መስከረም 1 ቀን 2012 ዓ.ም. የዘመን መለወጫ በዓልን ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣

ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣

የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣

በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጰያውያንና ኢትዮጵያውያት፡፤

የዘመናትና የዓመታት ባለቤት የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን የሁለት ሺሕ ዐሥራ አንድ ዓመተ ምሕረት ዘመነ ሉቃስን በሰላም አስፈጽሞ ወደ ሁለት ሺሕ ዐሥራ ሁለት ዓመተ ምሕረት ዘመነ ዮሐንስ እንኳን በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ!!

“አመ ርእሰ ሳብዕ ወርኅ ግበሩ መጥቅዐ፤ በሰባተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን ዕረፍት፣ በመለከት ድምፅ መታሰቢያ የተቀደሰ ጉባኤ ይሁንላችሁ” (ዘሌ. 2324)፡፡

የኢትዮጵያ የዘመን አቈጣጠር ሥር መሠረቱ ቀመረ አዳም፣ ቀመረ ኖኅ እንደሆነ ቅዱስ መጽሐፍ ያስረዳል፡፡ ይህም አቈጣጠር እስከ ዘመነ ሙሴ በመካከለኛው ምሥራቅ ሕዝቦች ሁሉ ጥቅም ላይ የዋለ ነበረ፡፡ በሊቀ ነቢያት ሙሴ ዘመን ግን በእግዚአብሔር ኀይል የሕዝበ እስራኤል ከግብጽ ባርነት መውጣትና ነፃነት ማግኘት ጋር በተያያዘ ወርኀ ሚያዝያ የወር መጀመሪያ እንዲሆን እግዚአብሔር ትእዛዝ መስጠቱ በቅዱስ መጽሐፍ ተመዝግቦአል፡፡ ይሁንና የወር መጀመሪያ እንጂ የዓመት መጀመሪያ ከመስከረም እንዳልተፋለሰ ‹‹በሰባተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን በድምፀ መለከት የተቀደሰ ጉባኤ ይሁንላችሁ›› ተብሎ ከእግዚአብሔር ለሙሴ በተሰጠው ትእዛዝ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም ሕዝበ እስራኤል ዛሬም ድረስ በጨረቃ አቈጣጠር ቢሆንም የዘመን መለወጫ ዐውደ ዓመታቸውን የሚያከብሩት መስከረም ላይ ነው፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ሀገራችን ቀመረ ዘመን አጠቃቀም የተመለከትን እንደሆነ የኖኅ አቈጣጠርን በትክክል የተከተለ ሆኖ ይገኛል፡፡ ይኸውም የቀኑም የወሩም የዓመቱም መጀመሪያ አንድ ላይ መስከረም አንድ ቀን መሆኑ ነው፤ የኖኅ ቀመር የሚቈጠረው በፀሓይ አቈጣጠር ሆኖ ከጳጉሜን በቀር ሁሉም ወሮች በሠላሳ ቀናት የተመደቡ መሆናቸውን መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹በሁለተኛው ወር፤ በዐሥራ ሰባተኛው ቀን የጥፋት ውኃ መዝነብ መጀመሩን ገልጾ፣ ከመቶ ኃምሣ ቀን በኋላ ደግሞ በመጀመሪያው ወር በመጀመሪያው ቀን ውኃው ከምድር ላይ ደረቀ›› ይላል፤ ይህም በጥቅል ሲገለጽ አምስት ወር እንደሆነ ያሳያል፤ በዚህ ስሌት መሠረት ወሮቹ በሠላሳ ቀናት የተመደቡ መሆናቸውን በግልጽ ያመለክታል ፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያ ሀገራችን እንዲህ ያለውን በእግዚአብሔር ትእዛዝና በአበው ትውፊት ከጥንት ከዘመነ አዳም ወኖኅ ጀምሮ የነበረውን የዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ ዓመት እስከ ዛሬ ድረስ ጠብቃ ማቈየቷ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ለመላው ዓለም የሚያኮራ ነው፡፡

ዛሬ የምንጠቀምበት የዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ ዓመት ጥንት የብዙ ሀገሮች ዘመን መለወጫ የነበረ ቢሆንም ሌሎቹ በተለያየ ሰው ሠራሽ ምክንያት ሌላ ቀመር በመፍጠር የነበረውን ትተው በሌላ እየተጠቀሙ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡ ክብር ለእግዚአብሔር ይግባውና እኛ ኢትዮጵያውያን ብቻ በተሟላ ሁኔታ የጥንታውያን አበው ማለትም የአዳምና የኖኅ ሐሳበ ቀመር ይዘን መዝለቃችን ለእግዚአብሔርና ለቀደምት አበው ያለን ታማኝነት ምን ያህል ጠንካራ እንደሆነ ያሳያል፡፡ ይህ በራስ ሃይማኖት ትውፊትና ባህል ኮርቶ በልበ ሙሉነት የመኖር ጸጋችን የሀገርን ነፃነትና የሕዝብን አንድነት ለመጠበቅም ጒልህ ሚና እንደተጫወተ በደምብ መገንዘብ ያስፈልጋል ፡፡ የኢትዮጵያ ዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ ዓመት ከሌሎች የዘመን መለወጫ በዓል ልዩ የሚያደርገው፤ በእግዚአብሔር የታዘዘ በአርእስተ አበው ዘመን የነበረ መሆኑ ብቻ አይደለም፤ ከነገረ ክርስቶስና ከሥነ ፍጥረትም በእጅጉ የተቈራኘ ምሥጢር አለው፡፡ ከነገረ ክርስቶስ አንጻር የክርሰቶስ መንገድ ጠራጊ የሆነው ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ የብሉይ ኪዳን ማብቂያና የሐዲስ ኪዳን መግቢያ መሆንና መስከረም አንድ ቀንም የአሮጌው ዓመት ማብቂያና የሐዲስ ዘመን መነሻ መሆን ተመሳሳይነት ስላላቸው የሁለቱን ንጽጽር በማገናኘት የዮሐንስ መታሰቢያ በዓል በርእሰ ዐውደ ዓመት እንዲከበር መደረጉ ነው፤ በተጨማሪም ይህ ንጽጽር ክርሰቶስ አሮጌውን ዓለም የሚያሳልፍ የሐዲስ ሰማይና የሐዲስ ምድር ጌታና ንጉሠ ነገሥት እንደሆነ የሚገልጽ ምሥጢር አለው፡፡ ከሥነ ፍጥረት አንጻር ሲታይ ደግሞ የክረምቱ የዝናም ውሽንፍር፣ የደመናው፣ የመብረቁ፣ የነጐድጓዱ፣ የጭፍናውና የጎርፉ ጋጋታ ሁሉ አልፎ ምድር በልምላሜና በአበባ ባሸበረቀችበት፣ ውኃው በየፏፏቴው በየሸለቈውና በየወንዙ ጥርት፣ ኮለል ብሎ በሚታይበት አዲስ እሸት በደረሰበት እንስሳቱም አእዋፉም በዝማሬና በደስታ በሚቦርቁበት ሰውም ከመልክዐ ምድር ውበት የተነሣ ልቡ በተስፋና በኃሤት በሚሞላበት የሚከበር የዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ ዓመት መሆኑ ልዩ ያደርገዋል ፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን፤

ይህ የዘመን መለወጫ በዓል በሁለመና ገጽታው ፍጹም መታደስን የሚያበስር ርእሰ ዐውደ ዓመት እንደሆነ በእግዚአብሔር ቃልም በሥነ ፍጥረትም ጭምር የተረጋገጠ መሆኑን በኅሊናችንም፣ በዐይናችንም የምናየው ሐቅ ነው፡፡ በመሆኑም ይህ ሁሉ የሆነው ለማን ተብሎ እንደሆነ መገንዘብና መጠቀም ከፍጡራን ይጠበቃል፡፡ እግዚአብሔር የፍጥረታት መታደስን የሚወድ አምላክ እንደሆነ በሥነ – ፍጥረት ብቻ የገለጸ አምላክ አይደለም፤ በቅዱስ ቃሉም ‹‹በልባችሁ መታደስ ተለወጡ›› በማለት ሁሉም መታደስ እንዳለበት አስተምሮናል እንጂ፡፡ አዲስ የዘመን መለወጫ ብለን የምንናገርለት ይህ ዕለት አዲስ ሊሆን የሚችለው በዋናነት የኛ ልቡና ሲታደስ ነው፡፡ እግዚአብሔር ቃል ኪዳኑን ጠብቆ እነሆ ምድራችንን በልምላሜ፣ በአበባ፣ በፍሬ፣ በምርት በሁሉም ነገር አስውቦ አዲስ አድርጎአታል፡፡ እኛ ሰዎችም በተመሳሳይ በአስተሳሰብ በሥራ በአኗኗር ሁሉ ከልብ የሆነ መታደስ ሊኖረን ይገባል፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ ሕዳሴን እናበሥራለን›› የሚለው መልካም ምኞታችን ከቃላት አልፎ ተግባራዊ እንዲሆን ከሁሉም በፊት ይቅርታና እውነተኛ መግባባት በሁሉም ወገኖች መከናወን አለበት፤ አንድ መቀበል ያለብን እውነት በሐሳብ መቀራረብና በሰጥቶ መቀበል መርሕ እየተቻቻሉ መሄድ እንደ አዋጭ ባህል አድርገን መጓዝ ካልቻልን መቼም ቢሆን ለችግራችን መፍትሔ አናገኝም፤ ምክንያቱም በታሪክ የሁሉም ሐሳብ አንድ ዐይነት ሆኖ የተገኘበት ጊዜ የለምና ነው፡፡ ያለን ብቸኛ አማራጭ የተወሰነውን በመተው፣ የተወሰነውን በመቀበል፣ የተወሰነውን ደግሞ በመስጠት ወደ አንድነት መምጣትና ሀገርንና ወገንን ማሳደግ ነው፡፡ ይህ ዐይነቱ መቻቻል በሀገራችን ውስጥ ባለመዳበሩ ሕዝባችን ለመከራ ተጋልጦአል ፡፡

ይህ ዐይነቱ ክሥተት ከአሮጌው ዘመን ጋር አብሮ ማክተም አለበት፤ መለያየት፣ መገዳደል፣ ወገንን ማፈናቀል፣ አብያተ ሃይማኖትን መዳፈር፣ የእርጅና ምልክቶች ናቸውና ከአሮጌው ዓመት ጋር አብረው ማለፋቸውን በአዲሱ ዓመት እናብሥር፤ በምትኩም ለአንድነት፤ ለመፈቃቀር ለመተዛዘን፣ ለመቻቻል፣ ለመከባበር፣ ለመተማመንና ለአብሮነት መበልጸግ ከዛሬዋ ቀን ጀምረን በአዲስ ልብ በአዲስ መንፈስ መነሣት ይኖርብናል፡ ይህን ስናደርግ ዘመኑም፣ ሥነ ፍጥረቱም፣ እኛም በትክክል በሕዳሴ መንገድ መጓዝ ጀምረናል ማለት እንችላለን፡፡ የእግዚአብሔር በረከት በሕዝቦች አንድነት ውስጥ አለ፡፡ የነፃነትና የኀያልነት መንፈስ በሕዝቦች አንድነት ውስጥ አለ፡፡ ችግሮችን ሁሉ በብቃት ተቋቁሞ በአሸናፊነት መወጣት በሕዝቦች አንድነት ውስጥ አለ፡፡ አንድነት ከሌለ ጒልበት የለም፤ ችግሮችን መቋቋምም አይቻልም፤ በባዕዳን መደፈርም ሊከተል ይችላል፤ እግዚአብሐሔርም ፊቱን ያዞራል፡፡ ስለዚህ ይህ ታላቅና ባለታሪክ ሕዝብ ለዘመናት ተንከባክቦ ያቆየው ሃይማኖቱን፣ ታሪኩን፣ ባህሉንና አንድነቱን ይፈልጋልና አሁንም፣ ነገም፣ ከነገ በኋላም የሕዝቡን አንድነት እንጠብቅ፤ ለግል ፍላጎት ስንል በሕዝቡ አንድነትና እኩልነት መሰናክል አናብዛ፤ በምናደርገውም ሁሉ በእግዚአብሔርና በታሪክ ፊት በደል እንዳንፈጽም እንጠንቀቅ ፡፡

በመጨረሻም፡ አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የፍቅር፣ የአንድነት፣ የስምምነትና የይቅርታ ዘመን ማድረግ የምንችለው ከእግዚአብሔር በታች እኛው ነን፤ ስለሆነም በይቅርታና በሰጥቶ መቀበል መርሕ ሁሉንም ልዩነቶች ወደ መቀራረብ ብሎም ወደ ፍጹም መተማመን በማምጣት ሀገሪቱንና ሕዝቦችዋን ወደ አንድነትና ወደ ላቀ ሕዳሴ እንድናሸጋግር አደራ ጭምር መንፈሳዊና አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ፤ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዘኢብሔር አሜን፡፡