• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

ከጥቅምት 12 እስከ 21 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡

October 31, 2013

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ፤ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቊጥር 164 በተደነገገው መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የመክፈቻው ሥርዐተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከጥቅምት 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ጥቅምት 21 ቀን 2006 ዓ.ም. ድረስ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባን በማካሄድ፤ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለኅብረተሰቡ የሚጠቅመውን፤ ለሀገርና ለዓለም ሰላም የሚበጀውን አጀንዳ በማመቻቸት በስፋትና በጥልቀት ተወያይቶ የሚከተለውን ውሳኔ አሳልፏል፤

1. የ32ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ውሳኔና የጋራ መግለጫ በምልአተ ጉባኤ የ2006 ዓ.ም. የሥራ መመሪያ እንዲሆን ጸድቋል፤

2. ከአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን እስከ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ድረስ በባለሙያዎች ተጠንቶ የቀረበውና በስላይድ የታየው የሥራ መዋቅር ወደታች ወርዶ በካህናት፣ በምእመናንና በሰንበት ትምህር ቤት ወጣቶች በውይይት ዳብሮ በሚገባ ተጠንቶና ተስተካክሎ ለቋሚ ሲኖዶስ እንዲቀርብና ቋሚ ሲኖዶሱም አይቶና ተመልክቶ በሥራ ላይ እንዲያውል ምልአተ ጉባኤው ወስኗል፤

3. ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በልማት ዘርፍ ዙሪያ የምታደርገው እንቅስቃሴ በማእከልም ሆነ በየአህጉረ ስብከቱ በበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ምልአተ ጉባኤው ተስማምቷል፤

4. የአብነት ትምህርት ቤቶችንና የካህናት ማሠልጠኛ ማዕከላትን፤ በጥንታዊነታቸውና በታሪክ መዘክርነታቸው ዕውቅና ያላቸውን ገዳማት፤ ወላጅ አልባ ዕጓለ ማውታ ሕፃናት እየተማሩ የሚያድጉበትንና ሴቶች መነኰሳዪያት በምናኔ የሚኖሩባቸውን ገዳማት በበለጠ እንዲጠናከሩ ማድረግ የታመነበት ስለሆነ፤ ለዚሁ አገልግሎት የሚውል በጀት በቤተ ክርስቲያኒቱ ማእከላዊ አስተዳደር ተጠንቶ ይቀርብ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ቀደም ሲል መመሪያን ሰጥቷል፤ አሁንም በድጋሚ መመሪያውን አጽንቷል፤

5. የዓለምን ሰላም፤ ፍቅር አንድነትን ጠብቆ መገኘት የሁሉም ዜጎች ኀላፊነት ስለሆነ ሁሉም ኅብረተሰብ አንድነትን ፈጥሮ አሁን በሀገራችን እየታየ ያለውን አክራሪነትና ጽንፈኝነትን በመቃወም ሰላምን የማስፈን ግዴታውን እንዲወጣ ቤተ ክርስቲያናችን ጥሪዋን ታስተላልፋለች፤

6. ከሀገራችን ውጭ ወደ ውጭው ዓለም ሕጋዊ ባልሆነ መንገድ የሚደረገው ፍልሰት የዜጎችን ሕይወት እየቀጠፈ በሀገርም ላይ ከፍተኛ ቀውስ እያስከተለ መሆኑ ስለሚታወቅ የችግሩን አስከፊነት ኅብረተሰቡ እንዲያውቀው በቤተ ክርስቲያናችን አስፈላጊው ትምህርት እንዲሰጥ ጉባኤው መመሪያ ሰጥቷል፤

7. የእናቶችና የዕጓለ ማውታ ሕፃናት፣ የአረጋውያንና የአረጋውያት፤ የሁሎችም ፍላጎት ተሟልቶ መኖር ይቻል ዘንድ ኅብረተሰቡ ትኵረት እንዲያደርግ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፤

8. ሀገራችን ኢትዮጵያ ከኤች አይ ቪ ኤድስ በሽታ፣ ከድንቊርና፣ ከድህነትና ኋላ ቀርነት ተላቅቃ ዓለም ወደ ደረሰበት መድረስ የምትችለው ማንኛውም ወገን ተቻችሎና ተከባብሮ ለሰላምና ለልማት ሥራ ሲነሣሣ ስለሆነ፤ ይኸው ታውቆ ሁሉም የየበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

9. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በርካታ የሥነ ጽሑፍ፣ የሥነ ጥበብ፣ ሥነ ሥዕልና ኪነ ጥበብ ቅርሶችና ሀብቶች ባለቤት መሆንዋ የታወቀ ስለሆነ፤ የእነዚህ የቤተ ክርስቲያኒቱ የዜማ መጻሕፍት፣ የትርጓሜ መጻሕፍት፣ የሕንጻዎች፣ የቋንቋ በአጠቃላይም ብሔራዊው የአእምሮ ንብረት ባለቤትነት መብቷ በሕግ ይከበር ዘንድ በቅርስ ጥበቃና ምዝገባ በቤተ መጻሕፍት ወመዘክር መምሪያ ተከታታይነት ጉዳዩ ለሚመለከተው የፍትሕ አካል ቀርቦ ውሳኔን እንዲያገኝ፤

10. የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የሢመተ ፓትርያርክነት በዓል እንደ ቀደሙት ቅዱሳን ፓትርያርኮች የተሾሙበት ዕለት በየዓመቱ የካቲት 24 ቀን እንዲከበር የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ወስኗል፤

11. ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪካዊነትና ቀዳሚነት ሁሉም ሰው መጻፍ ሲገባው እውነት ያልሆነውን በማስመሰል የሚነገረውን፣ የሚጻፈውን እውነታውንና ትክክለኛውን አስተካክሎ ለሕዝብ ለትውልደ ትውልድ ማስተላለፍ እንዲቻል መነሻ ይሆን ዘንድ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የኮሚቴ አባልነት ተጠንቶ የቀረበውን ጽሑፍ ምልአተ ጉባኤው በንባብ ሰምቶ ጉዳዩ ወደ ሊቃውንት ጉባኤ ቀርቦ የሊቃውንት ጉባኤውም ስለ ኢትዮጵያ ጥንታዊነትና ታሪካዊነት አብራርቶ፣ አስፍቶና አጒልቶ ለ2006 ዓ.ም. ለርክበ ካህናት ጉባኤ እንዲያቀርብ ወስኗል፤

12. የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ የቅዱስ ፍሬምናጦስ አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሦስቱም የቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳውያን ኮሌጆች በጀታቸው ተጠቃልሎ ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ገቢ እየሆነ በጀታቸውንም ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ እየበጀተ እንዲከፍል ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ወስኗል፤ ከዚህም ጋር በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ሥር የሚተዳደረው ከኮሌጁ ጋር ተያይዞ የሚገኘው አዲሱ ትልቁ ሕንጻ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ቤቶችና ሕንጻዎች፤ አስተዳደርና ልማት ድርጅት ሥር ሁኖ የሕንጻዎቹ ወርኃዊ የኪራይ ገቢም በሕጋዊ መንገድ እንዲሰበሰብ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤

13. የቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደር ድርጅትን በተመለከተ በሚፈርሱ ቤቶች ምትክ ቸል ሳይባል በትጋትና በንቃት የመልሶ ማልማቱ የሕንጻ ግንባታን ለማካሄድ የሚያግዝ ገንዘብ ማግኘት እንዲቻል ለየአህጉረ ስብከት፣ ለአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትና በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥር ላሉ የልማት ድርጅቶች የአክስዮን ሽያጭ እንዲደረግ ተወስኗል፤

14. ቤተ ክርስቲያኒቱ በሥሯ ያሉ ምእመናኖቿን በትክክል ቈጥራ መመዝገብ እንድትችል በሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ በኩል ቅጽ ተዘጋጅቶ በየአንዳንዱ ሀገረ ስብከት ኀላፊነት ቈጠራው በየአህጉረ ስብከቱ እንዲካሄድ ተወስኗል፤
15. ስለ ሰንበት ት/ቤቶች ውስጠ ደንብ ተጠንቶ የቀረበው መመሪያ ጸድቆ በሥራ ላይ እንዲውል ተወስኗል፤

16. በጉጂ ዞን ነገሌ ቦረናና የሲዳማ ዞን አህጉረ ስብከትን በተመለከተ በሁለት ተከፍለው ያለመግባባት ችግር ፈጥረዋል በሚል የተነሣው ሁከት ዓመታትን ካስቈጠረ በኋላ ችግሩን የፈጠሩት የሁለቱም ወገኖች ጉዳዩ በዕርቅ እንዲፈጸም ጥያቄ በማቅረባቸው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የዕርቀ ሰላሙን ሂደት የተቀበለ በመሆኑ ከቦታው ላይ ተገኝተው ዕርቀ ሰላሙን የሚያወርዱ ብፁዓን አባቶችን ሰይሟል፤ (ሀ) ብፁዕ አቡነ ማትያስ የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ (ለ) ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ረዳትና የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ (ሐ) ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊና በክልል ትግራይ የምዕራብ ሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሆን ስምምነቱንና ዕርቀ ሰላሙን አስፈጽመው የመጨረሻ የዕርቁን ሰነድ ለጉባኤው እንዲያቀርቡ ተወስኗል፤

17. የጣና ቂርቆስ ገዳም አንጡራ ሀብት የሆነው መስቀለ ያሬድ ተሰርቆ ወደ ውጭ ተወስዶ ከቆየ በኋላ ወደሀገሩ ተመልሶ በመንበረ ፓትርያርክ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ስለሚገኝ ገዳሙ መስቀሉ እንዲሰጠው በጽሑፍ በመጠየቁ ምልአተ ጉባኤው እንዲሰጥ ወስኗል፤

18. የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ልዩ ልዩ ፎቶ ግራፎች፣ መጻሕፍትና የተለያዩ ንዋያተ ቅድሳትና አልባሳት የመሳሰሉትን በተመለከተ ቋሚ ሲኖዶስ ኀላፊነት ወስዶ ኑዛዜም ካለ ሁሉንም እየመረመረና እያጣራ ለየሚመለከታቸው እንዲሰጥ ይደረግ ዘንድ ምልአተ ጉባኤው ወስኗል፤

19. ቤተ ክርስቲያናችን ወደፊት የምታከናውነውን ማኅበራዊና መንፈሳዊ አገልግሎት በዕቅድ የሚመራ እንዲሆን ለማስቻል በግንቦቱ ርክበ ካህናት ጉባኤ 2005 ዓ.ም. ተቋቁሞ የነበረው ኮሚቴ ያዘጋጀውን ጥናት ለጉባኤው አቅርቦ ጉባኤው ማብራሪያውን ካዳመጠ በኋላ ኰሚቴው ያላለቁ ሥራዎችን እንዲቀጥል በማለት መመሪያን ሰጥቷል፡፡

20. በጥንታዊቷ፣ በታሪካዊቷ በርእሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ዐውደ ምሕረት በመሠራት ላይ ያለው ቤተ መጻሕፍት ወመዘክሩ ግንባታን አስመልክቶ ከዐቢይ ኮሚቴው በቀረበው ሪፖርት ላይ በመነጋገር በቀጣይ የገቢ ማሰባሰቢያ ስልቶችን ያስቀመጠ ከመሆኑም በላይ ለጊዜው ለተቋራጩ ብር 5,000,000 (አምስት ሚሊዮን ብር) እንዲሰጠውና የቆመው የግንባታ ሥራ እንዲቀጥል ወስኗል፤

21. በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተጠንቶ እንዲቀርብ ስለታዘዘው የማኅበረ ቅዱሳን ደንብ ደንቡን እንዲያጠና የተመደበው ኮሚቴ ጥናቱ ለጊዜው ያልደረሰለት መሆኑን ስለገለጸ ለግንቦት ርክበ ካህናት 2006 ዓ.ም. ጥናቱ ተጠናቆ ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እንዲቀርብ ጉባኤው ትእዛዝ ሰጥቷል፤

22. የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅን በተመለከተ ኮሌጁን ማጠናከር አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ለኮሌጁ ዋና ዲን እንዲሾም ጉባኤው ውሳኔን አሳልፏል፤

23. ገዳማቱን መልሶ ማቋቋምና ማጠናከር ብሎም በነበሩበት ሁኔታ አደራጅቶ ሥራቸውን መቀጠል ይችሉ ዘንድ የሚያመለክት በመምሪያው በኩል ሰፊ ጥናት የተደረገ በመሆኑ ገዳማቱ የሚገኙትም በየአህጉረ ስብከቱ ስለሆነና ብፁዓን አበው የሌሉበት ጥናትም አጥጋቢ ውጤት ስለማይኖረው የተወሰኑ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከመምሪያው ተጠሪ ጋር ተገናኝተው ገዳማቱ እንዴት መቋቋምና መልማት እንዳለባቸው ጥናት ይደረግበት በሚለው ጉባኤው ተስማምቶ ጠለቅ ያለ ሐሳብ ከነመፍትሔው አጥንተው ለግንቦቱ 2006 ዓ.ም. ርክበ ካህናት ዓመታዊ ጉባኤ እንዲያቀርቡ፤ (1) ብፁዕ አቡነ ኤጲፋንዮስ የምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን (2) ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሊቀ ጳጳስና የሕንጻዎችና ቤቶች አስተዳደር ድርጅት የበላይ ኀላፊን (3) ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የከምባታ ሐዲያና ጉራጌ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን በመምረጥ ምልአተ ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ ወስኖአል፡፡

24. የመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሕንጻ ከጊዜ ብዛት የተነሣ ውኃ በማስገባቱ እድሳት የሚያስፈልገው ስለሆነ የእድሳቱም ጥናት በመቅረቡ የካቴድራሉ ሕንጿ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንና የሀገር ቅርስ እንዲሁም የቱሪስቶች መዳረሻ በመሆኑ የውስጥና የውጭ ቁመናውን እንደያዘ በጥንቃቄ እድሳቱ እንዲደረግ ጉባኤው ወስኗል፤

25. በውጭ ሀገር ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር ተጀምሮ የነበረው ዕርቀ ሰላም ወደፊት እንዲቀጥልና የቤተ ክርስቲያኒቱ አንድነት እንዲጠናከር ጉባኤ ተስማምቷል፤

26. በውጭው ዓለም ገለልተኛ አብያተ ክርስቲያናት ነን በሚል የሚገኙ ወገኖች ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው እንዲመለሱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ጥሪውን አቅርቧል፤

27. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጥንታዊትና ታሪካዊት እንደመሆኗ ሁሉ በቀጣይም አጠቃላይ ማኅበራዊም ሆነ መንፈሳዊ ሥራዎቿን በመሪ ዕቅድ በመምራት ሙስናና የመልካም አስተዳደር እጦትም ከሥሩ መቅረፍ እንዲቻል በባለሙያዎች የተጠናውን የመሪ ዕቅድ ዘገባ በመገምገም በቀጣይ ዕቅዱ ዳብሮ በሥራ መተርጐም በሚቻልበት ሁኔታ ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ ጉባኤው መመሪያ ሰጥቷል፤

28. አሁን ያለው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ተሻሽሎ እንዲቀርብ በተወሰነው መሠረት የተሻሻለው ረቂቅ ሕገ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት እንዲመለከቱት ረቂቁ የታደለ ሲሆን እንዲሁም በሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ታይቶና ሐሳብ ተሰጥቶበት በ2006 ዓ.ም. በግንቦት ርክበ ካህናት ውይይት እንዲካሄድበት ምልአተ ጉባኤው ተስማምቷል፤

ቅዱስ ሲኖዶስ ከላይ በተገለጹትና በሌሎችም መንፈሳውያንና ማኅበራውያን ጉዳዮች ላይ ለዐሥር ቀናት ያህል ሲወያይ ሰንብቶ አስፈላጊውን በመወሰን መደበኛ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት በጸሎት አጠናቅቋል፡፡

ቸሩ እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችን፣ ለሕዝባችን፣ ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣ ምሕረቱንና ፍቅር አንድነቱን ይስጥልን፡፡
እግዚአብሔር አምላካችን ይባርከን፤ ይቀድሰን፤ አሜን፡፡

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/007-3.jpg 664 1000 tc https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc2013-10-31 20:38:562024-12-03 20:43:00ከጥቅምት 12 እስከ 21 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መክፈቻ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ... Link to: ታኅሣሥ 29 ቀን የ2006 ዓ.ም. የልደት በዓል አስመልክቶ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ታኅሣሥ 29 ቀን የ2006 ዓ.ም. የልደት በዓል አስመልክቶ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ታኅሣሥ 29 ቀን የ2006 ዓ.ም. የልደት በዓል አስመልክቶ...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top