• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

ጥቅምት 13 ቀን 2012 ዓ.ም. በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች በልዩ ልዩ ምክንያቶች ሃይማኖትን፣ ብሔርና ቋንቋን መሠረት ያደረገ የሰው መግደልና የአብያተ ክርስቲያናት አስምልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በፍጹም የሚያወግዘው መሆኑን የተሰጠ መግለጫ በቅዱስነታቸው ተላልፏል፡፡

October 24, 2019

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

«ተገሐሥ እምእኩይ ወግበር ሠናየ — ከክፉ ነገር ራቅ፤ ሰላምን ፈልጋት።»
(መዝ. 33፥12)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሥራቿና አምላኳ የሰላም አባትና አለቃ የሆነው ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደመሆኑ በጸሎቷና በአገልግሎቷ ስለ ሀገር ሰላም፣ ስለ ሕዝቦቿና ስለ መላው ዓለም ሰላም ዘወትር ወደአምላኳ ስታማፅንና ስትማልድ የኖረች ያለችና ወደፊትም የምትኖር የሀገር ባለውለታና የሁሉም እናት መሆኗ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ በሀገራችን በተለያዩ ክልሎች ልዩ ልዩ ምክንያቶች የአማራና የቅማንት፣ የሱማሌና የአፋር፣ የአማራና የትግራይ የኦሮሞና የአማራ የጉምዝና የአማራ የሲዳሞና የወላይታ በሚል ብሔርና ሃይማኖትን እንዲሁም ቋንቋን መሠረት ያደረገ በኢትዮጵያ ሀገራችን እንኳንስ ሊደረጉ ይቅርና ሊታሰቡ የማይገባቸው መጠነ ሰፊ ግጭቶች በመከሠታቸው የሰው ሕይወት ጠፍቷል፣ በርካታ ንብረት ወድሟል፣ ዜጎች ከቀያቸው አለአግባብ እየተፈናቀሉ ለከፋ እንግልትና ዕርዛት ተዳርገዋል፡፡ እስከ አሁን ድረስ በግጭቶች እየደረሱ ካሉት የሰው ሕይወት ጥፋትና የንብረት ውድመት ልንማር ባለመቻላችን በያዝነው ሳምንት ችግሩ ቀጥሎ በአዲስ አበባ፣ በኦሮምያ ክልልና በሌሎችም ክልሎች እየተከሠተ ያለው ግጭት እጅግ አሳሳቢ ከመሆኑም በላይ ጊዜ የማይሰጥና ሁሉም ኢትዮጵያውያን በአንድነትና በኅብረት ችግሩን ካልቀረፍነው መጠነ ሰፊ ጉዳትን የሚያስከትል ከመሆኑም በላይ በሀገራችን ያሉ ጅምር የልማትና የእድገት ጒዞዎችን በመግታት ሀገሪቱን ለከፍተኛ ጥፋትና ድህነት የሚዳርግ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ በመሆኑ ዓመታዊ ስብሰባውን በማካሄድ ላይ የሚገኘው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስለ ሀገር ሰላም ቅድሚያ በመስጠትና ከሌሎች የመወያያ አጀንዳዎች በማስቀደም በጉዳዩ ላይ በስፋት ከተወያየ በኋላ ተከታዩን አስቸኳይ የአቋም መግለጫና የሰላም ጥሪ አስተላልፏል፡፡

1. ማንኛውም የተለየ ሐሳብና አመለካከት ያለው ወገን ቢኖር ሐሳቡን በሠለጠነና በሰከነ መንገድ ሀገራዊ አንድነትን ማእከል ባደረገ ሁኔታ በክብ ጠረጴዛ በመወያየት ችግሮቹ እንዲፈቱና የአሠራር ግድፈቶች ካሉም እንዲታረሙ እንዲደረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፣
2. የሀገር ተረካቢ የሆናችሁ መላው የኢትዮጵያ ወጣቶች ሀገራችሁ ኢትዮጵያ ከዛሬ ይልቅ ነገ በእናንተ ተተኪነትና በምታከናውኑት የማይተካ የላቀ አስተዋፅኦ ወደ ላቀ የእድገት ደረጃ ደርሳ እናንተም ሆናችሁ መላው ወገናችሁ ተጠቃሚ የሚሆንባት የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባትና እውን ለማድረግ የሀገሪቱ ሙሉ ተስፋ በእናንተ በወጣት ልጆቻችን ትከሻ ላይ የተጣለ መሆኑ ይታወቃል፤ በመሆኑም በወቅታዊና ሚዛናዊ ባልሆነ አንዳንድ ከሕግ ማዕቀፍ የወጡ አካሄዶችን በሰከነ አእምሮ እና በትኵረት በመመልከት ሀገራችን ኢትዮጵያን ከጥፋትና ካልተገባ ግጭት ትታደጓት ዘንድ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከአደራ ጋር በአጽንዖት ለእናንተ ለልጆቿ ጥሪዋን ታስተላልፋለች፡፡
3. በሀገራችን ኢትዮጵያ የተፈጠረውን የመድበለ ፓርቲ ሥርዐት ተከትሎ ለሀገራችሁ የሚሆን ልዩ ልዩ አማራጭ ሐሳቦችን በማመንጨት ሕጋዊ ዕውቅና አግኝታችሁ በመንቀሳቀስ ላይ የምትገኙ ሁላችሁም የፖለቲካ ፓርቲዎች በሙሉ ፖሊሲ ቀርጻችሁና ያመናችሁበትን ርእዮተ ዓለም አቅዳችሁ የምትንቀሳቀሱት ሀገራችሁ ኢትዮጵያ ወደተሻለ የእድገት ደረጃ እንድትደርስ የበኩላችሁን ድርሻ ለመወጣት መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ ከዚህ አንጻር በየጊዜው ዘር፣ ብሔርና ሃይማኖትን መሠረት አድርገው እየተከሠቱ ያሉ ግጭቶችን ከጅምሩ በአንድነት ማስቆም ካልተቻለ ነገ የምትረከቧትና የምታስተዳድሯት ሀገር ልትኖር ስለማትችል በቅድሚያ የፖለቲካ አመለካከት ልዩነት ሳይገድባችሁ ለሀገር ሰላምና አንድነት በኅብረት ዘብ በመቆም የበኩላችሁን ኀላፊነት ትወጡ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
4. ለመንግሥታችሁና ለሕዝባችሁ ሙያዊ ትንታኔን መሠረት ያደረገ አማራጭ ሐሳቦችን በግብአትነት በማበርከት የሀገራችንን እድገትና የዲሞክራሲያዊ ሥርዐት ወደ ተሻለ ደረጃ እንዲደርስ የበኩላችሁን አስተዋፅኦ ለማበርከት በማሰብ ልዩ ልዩ ጽሑፎችንና ዘገባዎችን በመገናኛ ብዙኃንና በማኅበራዊ ሚዲያ የምታቀርቡና የምታስተላልፉ የፖለቲካ ተንታኞችና አክቲቪስቶች ከስሜት፣ ከብሔር፣ ከቋንቋና ከሃይማኖት ልዩነት በጸዳ ሁኔታ እናት ሀገራችሁን ማእከል በማድረግ ለተሻለ ሰላምና አንድነት የበኩላችሁን ድርሻ ከማበርከት ባለፈ ሕዝብን ከሕዝብ የሚያጋጩና አንዳንድ ያልተገቡ ትርክቶችን አላግባብ ከማሰራጨት በመቈጠብ ሀገራዊ ግዴታችሁን እንድትወጡ እናሳስባለን፤
5. የመንግሥትም ሆነ የግል የመገናኛ ብዙኃን ድርጅቶች ከተቋቋማችሁበት መሠረታዊ ተልእኮና ዓላማ አንጻር በተቻለ አቅም ዘርን፣ ቀለምን፣ ብሔርንና ሃይማኖትን መሠረት ካደረጉ የትንኮሳ ቃላቶች በመራቅና ሚዛናዊ የሆኑ መረጃዎችን ለሕዝባችን በማድረስ ለሀገራችን ኢትዮጵያ ሰላምና አንድነት የበኩላችሁን ኀላፊነት እንድትወጡ አደራ እንላለን፤
6. የማኅበራዊ ሚዲያ መሠረታዊ ዐላማው ዜጎች በእውነታ ላይ የተመሠረቱ ወቅታዊ መረጃዎችን በተሻለ ፍጥነት እንዲያገኙ ታስቦ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ግን በሀገራችን ኢትዮጵያ እየታየ ያለው እውነታ ከዚህ በተለየ መልኩ ሕዝብን ከሕዝብ፣ ብሔርን ከብሔር፣ ጎሳን ከጎሳ ሃይማኖትን ከሃይማኖት የሚያጋጩና ከእውነት የራቁ ግጭት ቀስቃሽ ሐሰተኛ መረጃዎችን በማሠራጨት ሀገራችን ኢትዮጵያ የቆየ የአብሮነትና የአንድነት ባህሏን በሚያጎድፍ መልኩ ላልተገባ ዐላማ እየዋለ መሆኑ አጠያያቂ አይደለም፤ ከዚህ አንጻር ዛሬ በሌሎች ላይ የሚደርሰው የሰው ሕይወት መጥፋትና የንብረት ውድመት ነገ በየአንዳንዱ ቤት ሲያንኳኳ ሁሉም የጉዳቱ ሰለባ እንደሚሆን በመረዳት በተቻለ ዐቅም የማኅበራዊ ሚዲያውን ለሀገራዊ ሰላምና አንድነት በመጠቀም ሁሉም የማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚው ሕዝባችን የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ እንጠይቃለን፤
7. ሀገር በዕውቀት እና በተሻለ ሐሳብ የምታድግና የምትመራ መሆኑ አጠያያቂ አይደለም፡፡ ከዚህ አንጻር የሀገራችን ምሁራን ያላቸው ድርሻ በቀላሉ ሊገመት የማይችል ሲሆን በአሁኑ ወቅት ግን አንዳንድ ምሁራን የሚያስተላልፏቸው የኢትዮጵያን ታሪክ መሠረት ያላደረጉ ትርክቶች ለሀገራችን የግጭትና ያለመግባባት መንሥኤ ሲሆኑ ይስተዋላሉ፡፡ በመሆኑም የሀገራችን ምሁራን በተቻለ አቅም ከልዩነትና ከግጭት ይልቅ ለሀገራዊ አንድነት እና ሰላም ኀላፊነታችሁን እንድትወጡ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፤
8. በየደረጃው ያላችሁ የመንግሥት የሥራ ኀላፊዎች መላው ሕዝባችን ትመሩትና ታስተዳድሩት ዘንድ የሰጣችሁን ይሁንታና ሀገራዊ ኀላፊነት ከግምት ውስጥ ባስገባና በታላቅ ሀገራዊ ኀላፊነት ስሜት በተቻለ መጠን ግጭቶችና አለመግባባቶች ከመከሠታቸው በፊት ልዩ ልዩ የውይይት መድረኮችን ለመላው ሕዝባችሁ በማዘጋጀት እና በውይይት መድረኩ የሚገኙትን ግብአት የዕቅዳችሁ አካል አድርጋችሁ በመተግበር ኀላፊነታችሁን ከቀድሞው በተሻለና በላቀ ሁኔታ በመፈጸም ለሀገራችን ሰላምና አንድነት እድገትና ብልጽግና የድርሻችሁን እንድትወጡ እንጠይቃለን፤
9. በየደረጃው ያላችሁ የፀጥታና የፍትሕ አካላት ሁሉ በተለያዩ ቦታዎች ግጭቶችና አለመግባባቶች ከመከሠታቸው በፊት ቅድመ መከላከልን መሠረት ያደረገ የፀጥታ ሥራን በመተግበር እየተከሠቱ ያሉ ግጭቶችንና የሰው ሕይወት መጥፋትን እንዲሁም የንብረት ውድመትን በመከላከል የተጣለባችሁን ኀላፊነት እንድትወጡ እናሳስባለን፤
10. መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ! እስከ አሁን ድረስ የኢትዮጵያን ሰላም በማይወዱ አካላት የሚከሠቱ ልዩ ልዩ አፍራሽና ግጭት ቀስቃሽ አጀንዳዎችን ወደጎን በመተውና በአርቆ አሳቢነትና በሀገር ባለቤትነት መጠነ ሰፊ ትዕግሥት የተሞላበት ሀገራዊ አንድነትና ኅብረት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ላበረከታችሁት የማይተካ ሚናና ታሪክ የማይረሳው ውለታ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም እያመሰገነ እንደአሁን ቀደሙ ሁሉ ለሀገራችን ሰላምና አንድነት ዘር፣ ብሔርና ሃይማኖት ሳይለያያችሁ እጅ ለእጅ በመያያዝ የበኩላችሁን የማይተካ ድርሻ እንድትወጡ የአደራ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፤
11. በሀገራችን ኢትዮጵያ የምትገኙ የሁሉም የሃይማኖት ተቋማት ሀገራችን ኢትዮጵያ በሃይማኖት ብዝኀነትና ተቻችሎና ተከባብሮ በመኖር አስደናቂ ባህሏ ሌሎች ሀገራት የሚቀኑባትና በአርኣያነትም የሚጠቅሷት ሀገር መሆኗ ይታወቃል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ይህን አኲሪና አርኣያ የሆነ ታሪኳን በሚያደበዝዝ ሁኔታ ሃይማኖትና ብሔርን መሠረት ያደረጉ ግጭቶች እየተበራከቱ በመሆናቸው ዜጎች ያለምንም መሸማቀቅና ተጽዕኖ እምነታቸውን ለማምለክና ለማስመለክ የማይችሉበት የሥጋት አደጋ እየተጋረጠ ከመሆኑ አንጻር ሁሉም ቤተ እምነቶች ለሀገራዊ አንድነትና ለእምነት ነፃነት በአንድነትና በኅብረት ለመላው ሕዝባችን የሰላም ጥሪ በማስተላለፍና ዘወትር በየአስተምህሮአችን ለሕዝባችን የሰላምን ጥሪ ተደራሽ በማድረግ ሀገራዊ ኀላፊነታችንን እንወጣ ዘንድ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡
12. በመጨረሻም ያለ ሀገር ሰላምና አንድነት እንዲሁም ፍቅርና እድገት መኖር ስለማይቻል መላው ሕዝባችን እንደየእምነቱና ሃይማኖቱ ሥርዐት ከዛሬ ጥቅምት 13 ቀን 2012ዓ.ም. ጀምሮ ለ3 ቀን ያህል በጾም፣ በጸሎትና በኀዘን ስለ ሀገር ሰላም በአንድነት ጥሪውን ለፈጣሪውና ለአምላኩ ያቀርብ ዘንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ጸሎትና ምሕላ እንዲደረግ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም ጥሪውን አስተላልፏል፡፡ መንፈሳዊ አዋጁንም አውጇል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/007-3.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc32019-10-24 09:42:572025-01-27 09:45:34ጥቅምት 13 ቀን 2012 ዓ.ም. በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች በልዩ ልዩ ምክንያቶች ሃይማኖትን፣ ብሔርና ቋንቋን መሠረት ያደረገ የሰው መግደልና የአብያተ ክርስቲያናት አስምልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በፍጹም የሚያወግዘው መሆኑን የተሰጠ መግለጫ በቅዱስነታቸው ተላልፏል፡፡
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ጥቅምት 12 ቀን 2012 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ጥቅምት 12 ቀን 2012 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ጥቅምት 12 ቀን 2012 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ... Link to: ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 24 ቀን 2012 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ Link to: ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 24 ቀን 2012 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ ከጥቅምት 11 ቀን እስከ 24 ቀን 2012 ዓ.ም የተካሄደው...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top