• Amharic  
  • English 
  • Home
  • Papal Messages
  • Biography
  • Patriarchs
  • Contact
  • Menu Menu

ታኅሣሥ 29 ቀን የ2006 ዓ.ም. የልደት በዓል አስመልክቶ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ

January 7, 2014

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትኖሩ፣
የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
በሕመም ምክንያት በየሆስቲታሉ ያላችሁ፣ እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፣

ወልድ ተብሎ ውሉድ እንድንባል ላበቃን ለጌታችን ለአምላካችንና ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት እንኳን በሰላም አደረሳችሁ!!

“ወናሁ ትፀንሲ ወትወልዲ ወልደ ወትሰምይዮ ስሞ ኢየሱስ ዘውእቱ ያድኅኖሙ ለሕዝቡ እምኀጢአቶሙ፤እነሆ ትፀንሻለሽ፣ ወንድ ልጅንም ትወልጃለሽ፣ ሕዝቡን ከኀጢአታቸው ያድናቸዋልና፣ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ” (ሉቃ. 1፥31፤ ማቴ. 1፥21)፡፡

ሁላችንም እንደምናውቀው፤ ዘለዓለማዊና ቀዳማዊ የሆነ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ሰው ሆኖ እንዲወለድ ምክንያት የሆነው፣ የሰው ኀጢአት ነው፡፡ ሰው በኀጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር ተለይቶ ክብሩን ካጣ በኋላ፣በነፍሱም ሆነ በሥጋው፣ለአጠቃላይ ውድቀት ተዳረገ፤ ንጹሕ የነበረ ባሕርዩ እንደ ሰኔና እንደ ሐምሌ ጎርፍ ደፈረሰ፤ የኀጢአት ድፍርሱም እየባሰና እየከፋ ከመሄድ በቀር፣ መሻሻል አላሳየም፤ ይሁንና የክብር አምላክ የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን፣ ለክብር በክብር የፈጠረውን የሰው ልጅ፣እንደ ወደቀ ሊቀር አልፈለገምና፣የመዳኛ ዘዴ አበጀለት፡፡

አምላካችን እግዚአብሔር፣ሰውን የማዳን ሥራው፡- መቼ? በማን? የት? እንዴት? እንደሚከናወን፣ አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ሙሉ በትንቢት፣ በምሳሌ፣ በራእይና በቀመረ ሱባዔ፣በቅዱሳን ነቢያቱ አማካኝነት፣ ለዓለም ሲገልጽ ቆየ፡፡ በእርሱ የተያዘው ቀጠሮ ሲደርስ፣በፊቱ የሚቆመውን መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልን፤ወደድንግል ማርያም ላከ፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም፣ከእግዚአብሔር ንገር ተብሎ የተላከበትን መልእክት ይዞ፣ወደ ድንግል ማርያም መጣ፤ እንዲህም አላት “እነሆ ትፀንሻለሽ፤ ወንድ ልጅንም ትወልጃለሽ፤ ሕዝቡን ከኀጢአታቸው ያድናቸዋልና፣ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ፤ እርሱ የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ይባላል፤ አላት” ከዚህ አገላለጽ በመነሣት፣ፍሬ ነገሩን ስናስተውል፣ ከቅድስት ድንግል ማርያም የሚወለደው ሕፃን፡- ዕሩቅ ብእሲ (ተራሰው) ሳይሆን፣ የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር መሆኑን፣ የስሙ ትርጓሜም መድኀኒት ማለት መሆኑን፣ መድኀኒትነቱም ለሕዝቡ ሁሉ መሆኑን፣ ሕዝቡን የሚያድናቸውም ከኀጢአታቸው መሆኑን፣ በማያሻማ ሁኔታ ማወቅ ይቻላል፡፡

የጌታችን መድኀኒትነት ድንበር የለሽና፣በሁሉም በሽታዎች ላይ የሚሠራ ቢሆንም፣በዋናነት ግን፣በትልቁ የኀጢአት በሽታ ላይ ያነጣጠረ መድኀኒት መሆኑን፣ በተጠቀሰው ኀይለ ቃል መረዳት ይቻላል፡፡ ምክንያቱም በዓለም ላይ የሚታየውን ክፉ በሽታ ሁሉ፣ሰበብ በመሆን ጎትቶ ያመጣብን ይህ ኀጢአት ነውና፣ጌታችን በዋናነት እርሱን ለመደምሰስ መምጣቱን ለማሳየት፣ ከኀጢአታቸው ያድናቸዋል ተብሎ በግልጽ ተለይቶ ተነገረ፤ በሽታው ትልቅ መሆኑን የምንረዳውም፣ትልቅ ዋጋ ያለው መድኀኒት፤ ያውም የእግዚአብሔር ልጅን ያህል፣ለመሥዋዕትነት ያስፈልገው በመሆኑ ነው፡፡ ለመሆኑ የኀጢአት በሽታ የሚያስከትለው ጒዳት ምንድን ነው? ያልን እንደሆነ፤ ሰውን ከእግዚአብሔር በማራቅና እግዚአብሔርን በማሳጣት፣ሰውን ማዋረድ፣ ማጎሳቈልና መግደል ነው፤ ሰው እግዚአብሔርን ካጣ፣ሁሉንም ያጣል፤አዳም አባታችንና ሔዋን እናታችን ያጡትም ይህንን ታላቅ ሀብት ነበር፤እግዚአብሔርን ሲያጡ፤ሁሉንም አጡ፤ ኀጢአተኞችም ሆኑ፤ኀጢአተኛ ማለት ያጣ፣የነጣ ማለት ነው፤ምንን ያጣ? እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔር የሆነውን ሁሉ ያጣ ማለት ነው፤ ሰው ከእግዚአብሔር ከተለየ፡ በአጠቃላይ መልካም የሆነ ነገር ሁሉ የለም፤ሊኖር የሚችለው ተቃራኒው ነው፤ እርሱም፡- ሞት ፣ በሽታ፣ ድህነት፣ ጠብ፣ መለያየት፣ ውርደት፣ የመሳሰለው ክፉ ነገር ሁሉ ነው ሊኖር የሚችለው፤ ከዚህ አንጻር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ሕዝቡን ከኀጢአታቸው ያድናቸዋል ሲባል፣ በዋነኛነት እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔር የሆነውን ሁሉ ከማጣት ያድናቸዋል ማለት ነው፤ ይህንም በራሱ መሥዋዕትነት፣ሰውን ከእግዚአብሔር ጋር ስላስታረቀና ስላገናኘ፣ ድኅነታችንን በዚህ አረጋግጦልናል፤ ፈጽሞልናልም፤ (1 ቆሮ 5.19)፡፡

ዛሬ፣ እግዚአብሔርንና የእርሱ የሆነውን የምናጣበት የኀጢአት በሽታ፣በጌታችን ተወግዶአል፤ አሁን በፊታችን ቆሞ እየጠበቀን ያለው ኀጢአት ሳይሆን፣በኢየሱስ ክርስቶስ የተገኘው ጽድቅ ነው፤ ጽድቁን ተከትሎ ደግሞ፣እግዚአብሔርና የእርሱ የሆነው መልካም ነገር ሁሉ፣ ማለትም፣ መንግሥተ ሰማያት፣ ዘለዓለማዊ ሕይወትና ዘለዓለማዊ ክብር፣በፊታችን ቆመው እየጠበቁን ነው፤ እነኝህም ጌታችን ዳግመኛ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ፣እውን የሚሆኑ ናቸው፤ (1ጴጥ 1.5-7)፡፡

ዛሬ፣የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን በዓለ ልደት በታላቅ ድምቀት የምናከብርበት ዋናው ምክንያት፣ በኀጢአታችን ምክንያት ያጣናቸውን እግዚአብሔርና የእርሱ ሀብታት ሁሉ፣በእርሱ ፍጹም ምሕረትና ፍቅር፣ እንደገና ያገኘናቸው መሆናችን፣ በቤተ ልሔም በግልጽ የታየበት ዕለት ስለሆነ ነው፤ የጌታችን፣ ሥጋችንን ተዋሕዶ መገለጥ፣ የመላእክት የደስታ ዝማሬ፣ የእረኞችና የሰብአ ሰገል ተኣምራዊ ጒዞ፣ የኅብረታችን መመለስን ይገልጻሉ፤ የእኛ አካለ ሥጋና፣የእርሱ አካለ መለኮት፣በተዋሕዶ አንድ አካል ሆኖ በቤተ ልሔም መወለድ፣ሰው አጥቶት የነበረውን የእግዚአብሔር ኅብረት ማግኘቱ ብቻ ሳይሆን፣በአካለ ቃል ርስትነት፣አምላክ ለመሆን በመብቃቱ የኀጢአት ግንብ መደርመሱ እርግጥ ሆነ፤ የተፈለገው ትልቅና ወሳኝ መድኀኒትም ይሄ ነው፤ እግዚአብሔር፣ይህን ያህል ከወደደን፣ማለትም፣ ከመለኮት ጋር ለመዋሐድና፣ የመለኮት የሆነውን ሁሉ ባለቤት ለመሆን ካበቃን፣ይህን ላደረገልን አምላክ ምን ውለታ መክፈል እንችላለን?

እርግጥ ነው፣ለአምላክ የሚሆን ውለታ ላይገኝ ይችላል፤ ነገር ግን፣ለእርሱ ያለንን ፍቅር ለመግለጽ የሚያስችለን ተጨባጭ የሆነ ግብረ መልስ መስጠት፣ ከሁላችን ይጠበቃል፤ይህ ለሰው ሁሉ የሚቻል ነው፡፡ እርሱ፣ ሥጋችንን ከአፈር አንሥቶ፣ በተዋሕዶ የራሱ አካል እንዳደረገው፣እኛም በድህነትና፣ በስደት ምክንያት በሰው ሀገር አሠቃቂ የሆነ እንግልት እየደረሰባቸው የሚገኙ ወጣት ልጆቻችን፣አካላችን ናቸውና፣ ደግፈን በሁለት እግራቸው እንዲቆሙ ማድረግ ይጠበቅብናል፤ ከዚህ አኳያ መንግሥት ከፍ ያለ ገንዘብ በመመደብና አስፈላጊውን የዲፕሎማሲ ሥራ በመሥራት፣በሰው ሀገር ለከፍተኛ ጒዳት ተጋልጠው የነበሩትን ዜጎች፣ በፍጥነት ወደ ሀገር እንዲመለሱ ያደረገው ተግባር፣ቤተ ክርስቲያናችን በከፍተኛ አድናቆት ትመለከተዋለች፡፡

ለወደፊትም እንደዚህ የመሰለውን ወገንን የመታደግ ሥራ ለማከናወን መንግሥት በሚንቀሳቀሰበት ሁሉ፣ቤተ ክርስቲያናችን የበኩሏን ከማድረግ ወደኋላ እንደማትል በዚህ አጋጣሚ ታረጋግጣለች፡፡ ወጣት ልጆቻችንም፣ተሰዳችሁ ዋስትና የሌለውን የባዕድ ሀገር ሀብት ከመቋመጥ ይልቅ፣በሃይማኖታችሁና በሀገራችሁ ሆናችሁ፣ሥራን ሳትንቁና ሳታማርጡ ሌት ከቀን ጠንክራችሁ ሥሩ፤ጊዜያችሁን በሥራ ብቻ በማዋል አስተማማኝ ሀብት ማምጣት እንደምትችሉ አምናችሁ፣ ሀገራችሁን አልሙ፤ በሀገራችሁ ከብራችሁና ተደላድላችሁ፣ በክብር የምትኖሩበትን አስተሳሰብ መከተል፣ ቀዳሚ ምርጫችሁ ይሁን፤ እንደዚህ ያለውን ችግር ሁሉ በማስወገድ፣ዘላቂና መሠረታዊ የሆነ መፍትሔ በሀገራችን ላይ ለማምጣት፡- በመንፈስ፣ በኢኮኖሚና በማኅበራዊ አገልግሎት ያደገችና የበለጸገች ሀገር፣ እውን ለማድረግ በሚደረገው ርብርቦሽ፣ሁላችንም በመተባበርና በቀጥታ በመሳተፍ፣ የድህነት ቅነሳ መርሐ ግብሩን፣በተፋጠነ ሁኔታ ማሳካት ይኖርብናል፡፡ በተለይም፣ በዚህ የደስታና የኅብረት በዓል፣ የእግዚአብሔር ልጆችና ፍጡራን የሆኑ ወገኖቻችን፣ ምግበ ሥጋ እየሸተታቸው፣ በምግብ ዕጦት ምክንያት ጾም እንዳይውሉና፣ እግዚአብሔር እንዳያዝንብን፣ ከእኛ ጋር በማእዳችን እንዲካፈሉ ማድረግ አለብን፤ ለእግዚአብሔር ፍቅር የምንሰጠው ግብረ መልስ ይኸው ነው፤ እግዚአብሔርና ሕዝብ፣ሕዝብና ሕዝብ፣ አንድ ላይ አገናኝቶ ለሰመረ ሀገራዊ ውጤት የሚያበቃንም እንደዚህ ያለ መተዛዘንና መረዳዳት፣ መተጋገዝና መደጋገፍ፣ መቻቻልና መስማማት ፣ መተሳሰብና መከባበር ሲኖር እንደሆነ መዘንጋት የለብንም፡፡ በመሆኑም ሕዝበ ክርስቲያኑ በዓሉን ከተቸገሩ ወገኖቹ ጋር በአንድ ማእድ እንዲያከብር፣ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

መልካም የልደት በዓል ያድርግልን፤

እግዚአብሔር ሁላችንንም ይባርከን ይቀድሰን፤ አሜን።

Share this entry
  • Share on Facebook
  • Share on X
  • Share on WhatsApp
  • Share on Pinterest
  • Share on LinkedIn
  • Share on Tumblr
  • Share on Vk
  • Share on Reddit
  • Share by Mail
https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/001-2-1000.jpg 664 1000 tc https://eotcp.org/e/wp-content/uploads/logo-en.svg tc2014-01-07 10:24:332024-12-05 10:25:58ታኅሣሥ 29 ቀን የ2006 ዓ.ም. የልደት በዓል አስመልክቶ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ
Search Search

Recent Posts

  • ሃይማኖተ እግዚአብሔር በኢትዮጵያ
  • የኢትዮጵያ መንበረ ፓትርያርክ እና ሐዋርያዊ የሥልጣነ ክህነት ትውፊት
  • የካቲት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው የዐቢይ ጾምን መግባት በማስመልከት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ አስተላልፈዋል
  • ጥር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት አዋጅ
  • በቅዱስነታቸው ዘመነ ፕትርክና የተከናወኑና በታሪክ የሚዘከሩ ዐበይት ተግባራት፤

Archives

  • February 2025
  • December 2024
  • October 2024
  • September 2024
  • August 2024
  • June 2024
  • May 2024
  • March 2024
  • October 2023
  • September 2023
  • November 2022
  • October 2022
  • September 2022
  • August 2022
  • June 2022
  • May 2022
  • April 2022
  • February 2022
  • January 2022
  • October 2021
  • September 2021
  • August 2021
  • May 2021
  • March 2021
  • January 2021
  • November 2020
  • October 2020
  • September 2020
  • August 2020
  • May 2020
  • April 2020
  • March 2020
  • February 2020
  • January 2020
  • November 2019
  • October 2019
  • September 2019
  • July 2019
  • June 2019
  • May 2019
  • April 2019
  • March 2019
  • January 2019
  • October 2018
  • September 2018
  • August 2018
  • July 2018
  • May 2018
  • April 2018
  • February 2018
  • January 2018
  • October 2017
  • September 2017
  • August 2017
  • July 2017
  • June 2017
  • May 2017
  • April 2017
  • March 2017
  • February 2017
  • January 2017
  • October 2016
  • September 2016
  • August 2016
  • June 2016
  • May 2016
  • April 2016
  • March 2016
  • January 2016
  • November 2015
  • October 2015
  • September 2015
  • August 2015
  • May 2015
  • April 2015
  • February 2015
  • January 2015
  • November 2014
  • October 2014
  • September 2014
  • August 2014
  • May 2014
  • April 2014
  • February 2014
  • January 2014
  • October 2013
  • September 2013
  • June 2013
  • May 2013
  • March 2013
© Ethiopian Orthodox Tewahedo Church | Website by atbiya.com
  • Link to Facebook
Link to: ከጥቅምት 12 እስከ 21 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ Link to: ከጥቅምት 12 እስከ 21 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች፡፡ ከጥቅምት 12 እስከ 21 ቀን 2006 ዓ.ም የተካሄደው ቅዱስ... Link to: ጥር 11 ቀን የ2006 ዓ.ም የጥምቀት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ Link to: ጥር 11 ቀን የ2006 ዓ.ም የጥምቀት በዓል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ጥር 11 ቀን የ2006 ዓ.ም የጥምቀት በዓል ቃለ ምዕዳንና...
Scroll to top Scroll to top Scroll to top