• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

መስከረም 16 ቀን የ2009 ዓ.ም. በበዓለ መስቀል ላይ በአደባባይ የተሰጠ መልእክት

September 26, 2016

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

ከአራቱ የከተማችን መዓዝን የመጣችሁ ሕዝበ ክርስቲያን፤ እንደዚሁም በሀገር ውስጥና በውጭ ሆናችሁ የበዓለ መስቀሉን ሥነ በዓል በመከታተል የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

በመስቀሉ ተሰቅሎ ባፈሰሰው ደሙ ሰማያውያንና ምድራውያንን አስታርቆ ፍጹም ሰላምን ያጎናጸፈን ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት በዓለ መስቀል በሰላም አደረሳችሁ።

‹‹ወለጽልእ ቀተሎ በመስቀሉ
ጥልንም በመስቀሉ ገደለው።››
(ኤፌ. 2፥16)

ቅዱስ መጽሐፍ በግልጽ እንደሚነግረን ዓለም እንደተፈጠረ ብዙም ሳይቆይ የጥል ግንብ እንደተገነባ ነው፤ የጠቡ መነሻ የሆነው መሠረታዊ ችግር ለእግዚአብሔር አለመታዘዝ፣ ታማኝ ሆኖ አለመገኘት፣ ሕግን መጣስ፣ ከእግዚአብሔር ቃል ይልቅ የዲያብሎስን ምክር መቀበል ነው፤ (ዘፍ.2፡16-17፤ ዘፍ.3፡1-8)፡፡ ይህ አድራጎት የተፈጸመው በአባታችን አዳምና በእናታችን ሔዋን ሲሆን ድርጊቱ በፈጣሪና በፍጡራን፣ እንደዚሁም በፍጡራንና በፍጡራን መካከል ጽኑ የሆነ ጥል ፈጠረ፤ ከባድ የሆነ መርገምትና መለያየትም አስከተለ (ዘፍ. 3፥10-24)፡፡

ጥል ካለ ዘንድ መለያየቱም እየሰፋና እየከፋ መሄዱ የማይቀር ነውና ከአዳምና ከሔዋን የተገኘ የሰው ዘር በሙሉ እርስ በእርስ መጣላቱንና መለያየቱን በስፋት ቀጠለበት፣ በዚህም ሂደት የሰው ልጅ ሕይወት ጣዕም የለሽና መራራ ሆነች፣ ሁሉም በአምልኮ ባዕድና በድንቊርና ተዋጠ፤ ቀለም፣ እምነት፣ ዘር፣ ቋንቋ፣ መልክዐ ምድር ከባቢያዊ ባህል፣ ሀብት፣ ሥልጣን፣ ዕውቀት የመሳሰሉ ሁሉ ሰውን እርስ በርሱ ለያይተው ለከፋ ጕዳት ዳረጉት፤ እነዚህ ሁሉ ኀጢአት ወልዳ ያሳደገቻቸው የአለመታዘዝ ውጤቶች እንጂ ከጥንተ ፍጥረት የተገኙ አይደሉም፡፡ የሰው ዘር በአጠቃላይ ከአዳም ውድቀት አንሥቶ እስከ ስቅለተ ክርስቶስ ድረስ በዚህ የጨለማ ሕይወት ተውጦ ስለነበረ ቅዱስ መጽሐፍ “በጨለማና በሞት ጥላ የሚኖር ሕዝብ” ብሎ ይገልጸዋል፤ (ኢሳ. 9፡2)፡፡ ያ ዘመን የሰው ዘር በአጠቃላይ በሰማይም ሆነ በምድር፣ በነፍስም ሆነ በሥጋ ከባድ የሆነ የሞት ቅጣትን ያስተናገደበት ዘመን በመሆኑ ዓመተ ፍዳ፣ ዓመተ ኵነኔ ተብሎ ተገልጾአል፤ (ሮሜ 5፥12-19)፡፡ ይሁንና ምሕረት፣ ይቅርታ፣ ገደብ የለሽ ፍቅርና አዘኔታ ገንዘቡ የሆነ እግዚአብሔር አምላክ አንድ ቀን ሰውን ከዚህ የሞት ቅጣት እንደሚታደገው ከመጀመሪያው አንሥቶ ተስፋውን ያሰማ ነበር፤ (ዘፍ. 3፥15፤ ዘፍ. 22፡፥6-18፣ ኢሳ. 53፥4-12፤ ዳን. 9፥24-27)፡፡

ከዘመን በኋላ እግዚአብሔር በሰጠው ተስፋ መሠረት የባሕርይ ልጁ የሆነ ቀዳማዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድን ወደዚህ ዓለም ላከ፤ እሱም መጥቶ ሥጋችንን ተዋሐደ፤ የጥል ምክንያት የሆነውን ኀጢአትን ያጠፋ ዘንድ የኀጢአት መካካሻ ሆኖ በመስቀል ላይ መሥዋዕት ሆነ፤ በቀዳማዊ አዳም አለመታዘዝ የተበደለ እግዚአብሔር በዳግማዊ አዳም (በክርስቶስ) ድንቅ መታዘዝ ተካሰ፤ (ሮሜ 5፥19፤ 2ቆሮ. 5፥19፤ ዕብ. 5፥7-8)፡፡ በመሆኑም በዚህ መሥዋዕት ምክንያት እግዚአብሔር የዓለሙን ወይም የሰውን ኀጢአት ይቅር ብሎ የምሕረት በሩን ከፈተ፤ በሰውና በእግዚአብሔር የተገነባው ጥል ፈራርሶ በጥምቀትና በቅዱስ ቁርባን አማካኝነት ከእግዚአብሔር ጋር የአባትና የልጅ የሆነ ግንኙነትን መመሥረት ተቻለ፤ (ኤፌ2፡13-16፤ ዮሐ.6፡56፤ ሮሜ.6፡3-4)፡፡ በቀለም፣ በዘር፣ በፆታ፣ በሃይማኖት ወዘተ ተፈጥሮ የቆየውን የሰው ከሰው መለያየት ቀርቶ ሁሉም በአንድ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አምኖ እንዲድን የሁሉም መዳኛ የሚሆን ስም ሰጠ፤ ‹‹ከሰማይ በታች ከዚህ ስም በቀር የምንድንበት ሌላ ስም የለምና›› ተብሎ እንደተጻፈው፤ (የሐዋ.ሥራ 4፥9-12)፡፡

ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመታት ያህል ሥር ሰዶ የነበረው የጥል ግድግዳ በመስቀሉ ላይ በተፈጸመው የዕርቀ ሰላም መሥዋዕትነት ስለፈራረሰ ዛሬ ከእግዚአብሔር ጋር ለመገናኘት የሚከለክለን የለም፣ የኀጢአት ግንብ ቢኖርም እንኳ በንስሓ ይናዳል፤ ዛሬ በቀለም፣ በዘር፣ በፆታ፣ በቋንቋ፣ በዕውቀት፣ በሀብት፣ በሥልጣን ወዘተ ከእግዚአብሔር ምሥጢረ ድኅነት የሚከለከል የለም፣ የሚጠየቀው አንድና አንድ ብቻ ነው፤ እርሱም ማመንና ቀጥሎም በሥነ ምግባር ተወስኖ መኖር ነው።

ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመታት ጸንቶ የቆየው የጥል ግድግዳ የፈራረሰው በጌታችን በአምላካችንና በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መሥዋዕትነት ሲሆን፤ መሥዋዕትነቱም የተፈጸመው በመስቀል ላይ ነው፤ ለዚህም ነው ‹‹ጥልን በመስቀሉ ገደለ›› ተብሎ እየተነገረን ያለው፤ ሁላችንም እንደምናውቀው መግደል ማለት ማጥፋት፣ ህልውናን ማሳጣት ማለት እንደሆነ ለሁሉም ግልጽ ነው፤ከዚህ አንጻር ክርስቶስ በመስቀሉ ጥልን ገደለ ሲባል በፈጣሪና በፍጡራን መካከል የነበረውን የጥል ህልውና ጨርሶ አጠፋ ደመሰሰ ማለት እንደሆነ እናስተውላለን፤ ይሁንና በመስቀል የተፈጸመው ምሥጢር ጥልን ማጥፋት ብቻ አይደለም ዕርቅን፣ ሰላምን፣ አንድነትንና ነፃነትን በአጠቃላይ በመስቀል ላይ በተፈጸመው መሥዋዕትነት ተከናውኖአል፤ (ሮሜ 5፥10-11፣ 1ተሰ. 2፥13-15)፡፡ በመሆኑም መስቀልን ማሰብና ማክበር ሁለት ነገሮችን እንድናስታውስ ያስገድደናል፤ ይኸውም፡ (1) በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ያዳነን ክርስቶስንና የክርስቶስ ፍቅርን፣ (2) በመስቀል ላይ የተፈጸመው የድኅነታችን መሥዋዕትን እንድናስብ ያደርገናል፡፡ ስለሆነም መስቀሉን ማሰብ ማለት ክርስቶስንና የክርስቶስን የማዳን ምሥጢር ማሰብ ማለት እንደሆነ አንዘንጋ፤ መስቀል ሰላምን፣ አንድነትን፣ ነፃነትን ዕርቅን የሚሰብክና የሚያስተምር፣ ስለድኅነተ ሰብእ የሚመሰክር፣ የእግዚአብሔር የማዳን ዐርማ፣ የድልና የአሸናፊነት ምልክት ነው፤ ኀጢአትና ሞት ተሸንፈውበታልና (1ቆሮ. 15፥55-57)፡፡ ከዚህ አኳያ የክርስቶስ መስቀል ተራ ነገር ሳይሆን በስተጀርባው ነገረ ክርስቶስን ያዘለ በመሆኑ ክርስቶስንና የማዳን ተግባሩን እንደዚሁም የምንድንበትን መንገድ የሚያስተምረን ቅዱስ የሆነ ትእምርተ አድኅኖ ነው፡፡

በመጀመሪያዎቹ የክርስትና ክፍለ ዘመናት የነበሩ አይሁዳውያንና ክርስቲያኖች የተጋጩበት ዐቢይ ነጥብ በዚህ መሠረታዊ ምክንያት ነው፤ ሁለቱም ክፍሎች ትእምርተ መስቀሉ ክርስቶስን በቀጥታ እየሰበከ እንደሆነ አልሳቱትም፤ በመሆኑም አይሁዳውያኑ ክርስቶስን መስበኩ እንዲያቆም ፈልገው መስቀልን በጒድጓድ ሲቀብሩት፣ ክርስቲያኖቹ ደግሞ መስቀሉ ከተቀበረበት ወጥቶ ክርስቶስን መስበክ አለበት በማለታቸው በመካከላቸው ቅራኔ ተፈጥሮአል፡፡ ይሁንና “የማታ ማታ እውነታ ይረታ” እንዲሉ፤ ምንም ቢሆን እውነት መርታቱ አይቀርምና መስቀሉ ከተቀበረበት ወጣ፤ እውነትም ረታ፤ እኛም ዛሬ በከፍተኛ ድምቀት የምናከብረው በዓል መስቀሉ ከተቀበረበት ጒድጓድ የወጣበትን ለማሰብ ብቻ ሳይሆን መስቀሉ በዓለም ዐቀፍ ደረጃ ከፍተኛ መድረክ አግኝቶ የክርስቶስን አዳኝነት ለዓለም ሕዝብ እንዲሰብክ፣ እንዲያስተምርና እንዲመሰክር ምቹ ሁኔታን ለመፍጠርም ጭምር ነው፡፡

ምስጋና ለኀያሉ አምላካችን ለእግዚአብሔር ይሁንና ይህ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዘመናት ጥረት በዘመናችን እውን ሆኖ እነሆ መስቀለ ክርስቶስ ዓለምን በአጠቃላይ ለመስበክ የሚያስችል ምቹ መድረክ አግኝቶአል፡፡ ይኸውም በዓለ መስቀል በኢትዮጵያ ስም በተባበሩት የዓለም መንግሥታት ድርጅት መመዝገቡ ነው፤ በዚህም ለዚህ ታላቅ ዕድል ያበቃንን እግዚአብሔርን እጅግ አድርገን እናመሰግነዋለን፤ እንግዲህ የኢትዮጵያ ኦርቶደክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመስቀልን በዓል በከፍተኛ ሁኔታ የምታከብርበት ዋና ምክንያት የጥል ግድግዳን የሚያፈርስ፣ መለያየትን የሚንድ፣ በምትኩ ደግሞ ሰላምን፣ አንድነትን፣ ወንድማማችነትን፣ መተሳሰብን፣ መከባበርን፣ መተማመንን፣ መቻቻልን፣ መተጋገዝን ፍጹምና ዘላቂ የሆነ ፍቅርን የሚያሰፍን በመሆኑ ነው፤ በተለይም ደግሞ ሰላምን በዋናነት ማግኘት የሚቻለው ከመስቀል አስተምህሮ በመሆኑ ነው፤ መስቀል ‹‹የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው›› ብሎ ለገዳዮች ምሕረትንና ይቅርታን እየለመነ ፍጹም ፍቅርን ይሰብካል፤ መስቀል በንስሓ ለቀረበ በደለኛ ‹‹ዛሬውኑ ከኔ ጋር በገነት ትኖራለህ›› እያለ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ እንዲኖር ይጋብዛል፤ መስቀል ለሰው ድኅነት ሲባል ራስን አሳልፎ በመስጠት ፍጹም ድኅነትን ይሰብካል፤ ሌላም ለሰው ልጅ እጅግ ጠቃሚ የሆኑ የሰላም ትምህርቶችን ያስተምራል፤ በትምህርቱም በነፍስና በሥጋ ያድናል፡፡

ዛሬ በሀገራችን አልፎ አልፎ የሚከሠተው የጥል መንፈስ ያለበት የሚመስል ክሥተት የመስቀሉ ስብከትና ትምህርት በቅጡ ካለማጤንና ካለማስተዋል የተነሣ እንደሆነ መገንዘብ አለብን፤ የመስቀልን ምልክት በአካሉ፣ በአንገቱ፣ በግንባሩና በልብሱ የተሸከመ ሰው ወንድሙን አይጠላም፣ መናናቅንም አያስተናግድም፣ መከፋፈልን፣ መለያየትን፣ መነታረክን፣ መጨቃጨቅንና ራስ ወዳድነትን የመሳሰሉ የዲያብሎስ የጥፋት ሠራዊት መስቀልን ባነገበ ክርስቲያን ዘንድ ቦታ የላቸውም፡፡ የመስቀሉ ትምህርት በእኛ አስተማሪነት የሰላም ምሥጢርነቱን በዓለሙ ሁሉ ለማዳረስ በምንሮጥበት በአሁኑ ጊዜ እኛው ራሳችን የመስቀል ትርጒም ሰላምና ፍቅር መሆኑን መረዳት አቅቶን በጥላቻ ዐይን የምንተያይ ከሆነ ስለመስቀል ማስተማር እንችላለን ብለን ሁላችንም በዓለም ሕዝብ ፊት ቃል የገባንበት የማስተማር ብቃታችን ጥያቄ ውስጥ ይወድቃል፤ መስቀል የገደለውን ጥል እንደገና ስበንና ጎትተን እንዳናመጣው ማሰብና መጠንቀቅ አለብን፡፡ ባለፉት ወራት በሀገራችን ውስጥ የተከሠቱ ግጭቶች ቤተ ክርስቲያናችንን ያሳዘኑና ያሳሰቡ መሆናቸውን ካሁን ቀደም ቤተ ክርስቲያናችን በየሚድያውና በየዐውደ ምሕረቱ በተደጋጋሚ ስትገልጽ መቆየቷ አይዘነጋም፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ሁሉም ኢትዮጵያውያን በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ከማእዷ ተቋዳሾች ናቸውና ሁሉም ኢትዮጵያውያን ልጆቿ እንደሆኑ በጽኑ የምታምንበት ጉዳይ ነው፤ የሁሉም ኢትዮጵያውያን አንድነት፣ ነፃነትና እኩልነት አክብራ ከሦስት ሺሕ ዘመናት በላይ የሀገር አለኝታ ሆና የኖረችበት ምሥጢርም ይኸው ከእግዚአብሔር የተቀበለችው ሕዝብን አስማምታ የመጠበቅ አደራ በሚገባ መወጣት በመቻሏ እንደሆነ የሚካድ አይደለም፡፡

ስለሆነም የቤተ ክርስቲያናችን ተልእኮ እንደትናንቱ ሁሉ ዛሬም ልጆችዋን በሰላምና በፍቅር ተንከባክባና አስማምታ ማገልገል ነውና የሀገራችን ሕዝቦች አንድነትና ነፃነት መከባበርና መተማመን፣ መቻቻልና መስማማት ተጠብቆ ይቀጥል ዘንድ እንደዚሁም የሀገራችን ሕዝቦች አንጸባራቂ ታሪክ ባህልና ትስስር በወቅታዊ ትኵሳት ፈተና ላይ እንዳይወድቅ ኢትዮጵያን ከልብ የሚወድ ኢትዮጵያዊ ሁሉ በሰላማዊ፣ በወንድማዊና በሀገራዊ ፍቅር ችግሮችን በጋራ ውይይት እየፈታ በቆየው የወንድማማችነት መንፈስ ልማቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል የበኩሉን ያደርግ ዘንድ ቤተ ክርስቲያናችን አጥብቃ ታሳስባለች፡፡

በመጨረሻም፡ ሕዝባችን ከሰላምና ከፍቅር፣ ከመከባበርና ከመተማመን፣ ከወንድማማችነትና ከመፈቃቀር ጥቅም እንጂ ጕዳት እንደሌለ በጥልቀት የሚገነዘበው ነው፤ ኢትዮጵያ ሀገራችን አሁን ያለችበት ሁኔታም ይህንን ሐቅ ያረጋገጠ ነው፤ በሰላምና በፍቅር ስንኖር ዐባይን የመሰለ ታላቅ ወንዝ መገደብ ችለናል፤ የሕዝቡ አንድነት ፍቅርና ሰላም እስከተጠበቀ ድረስ እንደአባቶቻችን ሌሎች ብዙ አስደናቂ የሆኑ የልማት ሥራዎችን ከመሥራት የሚገድበን እንደሌለ በሚገባ ተገንዝበናል፤ ስለሆነም የመስቀል መልእክትም፣ ትምህርትም ሰላምና ሰላም ብቻ ነውና የሀገራችን ሕዝቦች ከምንም በላይ ለሰላም ቅድሚያ በመስጠት ረገድ የማያወላውል አቋም እንዲይዙ በእግዚአብሔር ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc3 https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc32016-09-26 13:12:072025-01-28 13:13:14መስከረም 16 ቀን የ2009 ዓ.ም. በበዓለ መስቀል ላይ በአደባባይ የተሰጠ መልእክት
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: መስከረም 1 ቀን 2009 ዓ.ም የዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ ዓመት መልእክት Link to: መስከረም 1 ቀን 2009 ዓ.ም የዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ ዓመት መልእክት መስከረም 1 ቀን 2009 ዓ.ም የዘመን መለወጫ ርእሰ ዐውደ... Link to: በ35ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ የሰበካ ጉባኤ ጥቅምት 7 ቀን 2009 ዓ.ም. አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ Link to: በ35ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ የሰበካ ጉባኤ ጥቅምት 7 ቀን 2009 ዓ.ም. አስመልከቶ የተሰጠ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ፡፡ በ35ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ የሰበካ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top