• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

መስከረም 1 ቀን 2009 ዓ.ም የዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ ዓመት መልእክት

September 11, 2016

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
በሕመም ምክንያት በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

ዘመናትና ዓመታት የማይቈጠሩለት እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከ2008 ዓ.ም.ዘመነ ዮሐንስ ወደ 2009 ዓ.ም. ዘመነ ማቴዎስ በሰላምና በጤና አደረሳችሁ ፡፡

‹‹ወእስምያ ለዓመተ እግዚአብሔር ኅሪተ፤ የተመረጠችውንና የተወደደችውን የእግዚአብሔር ዓመት እሰብክ ዘንድ ልኮኛል›› (ኢሳ.61፡2፤ ሉቃ.4፡19)፡፡

ሁላችንም እንደምናውቀው እንደ ሌላው ሁሉ ዓመትም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፤ ዓመት የጊዜ መለኪያ ነው፤ ጊዜም የሥራ መሣሪያ ነው፡፡ እግዚአብሔር ዓመታትን ለፍጡራኑ ሲሰጥ ለሥራ፣ ለኑሮ፣ ለምግብና ለጤና ወዘተ በሚያመች አኳኋን በተለያዩ ሐውዘ አየራት ከፋፍሎና አመቻችቶ መስጠቱ ዓለም በእርሱ መግቦት የሚመራ መሆኑን ይበልጥ ያጎላዋል፡፡ ከዚህም ጋር ጊዜያትን ለመለካት የሚያስችሉ መገብተ ብርሃን በጠፈረ ሰማይ ፈጥሮ ሰው በእነርሱ እየታገዘ ጊዜን በመለካት ለሥራውና ለኑሮው እንዲጠቀምባቸው አድርጎአል፡፡ ይህንንም በቅዱስ መጽሐፍ ‹‹እግዚአብሔርም ቀንና ሌሊትን ይለዩ ዘንድ ለምልክቶች፣ ለዘመናት፣ ለዕለታትና ለዓመታት መለያ ይሆኑ ዘንድ ብርሃናት በሰማይ ጠፈር ይሁኑ አለ›› በማለት በግልጽ አስቀምጦታል (ዘፍ. 1፥14)፡፡ ስለሆነም ሰው ቀንን በብርሃነ ፀሓይ፣ ወርን በብርሃነ ወርኅ፣ ወቅትን በብርሃነ ከዋክብት፣ ወዘተ. እየለካ ወቅቱን በመዋጀት ለእርሻ ተግባሩ ማለትም ለአዝርእቱ ለአትክልቱ፣ ለፍራፍሬው ምቹ ወቅት የትኛው እንደሆነ በመለየትና በማወቅ በግብርና ተግባር በሚገባ እንዲጠቀምባቸው አስችሎታል፡፡ በሌላም በኩል እግዚአብሔር ለአበው የሰጠው ተስፋ – ድኅነት ማለትም ዘመነ ሥጋዌ ወይም ዘመነ ክርስቶስ በዘመን ቀመር ስሌት አሠራር መቼ እንደሚሆን ቅዱሳን ነቢያት በኊልቈ ዓመታት ሲቈጥሩ፣ ሲከታተሉና ሲጠብቁ እንደነበሩ በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ በብዙ ቦታ ተጽፎአል።

በተለይም ነቢዩ ዳንኤል በደልና ኀጢአት የሚደመሰስበት ዘመነ ክርስቶስ ሊደርስ እርሱ ከነበረበት ዘመን አንሥቶ ሰባ ሱባዔ እንደቀረው በግልጽ ጽፎአል፤ በትንቢቱ መሠረትም ተፈጽሞአል፤ (ዳን. 9፥24-27)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ይህ ሱባዔ ሲፈጸም የሆነውን ነገር ሲገልጽ “የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ልጁን ላከ፤ ከሴትም ተወለደ ብሎአል” /ገላ. 4፡4/ ፡፡ ከዚህም አኳያ እግዚአብሔር ለማዳን ሥራ የመረጠው ወይም ለይቶ ያስቀመጠው ዓመት እንዳለ ከዚህ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ይህም ዓመት ምርጥ የሆነ የእግዚአብሔር ዓመት ተብሎ ተገልጾአል፡፡ ቅዱሳን ነቢያት እግዚአብሔር በገለጸላቸው ምሥጢር መሠረት የተወደደው፣ የተመረጠውና ምሕረት እንደዝናም የሚዘንብበት የእግዚአብሔር ዓመት እርሱም ዘመነ ክርስቶስ እንደሚመጣ ብቻ ሳይሆን መቼ እንደሚመጣ ጭምር ዓመታቱን በትክክል እየቀመሩና እየቈጠሩ ሲናገሩና ሲያስተምሩ መኖራቸው የዘመናት ቊጥር በሃይማኖት ዘንድም የላቀ ተፈላጊነት እንዳለው ያመለክታል፡፡ እግዚአብሔር የተናገረውን የማያስቀር ታማኝ አምላክ ነውና የተቈጠሩት ዓመታት በደረሱ ጊዜ፣ የዛሬ ሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመት ልጁን ወደዚህ ዓለም በመላክ ዓለሙን ከፍዳ ኀጢአት ታደገው፡፡ በመሆኑም በተጠቀሰው ዘመን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ መሥዋዕት ሆኖ የዓለምን ዕዳ-ኀጢአት በመሸከም የሰው ልጅን በምሕረቱ ስለተቀበለው ከልደተ ክርስቶስ ወዲህ ያለው ዘመን ምሕረተ እግዚአብሔርን ለማሰብና ለማወጅ ሲባል ‹‹ዓመተ ምሕረት›› ወይም እንደ ነቢዩ እንደ ኢሳይያስ አገላለጽ “የተመረጠ የእግዚአብሔር ዓመት” ይባላል፡፡ እኛም ኢትዮጵያውያን በክርስቶስ አምላክነትና አዳኝነት ከመጀመሪያው ምእተ-ዓመት መጀመሪያ አንሥቶ ምሕረተ እግዚአብሔርን ገንዘብ ካደረጉ ሀገራት መካከል የመጀመሪያዎቹ ነንና ምሕረቱን ተቀብለን በዘመን አቈጣጠራችን ላይ ‹‹ዓመተ ምሕረት›› እያልን ምሕረተ እግዚአብሔርን ስናስታውስና ስናውጅ እንኖራለን፡፡

ዘመን የእግዚአብሔር ጸጋ እንደሆነ ቀደም ብሎ ከላይ ተገልጾአል፤ የእግዚአብሔር ጸጋ እንደመሆኑም መጠን በጥንቃቄና በአግባቡ ልንጠቀምበት ይገባል፤ እግዚአብሔር ዘመናትን፣ ዓመታትንና ወራትን የሚሰጠን ለሃይማኖት ማጽኛ፣ ለሥነ ምግባር ማበልጸጊያ፣ ለንስሓ ማጎልበቻ፣ ለእድገት፣ ለብልጽግና፣ ለልማት፣ ለሰላም፣ ለፍቅር፣ ለአንድነትና ለስምምነት በአጠቃላይ የጎደለንን ለመሙላት ያጣነውን ለመተካት፣ የተስተካከለ መንፈሳዊና ሥጋዊ ሕይወት እንዲኖረን ለማስቻል እንደሆነ መገንዘብ አለብን፡፡

በመሆኑም ጊዜ ባለፈው አሮጌ ዘመን የጎደለብንን ሁሉ በአዲሱ ዘመን ለመሙላት እንድንችል በእግዚአብሔር የተሰጠን ልዩ ጸጋ ነውና በሥራ ልንጠቀምበት ይገባል፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ ባለፉት ክፍለ ዘመናት ያመለጧት ብዙ ነገሮች እንዳሉ የሚታወቅ ነው፤ ይሁን እንጂ ከብዙ ውጣ ውረድ በኋላ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ቀድሞ ያመለጧትን ነገሮች ለመሙላት ከፍተኛ እንቅስቃሴ ላይ መገኘቷና በዚህም ያመጣችው ለውጥ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፤ ይህም የእግዚአብሔር ጸጋ ነውና ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ኢታስትት ጸጋሁ ዘላዕሌከ፤ በአንተ ያለውን የጸጋ ስጦታ ቸል አትበል” እንዳለው የተሰጠንን ጸጋ-ልማት በጥቃቅን ነገሮች ልናደናቅፈው አይገባም፡፡

አሁን ባለንበት ዘመን የተገነዘብነው ዐቢይ ቁም ነገር ቢኖር ሰላም የልማት ቊልፍ መሣሪያ መሆኑን ነው፤ በሀገራችን እየፈነጠቀ ያለው የእድገት ጮራ የሰላም ውጤት እንጂ የሌላ አይደለም፡፡ ከዓለም ተሞክሮ ልምድ ብንወስድም አሁን በከፍተኛ የእድገት ጣራ ላይ የሚገኙ ሀገራት የልማታቸው ምሥጢር የሰላምና የአንድነት መረጋገጥ እንደሆነ ማስተዋሉ አይከብድም፡፡ ስለሆነም ያለ ሰላም ልማትና እድገት ፈጽሞ የሚታሰብ አይደለምና እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ለራሱ ልማት ሲል ለሰላም ጠበቃ መሆን አለበት፡፡ ባለፈው ዓመት ከዛሬ ሠላሳ አንድ ዓመታት በፊት ካጋጠመን ድርቅ ያልተናነሰ ከባድ ድርቅ ያጋጠመን ቢሆንም የሀገራችን ሕዝቦች ሰላማቸውንና አንድነታቸውን ጠብቀው ባስመዘገቡት እድገት ምክንያት ሀገራችን ችግሩን በራስዋ ዐቅም መቋቋም መቻሏ የሰላምና የአንድነት ጥቅም እንዲሁም እነርሱን ተከትሎ የተገኘው የእድገት ጣዕም ምን ያህል እንደሆነ የተገነዘብንበት ዓመት ሆኖ አልፎአል፡፡ስለሆነም አሁንም በተመረጠውና በተወደደው የእግዚአብሔር ዓመት ውስጥ ሆነን ዛሬ በምንጀምረው አዲስ ዓመት እግዚአብሔር ቸርነቱን አብዝቶልን የዝናሙ ስርጭትና የእህሉ ቡቃያ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢ ተስፋ ሰጪ ሆኖ ስለሚታይ፣ ሕዝቡ በዚህ ተነቃቅቶ ሰላሙንና አንድነቱን በመጠበቅ የበለጠ ልማትና እድገት ለማስመዝገብ ጠንክሮ እንዲሠራ፣ እንደዚሁም ከድህነትና ከሰላም ዕጦት የበለጠ ሌላ ጠላት እንደሌለው ሕዝቡ ተገንዝቦ በአዲሱ ዓመት አለመግባባትን በውይይት፣ ድህነትን በልማት ለማሸነፍ በሁሉም አቅጣጫ እንዲረባረብ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን ዘመኑ የሰላም፣ የአንድነትና የልማት ያድርግልን፡፡ እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ይቀድስ፤ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

መስከረም 2 ቀን 2009 ዓ.ም ርእሰ ዐውደ ዓመትን ምክንያት በማድረግ በመላ ሀገረቱ ጸሎት እንዲደረግ መመሪያ አስተላለፉ።

በቤተ ክርስቲያናችን ትውፊት ተጠብቆ የቆየውን እና በየዓመቱ የሚከናወነውን የእንኳን አደረስዎ መርሐ ግብር የዘንድሮ ዘመን መለወጫ በዓለ ቅዱስ ዮሐንስም መስከረም 2 ቀን 2009 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የየመምሪያ ኀላፊዎች እና አጠቃላይ ሠራተኞች፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ኀላፊዎችና ሠራተኞች፣ የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የሰ/ት/ቤት ወጣቶች መዘምራንና ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶች በተገኙበት በመንፈሳዊ ሥነ ሥርዐት ሲከበር ቅዱስነታቸው በቃለ ምዕዳናቸው በዋናነት የሰላምን አስፈላጊነት በስፋት አትተው ሁሉም የሰላም ሐዋርያ ሆኖ በክርስቶስ መሾሙን አስረድተዋል፡፡ “ሰላም የምናመጣውም ሆነ የምናሳጣው እኛ ነን፤ ሰላም በእጃችን ሳለ እንደ ቀላል እንቈጥረዋለን ስናጣው ግን ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ እንረዳለን፤ የሰላም ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ሰላሙ ሰጥቶና፤ ይህ የክርስቶስ ሰላም በመላ ሀገራችን እንዲሁም በመላ ዓለማችን ጸንቶ እንዲኖር ሁላችንም የሰላም ሐዋርያት፣ የሰላም መምህራን፣ የሰላም መልእክተኞች በመሆን የሚጠበቅብንን መንፈሳዊ ኀላፊነት መወጣት አለብን” በማለት የሰላምን አስፈላጊነት በስፋት አትተው በየደረጃው የሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች የሰላም ሐዋርያት ሆነው ሕዝቡን እንዲያገለግሉ አባታዊ መመሪያ አስተላልፈዋል፡፡ በመቀጠልም ያለፈውን ዓመት የነበረውን የሀገራችን የድርቅ ችግር አስታውሰው እግዚአብሔር የልጆቹ ጸሎት የሚሰማና ለልጆቹ የሚራራ ርኅሩኅ አምላክ ስለሆነ ያንን ድርቅ አሳልፎ ሀገራችን በሐመልማል በረከት ጎብኝቷል በማለት ያለውን ወቅታዊ የሀገራችን የአየር ጸባይ ካስረዱ በኋላ ይህ አሁን የምናየው ልምላሜ ከፍሬ እንዲያደርስልን እና እኛ ከማናውቀው መቅሠፍት ሁሉ ሰውሮ የተባረከ ዘመን እንዲያደርግልን አሁንም ጸሎት ስለ ሰላም፣ ስለ አትክልቱ እና አዝርዕቱ፣ ስለ ሕዝባችን ፍቅር እና አንድነት፣ ስለ ዓለም ሰላም ሁሉ በማሰብ ዐውደ ዓመቱን በጸሎተ ምሕላ እንዲጀመር በማለት ለሁለተኛ ጊዜ የጸሎተ ምሕላ ሱባኤ እንዲያዝ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc32016-09-11 13:10:342025-01-28 13:11:41መስከረም 1 ቀን 2009 ዓ.ም የዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ ዓመት መልእክት
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ነሐሴ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. በዓለ ደብረ ታቦርን በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ነሐሴ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. በዓለ ደብረ ታቦርን በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ነሐሴ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. በዓለ ደብረ ታቦርን በማስመልከት... Link to: መስከረም 16 ቀን የ2009 ዓ.ም. በበዓለ መስቀል ላይ በአደባባይ የተሰጠ መልእክት Link to: መስከረም 16 ቀን የ2009 ዓ.ም. በበዓለ መስቀል ላይ በአደባባይ የተሰጠ መልእክት መስከረም 16 ቀን የ2009 ዓ.ም. በበዓለ መስቀል ላይ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top