥር አንድ ጥያቄ መሆኑን ተገንዝበን ትልቁም ትንሹም፣ ሕዝብም መንግሥትም ከምንም በላይ ለሰላም ያለመታከት መሥራት አለብን፡፡ በዛሬው ዕለት የምናከብረው በዓለ ልደተ ክርስቶስም ለሰላም ተብሎ የሚከበር በዓል መሆኑን ማጤን ተገቢ ነው፤ይህ በዓል አካላዊ ቃል የሆነው እግዚአብሔር ወልድ አካላችንን አካል እስከ ማድረግ ደርሶ ምሕረትንና ይቅርታን ለሁላችን ማድረጉን በማስተማር የሚከበር በዓል ነው፡፡ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በልደቱ ሰላምን የሰበከልን፣ለሰው ልጆች በዚህም ሆነ በወዲያኛው ዓለም ከሰላም የበለጠ አስፈላጊ ነገር እንደሌለ ስለሚያውቅ ነው፤ሰላም ካለ ሌላው ሁሉ በሰላም ውስጥ ይገኛልና፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፡ ዛሬ በዓለም ዙሪያ ሁሉ የሚስተዋለው የጦርነት ሥጋት፣ የበሽታዎች መዛመት፣ የስደተኞች ንረት፣ የፍትሕና የእኩልነት መዛባት ምንጫቸው የሰላም ዕጦት እንደሆነ አንስተውም፤ የሰው ኅሊና በሰላም አየር የተሞላ ቢሆን ኖሮ ሥጋቱ ይቀርና ለአጥፊ መሣሪያና ለመሳሰለው የሚወጣው ወጪ ለልማትና ለድሆች ድጋፍ ይውል ነበር፣ የዓለማችንን ችግር ለማስወገድ ለጦርነት የሚወጣው ወጭ ከበቂም በላይ እንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ እግዚአብሔር በሀብተ ጸጋ የተሞላች ምድር ቢሰጠንም በራሳችን ደካማ አያያዝና የተሳሳተ አመለካከት ወደ ድህነት እየቀየርናት ነው፤ለሰው ልጆች ሰላምና ደግነት መጠበቂያ የሆነው ትምህርተ ሃይማኖትም ለነገር ትንኮሳና ለጠብ መጫሪያነት መጠቀም የተለመደ ሆኖአል፤ ነገር ግን የሃይማኖት ትንኮሳ ሌላውን ሳይሆን ተመልሶ ራስን ለባሰ አደጋ የሚያጋልጥ መሆኑን ሃይማኖታውያን ሁሉ በውል መገንዘብ ይኖርብናል፡፡
በተለይም ወጣት ልጆቻችን፣ እርስ በርስ ተፋቀሩ እንጂ ተጣሉ የሚል ሃይማኖት የሌለ መሆኑን፣ ነፍስን አድኑ እንጂ ግደሉ የሚል ሃይማትም እንደሌለ በትክክል ልታውቁ ይገባል፤ የሃይማኖት አስተምህሮ ምን ጊዜም ሰላምና ፍቅር ብቻ ነው፤ይህንን በቅጡ ያልተገነዘቡ ወገኖች ስሕተት ቢፈጽሙ እንኳ ስሕተትን በስሕተት ማረም ፍጽሞ አይቻልም፤ ስሕተት በሕግና በትምህርት ብቻ እንዲታረም ማድረግ እንጂ በስሕተት ላይ ስሕተት፣ በጥፋት ላይ ጥፋት በማከል ችግርን ማስፋፋት መፍትሔ አያመጣም ፡፡ የጐበጠውን ለማቅናት እንጂ የበለጠ እንዲጎብጥ ለማድረግ እግዚአብሔር እኛን አልጠራንምና በተጠራንበት ጥሪ ጸንቶ መኖር ከኛ ይጠበቃል፡፡ እኛ ክርስቲያኖች በዓለ ልደትን ስናከብር ሀገራዊ አንድነታችንንና ሁለንተናዊ ሰላማችንን ለማረጋገጥ ቃል መግባት ከሁላችን ይጠበቃል፡፡ ከዚሁም ጋር በልዩ ልዩ ምክንያት ችግር አጋጥሞአቸው የሚበሉትንና የሚጠጡትን፣ የሚለብሱትንና የሚጠለሉበትን ያጡ ወገኖችቻን ካለን በማካፈል በዓሉን ከኛ ጋር በደስታ እንዲያሳልፉ ማድረግ ይገባናል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ በዚህ ሁሉ ሃይማኖታዊ ግዴታውን እንዲወጣ አባታዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡
በመጨረሻም፤ ያለ ሰላምና መረጋጋት መምረጥም ሆነ መመረጥ፣ መምራትም ሆነ መመራት እንደሌለ ሁላችንም እናውቃለን፤ በመሆኑም ሁሉም የፖለቲካ ተፎካካሪ ፓርቲዎችና የሚድያ ባለሙያዎች የሀገርን ሰላምና አንድነትን ተቀዳሚ አጀንዳ አድርጋችሁ ኀላፊነት ባልተለየው ጥበብ ሥራችሁን እንድታከናውኑ፣ ሕዝቡም በተለይም ወጣቱ ትውልድ ሰላምን ከሚያደፈርሱ ተግባራት ተቈጥቦ፣ በምትኩ ሠርቶ የሚያተርፍበትን አማራጭ በማፈላለግ ለሀገር ልማት እንዲነሣሣ አደራ ጭምር አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡
መልካም በዓለ ልደት ያድርግልን እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ‹‹ወስብሐት ለእግዚአብሔር››