መጋቢት10 ቀን 2009 ዓ.ም የደብረ ዘይት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤
በሀገር ውስጥና በዓለም ዙሪያ ሁሉ ያላችሁ ሕዝበ ክርስቲያን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፤
ሁሉንም በቃሉ ኀይል የፈጠረና ያጸና እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለበዓለ ደብረ ዘይት በሰላም አደረሳችሁ፡፡
“ድልዋኒክሙ ንበሩ
ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፤”
(ማቴ 24፥44)
ይህ ኀይለ ቃል ተዘጋጅቶ መኖርን አስመልክቶ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረው ዐቢይ ትምህርት ነው፡፡ ሕያዋን ፍጥረታት በአጠቃላይ በተለይም በእግዚአብሔር መልክና አምሳል የተፈጠረው የሰው ልጅ በተስፋና በስኬት የታጀበ ፍጡር ነው፡፡ የሰው ልጅ እግዚአብሔር በውስጡ በፈጠረለት ባሕርያዊ ዕውቀትና ዝንባሌ በእጁ የሌለን ነገር በእጄ ውስጥ አስገባለሁ የሚል ተስፋ አንግቦ በብርቱ ጥረት ምኞቱን እውን በማድረግ የላቀ ስኬትን ሲያስመዘግብ ይኖራል፡፡ የሰው ልጅ በታሪኩ ብዙ አስደናቂ ስኬቶችን ሊያስመዘግብ የቻለው ይሆናል ከሚል ተስፋ ተነሥቶ እንደ ሆነ ለማንም ግልጽ ነው፤ እግዚአብሔርም ተስፋን ወደ ተጨባጭ እውነት የሚለውጥ የተስፋ አምላክ በመሆኑ “ ተስፋ ቅቡጻን ማለትም የችግረኞች ተስፋ ይባላል”፡፡
እንግዲህ የሰው ውጤታማነት በተስፋ ተጀምሮ በስኬት የሚጠናቀቅ ከመሆኑ አንጻር ሰው ያለተስፋ ሊኖር አይችልም ማለት ይቻላል ምክንያቱም ተስፋ ከሌለ መነቃቃት አይኖርም፣ መነሣሣት ከሌለም ጥረት አይከተልም፤ ያለ ጥረት ደግሞ ስኬት ሊመጣ አይችልምና ነው ፡፡ ይህ ከሕገ ተፈጥሮ ወይም ከሕገ እግዚአብሔር የመነጨ ባሕርያዊና አስገዳጅ ኩነት በመሆኑ ትናንትም ዛሬም ነገም ከሰው አይጠፋም፤ ሰውም ከዚህ ተለይቶ መኖር አይችልም፤ ከዚህ አንጻር ሰውን እንደሞተር እያሽከረከረ ወደ ስኬት ዓለም እያደረሰው የሚገኝ ትልቁ ኀይል ተስፋ እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡ የሰው ልጅ በእጁ የሌለ ነገርን ነገ እጅ አደርጋለሁ ብሎ በተስፋና በወኔ ወደ ሥራ ሲሰማራ እንዲሁ በዘፈቀደ ሳይሆን ካሰበው ቦታ ሊያደርስ የሚችል የተሟላ ዝግጅት አድርጎ ነው፡፡ በቂና የተሟላ ዝግጅት ከሌለ በተሳሳተ መንገድ መጓዝን፤ ያላስፈላጊ ወጭና ኪሣራ ማስከተልን ለስኬት አለመብቃትንና ሽንፈትን ሊያስከትል ይችላል፤ በመሆኑም ለማንኛውም ሥራ ወይም ተስፋ በቂ ዝግጅት አድርጎ በመጓዝ ወደተፈለገው ቦታ መድረስ የግድ ይሆናል፡፡ የዝግጅት አስፈላጊነት በሥጋዊ ዓለም ብቻ ሳይሆን በመንፈሳዊውም ዓለም ይበልጥ አስፈላጊ መሆኑን “ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ” የሚለው የጌታችን ትምህርት ያስገነዝበናል፡፡
በእግዚአብሔር መልክና አምሳል የተፈጠረው የሰው ልጅ አሁንም ከተስፋ ሁሉ የበለጠ ተስፋ በፊቱ አለ፤ ይህ ተስፋ በሰው ሕይወት ፍጻሜ ላይ ያነጣጠረ፣ የተስፋ ሁሉ ማጠቃለያና መደምደሚያ በመሆኑ ተወዳዳሪ የማይገኝለት ዐቢይና አምላካዊ ተስፋ ነው፡፡ የሰው ልጅ ይህንን ተስፋ ሕይወት እንዳያጣ ተብሎ የክርስቶስ ደም ተከፍሎበታል በሃይማኖት ዓለም የተደረገው፣ እየተደረገ ያለውና ለወደፊትም የሚደረገው ሁሉ ይህንን ተስፋ ሕይወት ላለማጣት ተብሎ የሚደረግ የሞት ሽረት ፍልሚያ ነው፡፡ ይህ ተስፋ “ተስፋ መንግሥተ ሰማያት ተብሎ የሚታወቅ ተስፋ ነው” በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ መኖርን የሚጋብዝ ነው፡፡ ቀደምት አበው፣ ቅዱሳን ነቢያት፣ ቅዱሳን ሐዋርያት፣ በዚህ ተስፋ ምክንያት ሕይወታቸውን ገብረዋል ሰማዕታት ደማቸውን አፍስሰዋል፣ ጻድቃን ጣዕመ ዓለምን ንቀው በየጫካውና በየዋሻው መራራ ሕይወትን አሳልፈዋል፣ ምእመናንና ምእመናትም ይህንን ተስፋ ላለማጣት ፈጠሪያቸውን ደጅ ጸንተዋል፣ በሃይማኖትም ተከትለውታል፡፡ ከሁሉ በላይ ደግሞ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ ቀርባለችና ንስሓ ግቡ፤ ተዘጋጅታችሁም ኑሩ” ብሎ በልዩ ልዩ ሕብረ አምሳልና ሕብረ ምሥጢር ከማስተማሩም ሌላ ሰዎችን ለእግዚአብሔር መንግሥት ለማብቃት ሲል ደሙን በማፍሰስ ሕይወቱን ለሞት አሳልፎ ሰጥቶአል፡፡ በደሙም ሰዎችን ለእግዚአብሔር መንግሥት አብቅቶአል የእግዚአብሔር መንግሥትም ለሰዎች ክፍት እንድትሆን አድሮጎአል፡፡
ይሁንና ምንም እንኳ በክርስቶስ ደም መሰነካክሉ ሁሉ ተወግዶ ሰውንና የእግዚአብሔር መንግሥትን የማገናኘት ዕድሉ እውን ቢሆንም አሁንም ዝግጅት የግድ አስፈላጊ እንደሆነ በማስረገጥ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ ብሎ አስተምሮናል፡፡ ስለሆነም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመድረስ የተሟላ ዝግጅት ማድረግ በእግዚአብሔር መልክና አምሳል ለተፈጠረ የሰው ልጅ ሁሉ የግድ ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ዘይት ላይ ሆኖ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት መምጣት በሚያስተምርበት ጊዜ ተስፋ መንግሥተ ሰማያት እውን የሚሆንበት የዓለም መጨረሻ፣ የመምጣቱ ምልክትና መምጫው መቼ እንደሆነ እንዲነግራቸው ሐዋርያት ጥያቄ አቅርበውለታል፤ ጌታችንም ሐዋርያትን ሲያስረዳቸው እንዲህ ብሎአቸዋል፡፡ “ተጠንቀቁ ብዙ ሐሰተኞች መምህራን ይነሣሉ፤ ብዙውንም ያስታሉ፤ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ለጦርነት ይነሣል፤ ፍቅር ይጠፋል፣ ዐመፅ ይስፋፋል፤ ረኃብና ቸነፈር ይበዛል ፣ የምድር መነዋወጥ ይሆናል፣ መጨካከን ይበዛል፣ ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፤ በምድር ላይ ሆኖ የማያውቅ መከራ ይከሠታል፤ ከመከራው በኋላ ፀሓይ ይጨልማል፤ ጨረቃም ብርሃንዋን አትሰጥም፤ ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፤ የሰማያት ኀይሎችም ይነዋወጣሉ፤ ያን ጊዜ መብረቅ ከምሥራቅ ሲወጣ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ የሰው ልጅ ምጽአት ምልክት በደመና ሰማይ ይታያል በአራቱ መአዘነ ዓለም ከዳር እስከዳር ያሉትን ይሰበስቡ ዘንድ መላእክቱ ድምፀ መለከትን ይነፋሉ” ከዚያ በኋላ የሰው ልጅ ክርስቶስ በጌትነቱ ዙፋን ይቀመጣል፤ ጻድቃንን በቀኙ፣ ኃጥኣንንም በግራው ያቆማል፤ ጻድቃንን ካመሰገነ፣ ኃጥአንንም ከወቀሠ በኋላ፣ ጻድቃንን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ያስገባል፡፡ ኃጥአንንም ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት፣ ሥቃይ ወደ ጸናበት ያሰናብታል፤ የዓለም ፍጻሜው፣ የሰው ልጅም የመጨረሻ ዕድሉ ይኸው ነው ብሎ ነግሮአቸዋል” ይህ ትምህርተ መለኮት የተላለፈው በደብረ ዘይት ተራራ ላይ በመሆኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሰው ሕይወት ላይ ወሳኝ ትርጒም ያለው የነገረ ምጽአት ትምህርት በስፋትና በጥልቀት የሚሰጥበት ቀን በመለየትና ደብረ ዘይት ብላ በመሰየም ቀኑ በጸሎት በአምልኮትና በትምህርት እንዲከበር አድርጋለች፡፡
የሰው ልጅ የመጨረሻው ዕድል መንታ መንገድ እንዳለው ማለትም አንዱ የሕይወት መንገድ ሌላው የሞት መንገድ በፊት እንደሚጠብቁት ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር አሳውቆአል፤ በቅዱሳት መጻሕፍትም አጽፎ ሁሌ እየነገረን ይገኛል፡፡ የሰው ልጅ ከሁለቱ መንገድ አንዱን መርጦ መጓዝ የራሱ ውሳኔ ቢሆንም የእግዚአብሔር ምርጫ ግን የሕይወት መንገድ እርሱም የእግዚአብሔር መንግሥትን መምረጥ እንደሚሻል ብቻ ሳይሆን ሰውን ዘለዓለማዊ ሕይወት ለሚገኝበት ለመንግሥተ እግዚአብሔር ለማብቃት ሲል አንድ ልጁን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመሥዋዕትነት አሳልፎ ሰጥቶአል፡፡ በዚህ ሁኔታ እግዚአብሔር ተስፋውን ነግሮ፣ሰውን ሁሉ ወደ መንግሥቱ ለማስገባት ዝግጅቱን አጠናቅቆ ዕድሉንም ሰጥቶ ይጠብቃል፡፡ ትልቁ ጥያቄ እኛ ሰዎች ይህንን የእግዚአብሔር ጥሪ በአግባብ ዐውቀናል ወይ? ዐውቀንስ የዕድሉ ተጠቃሚ ለመሆን ከልብ ተንቀሳቅሰናል ውይ? የሚፈለገውን ያህል ዝግጅትስ እያደረግን ነው ወይ? የሚለው ነው፡፡
እነዚህ ጥያቄዎች ገና በዚህ ዓለም ሳለን ልንመልሳቸው የሚገቡ ናቸው ሰው መጀመሪያ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ባዶ ሆኖ ዕራቊቱን እንደመጣ፣ ነገም ወደ ሌላኛው መንፈሳዊ ዓለም ሲሄድ ባዶ እጁ ሆኖ ከመሄድ በቀር በዚህ ዓለም ሳለ ከሰበሰበው ሀብት አንዳች ስንኳ የሚወስደው እንደሌለ የታወቀ ነው፤ የመኖር ታሪካችንም በዚህ ዓለም ብቻ የተወሰነ ሳይሆን ሕይወታችን ፍጻሜ በሌለው ህልውና በመንፈሳዊ ዓለም እንደሚቀጥል እግዚአብሔር ያለማቋረጥ እየነገረን ነው፡፡ እንግዲህ ይህ በውድም ሆነ በግድ የማይቀርልን ግዳጅ ነው፤ሕይወታዊ ዕድሉ ለተወሰነ ጊዜ የተሰጠ ሳይሆን ለዘለዓለሙ የሚዘልቅና ማብቂያ የሌለው ነው፡፡ እኛ ሰዎች እግዚአብሔርን የምናምንበትና የምናመልክበት ዋና ምክንያት ይህንን ተስፋ ከሩቅ በመመልከት ነው፡፡ ተስፋው ተነግሮናል፤ እኛም እናውቀዋለን፡፡ ነገር ግን ተዘጋጅታችሁ ኑሩ ተብለናልና ዝግጅታችን ምን ይመስላል? የሚለው ጥያቄ ከአእምሮአችን ሳናስወጣ ሁሌም ዝግጁ ልንሆን ይገባል፡፡ ትልቁና ዋናው ዝግጅትም ለእግዚአብሔር መታዘዝ ነው፡፡ ሁላችንም ለመታዘዝ ዝግጁ ከሆን፣ ትእዛዙን ዐውቀን ለመፈጸም ከባድ ዐቀበት አይኖርብንም፤ ምክንያቱም የእግዚአብሔር ትእዛዝ ለአእምሮ የሚመች፣ ለመንፈሳዊ ሕይወት ብቻ ሳይሆን ለሥጋዊ ሕይወትም የሚጠቅም፣ ኅሊናን በደስታና በነፃነት የሚሞላ ነውና፡፡
በአጭሩ የእግዚአብሔር ትእዛዝ በሁለት ዐበይት ነገሮች ተጠቃሎ እንደሚፈጸም ጌታችን አስተምሮናል፤ ይኸውም እግዚአብሔርንና ሰውን ከልብ በመውደድ ትእዛዙን ሁሉ ማጠቃለል ይቻላል ብሎናል፤ እኛ እግዚአብሔርን ከልብ የምንወድ ከሆነ ለእርሱ ለመታዘዝ አንቸገርም፤ ሰውንም እንደራሳችን አድርገን የምንወድ ከሆነ በሰው ላይ በደልን አንፈጽምም፤ ይህንንም መደበኛ፣ ቀዋሚና ዕለታዊ ሥራችን አድርገን የምንኖር ከሆነ መዘጋጀት ማለት ይኸው ነው፤ ስለዚህ እግዚአብሔር ፍቅር ነውና እኛም በፍቅር እንከተለው፤ እርስ በርሳችንም በፍቅር ገመድ እንተሳሰር፤ የመንግሥተ ሰማያተ መግቢያ ካርድ ይኸው ነው፤ በፍቅር የምናሳልፈው ሕይወት እርሱ ራሱ መንግሥተ ሰማያት እንደሆነ እናስተውል፤ በአንጻሩ ደግሞ በጥላቻ በንትርክ፣ በፍጅትና ለእግዚአብሔር ባለመታዘዝ የምናሳልፈው ሕይወት ገሃነመ እሳት ማለት እርሱ እንደሆነ እናስተውል፤ የሚያጠግብ ቂጣ ከምጣዱ ሳለ ይታወቃል የሚለው የአበው ብሂል ከዚህ ጋር ይስማማል፣ እኛ ሰዎች በዚህ ዓለም በየቀኑ በምንፈጽመው ድርጊት ወዴት እያመራን እንደሆነ ማወቅ ይቻላል፤ ስለዚህ ሁሌም ምን ላይ እንዳለን ወዴትስ እያመራን እንደሆነ ቆም ብለን በማሰብ መንገዳችንን ማስተካከል፤ ዝግጅታችንንም ማጧጧፍ ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሔር መዋዕለ ጾሙን በሰላም አስፈጽሞ ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም ያድርሰን፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡