በ36ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ የሰበካ አሰተዳደር ጉባኤ ከጥቅምት 6-9 ቀን 2010 ዓ.ም አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

መጋቤ ኵሉ ወመሴስየ ኵሉ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር ከያለንበት ሰብስቦ በዚህ የሠላሳ ስድስተኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ተገኝተን ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ለመወያየት ስለተሰበሰብን በቅድሚያ አምላካችንን እናመሰግናለን፡፡ እናንተም እንኳን አደረሳችሁ እንኳንም በደኅና መጣችሁ እንላለን!!

“መኑ እንጋ ገብር ምእመን ወጠቢብ ዘይሠይሞ እግዚኡ ውስተ ቤቱ ከመ የሀቦሙ ሲሳዮሙ በበጊዜሁ — ምግባቸውን በየጊዜው ይሰጣቸው ዘንድ ጌታው በቤተ ሰቦዎቹ ላይ የሚሾመው ታማኝና መልካም አገልጋይ ማን ነው” (ማቴ. 24፥45)

ይህ አረፍተ ነገር ጌታ በቤተሰቡ ላይ የሚሾመውን ታማኝ አገልጋይ አስመልክቶ በትእምርተ ጥያቄ ያስተማረው ትምህርት ነው፡፡ የትምህርቱ ይዘት በጥያቄ መልክ የቀረበ እንደመሆኑ መጠን ከእያንዳንዳችን መልስ የሚያስፈልገው እንደሆነም በግልጽ ይታያል፡፡ በዚህ ትምህርት መሠረተ ሐሳብ የክርስቶስ ተከታዮች የሆኑ ምእመናን በአጠቃላይ የጌታ ቤተሰብ እንደሆኑ በሚገባ ተቀምጦአል፤ በጌታና በቤተሰቡ መካከል ያለው ግንኙነት ምን ያህል ጥብቅ እንደሆነ ሁላችንም እናውቃለን፤ ጌታ ለሚወዳቸውና ለሚያስብላቸው ቤተ ሰቦቹ እጅግ ታማኝና መልካም አገልጋይ ሲፈልግ መገኘቱ ቤተ ሰቡን እጅግ የሚወድና ለቤተሰቡ የሚቈረቈር፥ የሚያስብና የሚጠነቀቅ መሆኑን የሚያመለክት ማስረጃ ነው፡፡

በመሆኑም በጌታ በቤተ ሰቡና በአገልጋዩ መካከል ያለው ግንኙነት አስተማማኝና እጅግ በጣም ጤናማ ሆኖ እንዲቀጥል የጌታ ጽኑ ፍላጎት ነው፤ ጌታ ጥንቃቄ ማድረግ የፈለገው አገልጋዩን መሾም ላይ ነው ምክንያቱም ለቤተሰቡ የተቃና እድገትና ኑሮ ወሳኝ ሚና የሚጫወተው አገልጋዩ ነውና ነው፡፡ አገልጋዩ ታማኝና መልካም ከሆነ ቤተሰቡም በሥነ ምግባር፣ በዕውቀት፣ በጥሩ ሰብእና፣ በመልካም ኑሮ የመኖር ዕድል ይኖራቸዋል፤ አገልጋዩ ግድ የለሽና ምግባሩ ያልቀና ከሆነ ግን ቤተሰቡም በተመሳሳይ ታማኝነት የሌላቸው፣ ምግባራቸው ያልቀና፣ ለጌታቸው ሸክም የሆኑ፣ በገቡበትና በሄዱበት ሁሉ መለያየትና መናቈርን የሚወዱ፣ መልካም ሰብእና የጎደላቸው፣ ጌታቸውን ጭምር የሚያስነቅፉ፣ ወላጆቻቸውን የሚያስረግሙ ይሆናሉ፤ ጌታ ለቤተሰቡ የሚሆን መልካም ታማኝ አገልጋይ የመፈለጉና የመሾሙ ነገር በጣም ሲጠነቀቅበት የሚታየው በቤተሰቡ እንዲህ ያለው ችግር እንዳይደርስ ነው፡፡ ይህ አማናዊ የሆነ የወልደ እግዚአብሔር ክርስቶስ ትምህርት መልካምና ታማኝ የሆኑ ካህናትንና ምእመናነ ክርስቶስን በመመገብ ረገድ ያላቸው ኀላፊነት ምን ያህል ታላቅና ጥንቃቄ የሚያስፈልገው እንደሆነ የሚያሳይ ነው፤ እንደ ጌታቸን አስተምህሮ የምእመናን ሕይወት መቃናት አለመቃናት በካህናት እጅ የወደቀ ነው፤ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ጥሩ ያልሆነ ሕይወትና ሥርዐት አልበኝነት እየሰፋ ሄደ ማለት፣ ካህናት ምእመናንን በትምህርተ ወንጌል በአግባቡ መመገብ አለመቻላቸውን የሚያመለክት ነው፤ በአንጻሩ ደግሞ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተስተካከለና እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የሚኖር ሕይወት ከተስፋፋ፣ አንድነት፣ ታዛዥነት፣ ትሕትና፣ ፍጹም ፍቅርና ስምምነት መልካም ሥነ ምግባርና በሥርዐተ አበው መመራት ካለ ካህናት ምእመናኑን በሚገባ እየመገቡ መሆናቸውን የሚያስረግጥ ነው፡፡

ከዚህ አኳያ በቤተ ክርስቲያናችን ውሰጥ በአሁኑ ጊዜ እየተስተዋለ ያለው ከሁለቱ የትኛው ነው የሚለውን መገምገሙ ብልህነት እንጂ ሌላ ሊሆን አይችልም፤ ሥራን ገምግሞ ለንሥሓ መዘጋጀትና ለተሻለ ሥራ እንደገና መነሣት የእግዚአብሔር ፈቃድና የጻድቃን ምርጥ የሕይወት ጒዞ ነው፤ ስለዚህ እኛም የተሻለ የምእመናን ምግብና ልናሰፍን የምንጥር ከሆነ ከወቅቱ ተጨባጭ ሁኔታ በመነሣት ያለውን እውነታ ገምግመን ማወቅ በቅድሚያ ያስፈልጋል፤ ከዚያም ቀጥለን ክፍተቶቻችንን በመዝጋት፣ ዐቅዶና አልሞ በአዲስ መንፈስ በመሥራት ውጤትን ማስመዝገብ የግድ ይላል፡፡

ልዩ ልዩ የቊጥር ዘገባዎችና መረጃዎች እንደሚያሳዩት በአሁኑ ጊዜ በመካከለኛውና በደቡቡ የሀገራችን ክፍል የሚገኙ ምእመናን በቂ የካህናት ምግብና ባለማግኘታቸው በተኵላዎች በከፍተኛ ደረጃ እየተነጠቁ መሆናቸውን ነው፤ እንደዚህ ያለው ክሥተት ገዝፎ በሚታይበት በአሁኑ ጊዜ የካህናት አገልግሎት በታማኝነትና በመልካም ሁኔታ እየተከናወነ ነው ብለን የምናስብ ከሆነ ሌላውን ሳይሆን ራስን ማታለል ነው የሚሆነው፤ በሌላ በኩል መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “መንጋው አንድ እረኛው አንድ” ብሎ የመሠረታት አበው ሠለስቱ ምእትም “በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን” ብለው ያጸኗትን የአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት ለመከፋፈልና ለማዳከም በውስጥም በውጭም የሚሯሯጡ ቢጽ ሐሳውያን እየተበራከቱ መምጣታቸው በግልጽ እየታየ ነው፤ የእነዚህ ሁሉ ድምር ውጤት ዞሮ ዞሮ የካህናት ምግብና እጥረት ከመሆን አያልፍም፡፡

እውነቱን እንናገር ከተባለ እነዚህ ሁሉ ቤተ ክርስቲያናችን ወልዳ ስመ ክርስትናም ሰጥታ ያሳደገቻቸው በካህናት እጅ የነበሩ ምእመናን ልጆቿ ናቸው፤ ይህ የማንክደው ሐቅ ነው፤ ነገር ግን የእኛ የካህናት እጅ አጥብቆ መያዝና መመገብ ባለመቻሉ ሌላው ከእጃችን ፈልቅቆ ወሰዳቸው፤ በእጃችን አሉ የምንላቸውም ቢሆኑ የቤተ ክርስቲያንን አንድነትና ሥርዐት በቅጡ በአእምሮአቸው ውስጥ ማሥረጽ ባለመቻሉ በጥቂት አፈ ጮሌዎች፣ አታላዮችና አስመሳዮች ግራ ተጋብተው የሚይዙትና የሚጨብጡት ጠፍቶቸአው የሚባዝኑ ብዙ ሆነው ይታያሉ፤ ይህ ለምን ሆነ ብሎ መጠየቅ የወቅቱ አንገብጋቢ ጥያቄ ነው፤ ይህ ጥያቄ በአፋጣኝ መልስ ማግኝት አለበት፤ መልሱ የመልካምና የታማኝ አገልጋይ ካህን ህልውና ማረጋገጥ ነው፤ መቼም አገልጋይ ማለት ካህን ማለት እንደሆነ፣ ካህን ማለት ደግሞ ከፓትርያርኩ ጀምሮ እስከ ዲያቆኑ ድረስ የሚዘልቅ የወል ስም እንደሆነ አንስተውም፤ ይህም ከሆነ ያጋጠመንን ክፍተት ለመዝጋት ከሁሉ በላይ ለአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንና ለምእመናንዋ ጥብቅና ብቻ የቆመ ካህን ያሰፈልገናል ማለት ነው ፤ በተለያዩ ስሑታን ቤተ ክርስቲያን ስትከፋፈልና አዛዥዋ ሲበዛ ዝም ብሎ የሚመለከት፤ ከዚያም አልፎ የሚደግፍ ካህን በምንም መመዘኛ ታማኝና መልካም አገልጋይ ሊሆን አይችልም፤ መጋቢ ሆኖ ምእመናንን ማስተዳደርም አይችልም፡፡

ሁላችንም ውሉደ ክህነት ጌታችን በቤተሰቡ ላይ የሾመን ነን በመሆኑም ከተሰጡን መንጎች አንዱ ስንኳ እንዳይጠፋ ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን ማእከል አድርገን በተሳሳተ መንገድ እየተጓዙ ቤተ ክርስቲያንን ለመከፋፍል የሚከጅሉ ልጆቻችንን አንድ ላይ ሆነን ተዉ ንሥሓ ግቡ፣ ታዘዙ፣ የቤተ ክርስቲያንን አንድነትና ሥርዐት ጠብቃችሁ በአበው እግር ዋሉ እንበላቸው፤ ይህ ሲሆን መልካምና ታማኝ እረኛ መሆናችንን እናረጋግጣለን፤ አንዲት ኀያልና ጠንካራ ቤተ ክርስቲያንም ትኖረናለች፤ ይህ ሲሆን የጋራ ጠላት የሆነውን የውጭ ባለጋራ ለመመከት ለምንም ለምን የማይበገር ዐቅም እንፈጥራለን፤ እኛ አንድ ስንሆን እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ይሆናል፤ ኀይላችንም የበረታ ይሆናል፡፡

በመጨሻም፡ የሠላሳ ስድስተኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዙሪያ በሰፊው በመወያየት ለአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ህልውና እና ሉዓላዊ ሥርዐት መከበር በአንድነት እንዲቆም አባታዊና መንፈሳዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡እግዚአብሔር የቤተ ክርስቲያናችንን አንድነት ይጠብቅ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን በማለት መልእክታቸውን ያጠናቀቁ ቅዱስነታቸው የ36ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በዚህ ዙሪያ የተሟላ ግንዛቤ ወስዶ ለአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ህልውና እና ሉዓላዊ ሥርዐት መከበር በአንድነት እንዲቆም አባታዊና መንፈሳዊ መልእክታቸውን አጠቃልለዋል፡፡