• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

መስከረም 16 ቀን 2012 ዓ.ም በመስቀል ደመራ በዓል ላይ የተላለፈ መልእክት

September 27, 2019

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ከመስቀሉና ከቃሉ የተነሣ አባቶቻችንን በክብርና በዘለዓለማዊ ሕይወት ከፍ ከፍ ያደረገ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ!!!

“በመስቀሉ ወበቃሉ አዕበዮሙ ለአበዊነ፤
በመስቀሉና በቃሉ አባቶቻችንን ከፍ ከፍ አደረጋቸው።”
(ቅዱስ ያሬድ)

የክርስትና ሃይማኖት እምነትና አስተምህሮ መሠረታዊ ይዘት ድኅነተ ዓለም በክርስቶስ መስቀል ተፈጽሞአል፤ ወደፊትም ይፈጸማል የሚል እንደሆነ ሁሉም የሚያውቀው ነው፡፡ የጌታችን ግብረ አድኅኖ ፍጹም እንደመሆኑ መጠን ወደኋላም ወደፊትም ያሉትን ሁሉ ያካተተ እንደሆነ በቅዱስ መጽሐፍ ተረጋገጦአል፡፡ በፍዳ ኀጢአት ተግዘው ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመናት በግዞት ይማቅቁ የነበሩ ነፍሳተ አበው በአጠቃላይ በመስቀል ላይ በተፈጸመው የቤዛነት መሥዋዕት ምክንያት ነፃነትን አግኝተው ወደቀድሞው የክብር ቦታቸው እንደገቡ “ወሖረ ኀበ እለ ሙቅሕታ ትነብር ነፍሶሙ ወሰበከ ሎሙ ግዕዛነ፤ ተግዘው ወደነበሩት ነፍሳት ሄዶ ነፃነትን ሰበከላቸው ወይም አወጀላቸው” በማለት ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የምሥራቹን ያስረዳናል፡፡ ከዚህ እውነታ በመነሣት ኢትዮጵያዊው ነባቤ መለኮት ቅዱስ ያሬድ በዜማ መጽሐፉ የአባቶቻችን ክብር የተረጋገጠው በቅዱስ ወንጌል በተነገረውና በቅዱስ መስቀል በተፈጸመው የቤዛነት መሥዋዕት እንደሆነ በጣዕመ ዜማው ይነግረናል፡፡

ቅዱስ መጽሐፍም እንደሚያስረዳን በመስቀሉና በቃሉ የከበሩ ከክርስቶስ በፊት የነበሩ ቀደምት አበው ብቻ አይደሉም፤ ከዘመነ ክርስቶስ ጀምሮ እስካሁን ያሉት ሕዝበ ክርስቲያንም በመስቀሉና በቃሉ ከብረዋል እንጂ ይለናል፡፡ ከዚህ አንጻር በዚህ ዘመን የምንገኘውም ሆን እስከ ዕለተ ምጽአት የሚነሣው ትውልድ ሁሉ የክብር ክብርና የዘለዓለም ሕይወት የሚያገኘው በመስቀሉና በቃሉ መሆኑን ያሳየናል፡፡

ጌታችን ወደዚህ ዓለም በመጣ ጊዜ ያከናወናቸው ተግባራት ሁሉ በሁለት ዐበይት ነገሮች የሚጠቃለሉ ናቸው፤ እነሱም፡- አንደኛው እግዚአብሔርንና መንግሥቱን ፈቃዱንም ጭምር ለሰው ልጆች መግለፁ ነው፤ ይኸውም በቅዱስ ወንጌል ተጽፎ የምናገኘው ቅዱስ ቃሉ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በሰው ልጆች ፈንታ እሱ ራሱ በመስቀል ላይ መሥዋዕት በመሆን የሰው ልጆችን ማዳኑ ነው፡፡ ጌታችን በእነዚህ ሁለት ዐበይት ነገሮች ትዝምደ ሰብእን ወይም የሰው ዘርን አድኖአል፤ ስለሆነም መዳናችን ቃሉ በተመዘገበበት በቅዱስ ወንጌልና የቤዛነት አዳኝነቱ በተከናወነበት በቅዱስ መስቀል ላይ የተፈጸመ በመሆኑ ቅዱስ መስቀልንና ቅዱስ ወንጌልን በከፍተኛ ደረጃ ማክበራችን ተገቢ ብቻ ሳይሆን ከተገቢም በላይ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ክቡራንና ክቡራት የበዓለ መስቀሉ ተሳታፊዎች፡- የፍቅረ መስቀሉ መንፈሳዊ ተመሥጦ ያደረባት የታላቁ ቈስጠንጢኖስ እናት ቅድስት ዕሌኒ መስቀሉን ለመፈለግ ከዛሬዋ የቱርክ ሀገር እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ የተጓዘችው መስቀሉ የክብሯ ምንጭና የዘለዓለማዊ ሕይወቷ መገኛ መሆኑን ከቃሉ በመረዳትዋ፣ በተግባርም በማየቷ እንደሆነ መገንዘቡ አይከብድም፡፡ ቅድስት ዕሌኒ በዛሬው ዕለት የልቧ ምኞት በእግዚአብሔር ፈቃድ ተሳክቶ ዕጣንና ዕንጨት አንድ ላይ ደምራ በማቃጠል በጢሱ አማካኝነት መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ ያወቀችበት ዕለት በመሆኑ በዚህ ምክንያት ይህንን ቀን ቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ በታላቅ ድምቀት ታከብረዋለች፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ የሰው ልጆች ድኅነት በምልአት የተፈጸመበት ቅዱስ መስቀል ከምንም በላይ ሊከበርና ሊደመጥ ይገባል፡፡ የመስቀል ነገረ ድኅነት በአንድ ጊዜ ተከናውኖ የተጠናቀቀ አይደለም፤ ዛሬም ነገረ መስቀሉ በየሰከንዱ ብዙዎችን ያድናል፡፡ ነገረ መስቀሉ የተለያዩትን አሰባስቦ አንድ የሚያደርግ ነው፤ ነገረ መስቀሉ የተጣሉትን አስታርቆ በአንድ ማእድ የሚያስቀምጥ ነው፡፡ ነገረ መስቀሉ ቂምንና በቀልን ከሥሩ መንግሎ የሚጥል፣ በምትኩም ሰላምንና ፍቅርን የሚያድል አምላካዊ ምሥጢር ነው፡፡ ነገረ መስቀሉ ኀጢአትን በደልንና መርገምን ደምስሶ ነፃነትን፣ ጽድቅን፣ ሕይወትንና ክብርን የሚያጐናጽፍ ነው፤ ግን ይህ ሁሉ እውን ሊሆን የሚችለው ነገረ መስቀሉ በትክክል ሲደመጥና ሲከተሉት እንደሆነ መዘንጋት የለብንም፡፡ ቀደምት ኢትዮጵያውያን አበው ነገረ መስቀሉን በትክክል አዳምጠውና ተከትለው በነፃነት፣ በአንድነት፣ በወንድማማችነት፣ በይቅር ባይነትና በሰላም ኖረዋል፡፡

አባቶቻችን በዓለም ብቸኛ የሆነ የሀገር ነፃነትና አንድነት ጠብቀው ለእኛ ሊያስረክቡ የቻሉት የነገረ መስቀሉን አስተምህሮ ብቻ በመከተላቸው እንደሆነ ማስተዋል ይገባናል፤ ይህንን እውነት የማንገነዘብና የማናስተውል ኢትዮጵያውያን ካለን ራሳችንን አላወቅንም ማለት ነው፡፡ ደግሞስ አብያተ ክርስቲያናትን እየተዳፈሩና እያቃጠሉ፣ እየዘረፉና እየገደሉ፣ ሰላምንና አንድነትን፣ ፍቅርንና ልማትን ማምጣት ይቻላል ወይ? እንደዚህ ዐይነቱ አጒል አስተሳሰብና ድፍረት በእግዚአብሔርና በሕዝበ ክርስቲያኑ ላይ እየተፈጸመ ያለ ክፉና አጥፊ ድርጊት መሆኑ ታውቆ በአስቸኳይ መቆም አለበት፤ እስከ መጨረሻውም መገታት አለበት፤ በዚህ ዙሪያ በሚሆነው ነገር ሁሉ በጭራሽ መግባባት አይኖርም፡፡ ኢትዮጵያውያን አበው መስቀልን ይሳለሙታል እንጂ አያቃጥሉትም፤ ኢትዮጵያውያን አበው መስቀልን የአክብሮት ስግደት ይሰግዱለታል እንጂ አይረግጡትም፣ ኢትዮጵያውያን አበው መስቀልን ያከብሩታል እንጅ አያዋርዱትም፤ ምክንያቱም በመስቀሉና በቃሉ ክብራቸውንና ድኅነታቸውን እንዳገኙ አሳምረው ያውቃሉና ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ “ትመኛላችሁ፤ ለእናንተም አይሆንም፣ ትገድላላችሁ፣ በብርቱም ትፈልጋላችሁ፣ ልታገኙም አትችሉም፣ ትጣላላችሁ፣ ትዋጉማላችሁ፣ ነገር ግን አትለምኑምና ለእናንተ አይሆንም” እንዳለው ምኞታችን ሁሉ ሊሳካ ያልቻለው ከመስቀሉ እየራቅን ስለሄድን ነው፤ ልመናችንም ወደ እግዚአብሔር ለማቅረብና በፈቃዱ ለመኖር እንደ አሳፋሪ ነገር ስለቈጠርን ነው፡፡

ይህም በመሆኑ እግዚአብሔር በነቢዩ በኢሳይያስ በኩል “አንትሙኒ ተሐውሩ ግድመ ግድመ፤ ወአነኒ አሐውር ግድመ ግድመ፤ እናንተም ዳር ዳሩን ትሄዳላችሁ፤ እኔም ዳር ዳሩን እሄዳለሁ” ያለውን በኢትዮጵያ ላይ እየተፈጸመ ይገኛል፡፡ ኢትዮጵያውያን መሪዎችና ልሂቃን ከኃምሣ ዓመታት ላላነሱዘመናት ከእግዚአብሔር ርቀዋል፡፡ ከመስቀሉ ሥርም ጠፍተዋል፡፡ ይህ ዐይነቱ አመለካከት በኢትዮጵያ ውስጥ አያስኬድም፣ እንደማያስኬድም በግልጽ እያታየ ነው፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ ተዉ ወደ እግዚአብሔር እንመለስ፤ እንደ ቀደምት አባቶቻችን ከቤተ ክርስቲያን ዐጸድና ከመስቀል ሥር እንገኝ፡፡ የጎደለንን ፍቅርና ሰላም፣ አንድነትና እኩልነት፣ ፍትሕና ወንድማማችነት በመስቀሉ ውስጥ ተትረፍርፎ እናገኘዋለን፡፡ ይቅርታና መተባበር፣ መከባበርና መተማመን በመስቀሉ ውስጥ ሞልቶአል፡፡ የኢትዮጵያ ፈውስ ከመስቀሉ ሥር እንደሆነ ሁላችንም እንወቅ፤ እንደ አባቶቹ በመስቀሉና በቃሉ ለመክበር የሚፈልግ ትውልድ ወደ መስቀሉና ወደቃሉ ሊመለስ ግድ ይለዋል፤ ያለዚያ ግን ምኞቱ ሁሉ ቅዠት ከሚሆን በቀር ሊሳካ አይችልም፡፡

በመጨረሻም፤ የመስቀል ትሩፋት ግኝት የሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከሁሉም በላይ እኩልነትን ከአንድነት ጋር፣ ነፃነትን ከወንድማማችነት ጋር አጥብቆ እንደሚወድ፣ ይህንንም ከመስቀሉ ቃል ያገኘው ዕሴት እንደሆነ ዐውቃችሁ፣ የሀገሪቱ ምሁራን፣ ፓለቲከኞች፣ ልኂቃንና አክቲቭስቶች ከጥላቻና ከመወራረፍ፣ ከስድብና ከመጠላለፍ፣ ከመፎካከርና ከመዘለዓለፍ ተቈጥባችሁ በቅንነት፣ በአርቆ አስተዋይነት፣ በይቅርታና በፍቅር ይህንን ታላቅ ሕዝብ በእኩልነት እንድናገለግል፣ አንድነታችንንና ሰላማችንንም የጋራ ሀብት አድርገን እንድንጠብቅ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡ መልካም የመስቀል በዓል ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ይቀድስ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc32019-09-27 13:55:522025-01-28 13:57:24መስከረም 16 ቀን 2012 ዓ.ም በመስቀል ደመራ በዓል ላይ የተላለፈ መልእክት
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: መስከረም 1 ቀን 2012 ዓ.ም. የዘመን መለወጫ በዓልን ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: መስከረም 1 ቀን 2012 ዓ.ም. የዘመን መለወጫ በዓልን ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ መስከረም 1 ቀን 2012 ዓ.ም. የዘመን መለወጫ በዓልን... Link to:  38ኛው የሰበካ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ከጥቅምት 5-8 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ Link to:  38ኛው የሰበካ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ከጥቅምት 5-8 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡  38ኛው የሰበካ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ከጥቅምት...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top